መለያዎች

ልጥፎችን በመለያ ጨዋታ እና ቀልዶች በማሳየት ላይ። ሁሉንም ልጥፎች አሳይ
ልጥፎችን በመለያ ጨዋታ እና ቀልዶች በማሳየት ላይ። ሁሉንም ልጥፎች አሳይ

ማክሰኞ 14 ማርች 2017

የካህኑ የመጨረሻ ቃል

አንድ ካህን በጠና ታሞ ከተኛበት ሆስፒታል ውስጥ እንዳለ በነፍስ ተይዞ እያጣጣረ፣ አንድ ፖሊስ እና  አንድ ፖለቲከኛ እንዲጠራለት ዶክተሩን አጥብቆ ለመነ።

ከደቂቃዎች በኋላ እንዲጠሩለት የጠየቃቸው ሰዎች ከሆስፒታሉ ተገኝተው ከአልጋው ግራ እና ቀኝ ቆመው ነበር። 

ካህኑ የሁለቱንም እጅ የቀረውን እንጥፍጣፊ አቅም አሟጥጦ ያዘ። ፖለቲከኛው ሰው ግን እጅግ ተጨንቆ ጠየቀው፦

“እኛን ለምን ብለህ እንዳስጠራኸን አልገባኝም። ግን ለምንድን ይሆን?”

ካህኑ ትንፋሹን ሰብስቦ እንዲህ አለ፦

“እኔም ልክ እንደ ኢየሱስ በተመሳሳይ መንገድ በሁለት ወንበዶች መካከል መሞት እፈልጋለሁ ...”

እናም ሞተ !!!!

ሰኞ 9 ጃንዋሪ 2017

በእንክርዳድ ማሳ ላይ (ስኬች)

(ኄኖክ ስጦታው)

*1*
ስንዴ እና ገብስ እንክርዳድ ተነቅሎ ከተዘጋጀው የማሳ ላይ ተዘሩ።

“ሞተን እየተቀበርን መሆን አለበት ” አለ ገብስ።

“አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ” የተባለው ቃል እየተፈፀመ ነው። ሲል ስንዴ መለሰ።

*2*

ጥቂት ዘሮች በወፎች ተበሉ። ብዙዎችም መበስበስ ጀመሩ። መበስበሳቸው የህይወታቸው ፍፃሜ አልነበረም። የሌላኛው ሕይወት ጅማሬ እንጂ።

*3*
የማቆጥቆጥ ዘመን

“እነሆ የመጨረሻው ዘመን ፍሬዎች እንሆን ዘንድ ለፍርድ ተነስተናል።” ሲል አንዱ ስንዴ አጠገቡ ላለው ሌላ ስንዴ ተናገረ።

“አይደለም። ፀድቀን ነው። ዙሪያህን ተመልከት! እኛ ብቻ አይደለንም የፀደቅነው። ከመካከላችን ጥቂት ወንድሞቻችን ፀድቀዋል።”

ገብስ ተናገረ “እኔ ከመሰሎቼ ነጥሎ ከናንተ መካከል እንድበቅል ያደረገው ፈጣሪ ተቆጥቶ ቢሆን ነው።” አለ ዙሪያውን ለከበቡትን ስንዴዎች።

እንክርዳድ ግን ከመካከላቸው ሆኖ“ወዶኛልና አዳነኝ” እያለ ጮክ ብሎ ይዘምር ነበረ።

ማክሰኞ 6 ሴፕቴምበር 2016

ከራስ ባህሪይ ጋር ጦርነት

አንድ የቼሮኬ አዛውንት ለልጃቸው ልጅ ይህን ታሪክ አጫወቱት፣
"የእኔ ልጅ፣ በሁለት ተኵላዎች መካከል ታላቅ ጦርነት ተፈጠረ። አንደኛው ተኩላ #ክፉ ነው። ይህም ማለት፣  ቁጣ፣ ቅናት፣ ስግብግብነት፣ ቂመኝነት፣ በየበታችነት ስሜት እና በውሸት የተሞላ ነው።
“ሌላኛው ተኩላ ደግሞ #ጥሩ ነው። ይህም ማለት… ደስታ፣ ሰላም፣ ፍቅር፣ ተስፋ፣ ትህትና፣ ደግነት፣ አዘኔታ፣ እና ሀቀኝነት ያሉት ነው።”
ህፃኑ ልጅ እንዲህ ሲል አያቱን ጠየቀ፦ "የትኛው ተኵላ አሸነፈ?"
አዛውንቱ ለጥቂት ጊዜ ያክል ዝም ብለው ቆይተው ይህን መለሱ፦
"አሸናፊው ያለው ከውስጥህ ነው።"

ረቡዕ 8 ጁን 2016

ወጣ ያሉ የግዕዝ ቅኔያት

ወጣ ያሉ የግዕዝ ቅኔያት

በአጋጣሚ አግኝቼ ያነበብኩት መጽሐፍ ነው። “ቅኔያዊ የእውቀት ፈጠራ“ ይሰኛል ርዕሱ። በማርዬ ይግዛው ተሰናድቶ በ የጀርመን የባህል ማዕከል፣ 2006 ዓ.ም የታተመ ነው።

“…አብዛኛዎቻችን ቅኔ ኃይማኖታዊነት ብቻ የሚንጸባረቅበት ይመስለን ይሆናል። ቅኔ የማይዳስሰው ነገር የለም። የጾታ ተራክቦን (የግብረ—ሥጋ ግንኙነትን) እና መዳራትን ጨምሮ።…” እያለ ይቀጥላል የመጽሐፉ ትንታኔ።
ቀነጫጭቤ ጋበዝኳችሁ፦

ቅኔ ፩

ኢይጠፍእ ሕልጽ እሳት ላዕሉ ወታህቱ፣
እስኪት ጉልጥምት እስመ ተዳፈነ ቦቱ።
ትርጉም፦
          እምስ የላይና የታቹ እሳት አይጠፋም፤
          ቁላ/ጉልጭማ (እንጨት) ተዳፍኖበታልና።
ምስጢር ፦

ጉልጭማ የተዳፈነበት እሳት እንደማይጠፋ ቁላ የሚገባበት እምስም ሙቀት አይለየውም። በተለምዶ እሳት የሚጠፋው በውሃ፣ ሙቀት የሚበርደውም በቀዝቃዛ ነገር ነው። እምስ ግን ራሱ የቁላን ትኩሳት የሚያስታግሰው በማይጠፋ ሙቀት ነው እንጂ ከቀዘቀዘ አስተናጋጅነቱ ይቀራል።

እሳቱ/ሙቀቱ የማይጠፋ የሚለው የመራባት የሰው እንስሳዊ ህይወት ምንጭ መሆኑንም ያመላክታልና በዚህ ግልፅ ወሲባዊ ቅኔ ውስጥም ስለ ሕይወት ቁም ነገር አልጣበትም።

ቅኔ ፪

እታገኝ ደመርኪ እምላእለ ክብርኪ ክብር፣
ለነዳይ እስኪት እስመ ወሀብኪ ቂንጥር።

ትርጉም ፦
         እታገኝ በክብር ላይ ክብር ጨመርሽ
         ለድሃው ሰው ቁላ ብልት በመጽውተሽ። (መጽውተሽዋልና)

ምስጢር ፦
ይህ ቅኔ እማሆይ ገላነሽ እታገኝ የተባለች ልጃቸው ስታገባ የተቀኙት ነው ይባላል። ሰሙ በዚህ ዓለም ለተራቡ ሰዎች የሥጋ ብልት ሳይቀር የሚመጸውቱ ሰዎችን ይገልፃል። ባለቅኔዋ እታገኝ የተባለችው ልጅ ስታገባ ለተራበ ቁላ የሚገባውን ምግብ በመስጠት የጽድቅ ሥራ ማድረጓን አስመስጥረዋል።

ቅዳሜ 21 ሜይ 2016

ለምን አልስቅ?!

እስቃለሁ!
(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)

የክልከላ እና የተግሳፅ ህግ ተሸብበን ሳቅ አልባ ሆንን። የሳቅ መንስኤዎች በሙሉ ከጊዜ ወደጊዜ እየተመናመኑ መጡ። ሳቅ አጠር ሆነን የሚስቁትንም አሳቀቅን። የሚያስቀው አያስቀንም። ለቀልድም ሆነ ጨዋታ መራር ትርጉም ፍራቻ ቁጥብ ሆንን። የክልከላ ህግ ለስሜት ቅድመ ሳንሱርነት ተሹሞ በላያችን ላይ ሰለጠነ። ስሜት ፈንቅሎት እንዳይወጣ በሳቃችን ላይ ከመርግ የከበደ ጭፍግ ቆለልንበት።

የሚስቅና ሌሎችን ለማሳቅ የሚወድ እንደ "ተራ ቧልተኛ" ተቆጠረ። መሳቅም ሆነ ማሳቅ ከበደ። ለአሳሳቅ ስልት ተበጀለት።

እንዴት እንደማይሳቅ የሚመክሩ ጭፍግ መካሪዎች በዙ። ሳቃቸውን አፍነው የሚወቅሱ በዙ። በፍራቻ ተሸብሸው የሚገስፁ በዙ። በይሉኝታ ታፍነው ፊታቸውን የሚጨፈግጉ በዙ። በንዴት ቱግ ብለው የሚንጨረጨሩ በዙ። "አያስቅም" የሚሉ በዙ።

ሳቅ ጠፋን። አሳሳቅ ጠፋን። ከአዘኑት በላይ ያዘንን መሳይ፣ በሚስቁት ላይ የምንበሳጭ…  የተውሶ ፊቶች ጥርቅም ሆንን። ሳቅ ጠፋን! አሳሳቅ ጠፋን። በላያችን ላይ እንዴት እንደሚሳቅ የሚያስተምር ትምህርት ቤት ተከፈተ።

እናም ዛሬ ከዚህ በታች ያለውን ቀልድ ከአመት በኋላ ድጋሚ ሳነበው በድጋሚ ሳቅኩ።

————
አንድ ሰሞን በአንድ አገር ዋና ከተማ ውስጥ ብዙ የጦር መሳሪያ ስለጠፋ የቤት ለቤት ፍተሻ ተጀምሮ ነበር፡፡ ሁሉም ተፈትሾ፣ ተፈትሾ ጳጳሱ ቤት ይደረርስና እዛ ገብተው ሁሉንም ክፍሎች ፈትሸው ምንም ስላልተገኘ በስተመጨረሻ እሳቸው ወደ ተቀመጡበት ሄደው ሲፈትሹ በጣም ብዙ መሳሪያ ያገኛሉ፡፡ ፈታሾቹም ተገርመወው፡-

“ይሄን ሁሉ መሳሪያ ከየት አገኙት?” ብለው ሲጠይቋቸው ፡-

“ሚኒስትሩ በስለት ያስገባው ነው”

የሁለት አህዮች ወግ

ሁለት አህዮች … እያወሩ ነው።

የመጀመሪያው አህያ፣ “የእኔ ባለቤት እንዲሁ ከመሬት ተነስቶ በዱላ ይደበድበኛል” ይለዋል በምሬት።

ሁለተኛ አህያ፣ “ታዲያ ለምን ትተኸው አትሄድም?”

የመጀመሪያ አህያ፣ “እሱስ እውነትህን ነው። እንዳልከው ለማድረግ በተደጋጋሚ አስቤ ነበር። ነገር ግን እጅግ በጣም ውብ እና መልካም ፀባይ ያላት ሴት ልጁን ሳስብ ሃሳቤን እቀይራለሁ።” 

ሁለተኛው አህያ፣ “እንዴት ማለት? አልገባኝም”

የመጀመሪያው አህያ፣ “አሳዳሪዬ በዚህች ቆንጆ ልጁ ሲበሳጭ… ‘አህያ ካልሆነ በቀር የሚያመዛዝን ሰው አያገባሽም!’ ሲል ይናገራታል፤ እኔም የምታገሰው ይህ ሁኔታ እስከሚፈጸምበት ጊዜ ብቻ ነው።”

ዓርብ 20 ሜይ 2016

ቆይታ (ከቀብር አስፈፃሚዎቹ ጋር)


☞ኄኖክ ስጦታው

ለሞት ያለኝ ግንዛቤ ግልፅና አጭር ነው። ሞት እድገት ነው፤ መወለድም እድገት። "የሰው ልጅ ከሞት በኋላ ያለውን ካለማወቅ ፍራቻ አያሌ መሸሸጊያ ፈጥሯል" ያለው ዲካርት መሰለኝ ።

ጓደኞቼ "እንሳለም" ብለው ሚካኤል ቤተክርስቲያን ጋር መኪናዋን አቆሙ።"ዛሬኮ አርሴማና ተክልዬ ይነግሳሉ፤ አትሳለምም?"

"አልሳለምም፤ እናንተ ደርሳችሁ እስክትመጡ ቀብር አስፈፃሚዎቹ መደብር ውስጥ እጠብቃችኋለሁ።"

ወደ ሬሳ ሳጥን መሸጫና ማደሻ መደብር አመራሁ። ብዙ አይነት የአስክሬን ሳጥኖች ተደርድረዋል። ሁለት አይነት አበቦች (በወረቀት ተሰርተው ቀለም የተነከሩ እና ከበቀሉበት የተዘነጠፉሸአበቦች) ደጃፉ ላይ አየሁ። ፊትለፊት ሆነው እይታዬን ያልሳቡት ለምን ይሆን? ስልኬን አውጥቼ ፎቶ ማንሳት ጀመርኩ።

ሰዎች እንዳላዩ ሆነው ከሚያልፏቸው ነገሮች አንዱ እንደዚህ አይነት መደብሮችን ነው። መደብሩ በራፍ ላይ አበቦች አሉ። ከአበቦቹ በላይ ያሉት በላይ በላያቸው የተደራረቡ ሳጥኖች ግን አበቦቹን ጋርዷቸዋል። አ አ!  አይደለም። አስክሬን ሳጥኑ ከፊት ካልሆነ በቀር አበቦቹን እንዴት ከዕይታ ሊጋርዳቸው ይቻለዋል?

"ሄይ፣ ፎቶ ማንሳት ክልክል ነው!" የሚል ድምፅ ሰማሁ። ሁለት ወጣቶች ወደኔ መጡ።

ፎቶ ማንሳት ክልክል መሆኑን የሚገልፅ ምንም ምልክት የለም። ለምን ክልክል እንደሆነ ጠየኩ።

"የአስክሬን ሳጥኖቹ ዲዛይን ይሰረቅብናል። አይቻልም።"

"የሳጥኑ ዲዛይን ከሌላው በምን እንደሚለይ ማወቅ እችላለሁ?"

"የማትገዛ ከሆነ ብነግርህ ምን እጠቀማለሁ?"

"እኔ ባውቅ ምንስ የምታጣው ነገር አለ?"

"ለምንህ ነው ማወቅ የምትፈልገው?" ሲል ሌላኛው ጠየቀኝ።

"በቃ፣ ደስ ይለኛል። ሳጥኖቹን በቅርብ ሆኜ ባይ፣ አብሬያችሁ ውዬ ቀብር ባስፈፅም ደስ ይለኛል። በተለይ ከሳጥኖቹ መሐል የማስታወሻ ፎቶ ብነሳ… ደስ ይለኛል" አልኩ። እውነቴን ነበር።

እርስ በራሳቸው ተያዩና ፈገግ አሉ። ወደ ውስጥ እንድገባ ፈቀዱልኝና ትልቅ አልበም እንድመለከት ጋበዙኝ።
ለጨዋታ መጀመሪያ ያክል "ስራ እንዴት?" አልኩ።

"እግዚአብሔር ይመስገን"
(ምሥጋና ጥሩ ነው) 😱

የሚያምር የሬሳ ሳጥን አየሁና ዋጋውን ጠየኩ፦

"12ሺ ብር።" አለ።

"ዋጋው እንደዚህ የተወደደበት ምክንያት ምንድነው?"

"በኤምዲኤፍ ነው የተሰራው። እንደምታየው የሳጥኑ የላይኛው ክፍል ሙሉ መስታወት ነው። አስክሬኑ በሱፍ ሽክ ተደርጎ ይገነዛል።"

"ዋጋው አስክሬኑ የሚለብሰውን ሱፍ ጨምሮ ነው? "

"ልብሱን ቤተሰብ ነው የሚያዘጋጀው።"

"ለሴቶች ሲሆንስ?"

"አይቀንስም"

ሳቅኩ።
"ዋጋውን አልነበረም የጠየኩህ። አስክሬኑ የሴት ከሆነ ምን አይነት ልብስ ነው የምትገነዘው?"

እርስ በራሳቸው ተያዩ። መቼስ ሱፍ አያለብሱ።
ሁለተኛው መለሰልኝ፦
"የአገር ባህል ልብስ ሊሆን ይችላል። እነዚህ ባለሙሉ መስታወት ሳጥኖችን ግን እስካሁን የተጠቀምነው ለወንዶች ነው።"

"የአሜሪካ ሳጥንም አለን።" አለ ሌላኛው።

"የትኛው ነው?"

"እዚህ የለም። አልበሙ ላይ ላሳይህ…።" አልበሙን ተቀብሎኝ ገለጥ ገለጥ አድርጎ "ይኸው!" አለ።

ያምራል።

"ዋጋው ምን ያህል ነው?"

"35 ሺ ብር"

"እ?"
ደገመልኝ። በሰላሳ አምስት ሺህ ብር የ1972 አዲስ ብራንድ አፍሮ ቮልክስ መሸመት የሚችል ብር እንደሆነ አሰብኩት። የገረመኝ ግን ሌላ ነበር፦
"ሳጥን አስመጪ አለ ማለት ነው?"

"አስመጪ የለም። ከአሜሪካ አስክሬን ይመጣበትና የአገር ውስጥ ሳጥን ላይ ብር ጨምረን ከቤተሰቦቹ ላይ እንገዛዋለን።"

"እዝጎ!" (አልኩ በውስጤ)

ዓርብ 6 ሜይ 2016

ልዩነቱ ግልፅ ነው

ዮናስ ጨርጨር ስጋ ቤት ምሳ ልበላ ገብቼ ሳለ…ቴዲ አፍሮ ፊት ለፊቴ ካለው ጠረጴዛ ላይ ተቀምጦ ሥጋ እየበላ ነው።
ልዩነታችን አሰብኩት።
ግልፅ ነው!
እኔ ስጋ ቆራጩን አውቀዋለሁ፤ እሱን ግን ስጋ ቆራጩ ያውቀዋል 

ዓርብ 22 ኤፕሪል 2016

ፍተላ

(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)

ከዕለታት ባንዱ ጠዋት ነው።
ሌሊቱን ኦቭረን ጠዋት ላይ ነዳጅ ልቀዳ ማደያ ውስጥ ገባሁ።

"የስንት ልቅዳልህ?" አለ ነዳጅ ቀጂው።

"ደብል ቅዳልኝ" በግማሽ ልብ ሆኜ ነበር የመለስኩለት።

"የምን ደብል?"

ግሮሰሪ እንዳልገባሁ ትዝ ሲለኝ ፦ "ፉል አድርገው። የሃምሳ ብር!" አልኩት።

በግርምትና በድንጋሬ ከላይ እስከታች አይቶኝ እንዲህ አለ፦

"ላይተር ነው የምታስሞላው?"

ረቡዕ 2 ማርች 2016

ጥያቄ ጥያቄ ጥያቄ

አንዳንዴ፣ ራሴን እንዲህ ስል እጠይቀዋለሁ፦
ሰፊውን አለም  ማን አጠበበው?

እውነት ጀግና ማለት ለአገሩ የሞተ ነው?  የገደለ?

ለአገር መሞት ማለት፣  በሌላው መገደል ብቻ ነው? ወይስ መግደል?

የመሞት ዓላማው ከመግደል በመጠኑም ቢለይም ስንኳን ፣ ሰውን ያክል አምሳያ መግደል በርግጥ ጀግነት ነው?  ወይስ አረመኔነት? ወይስ ተፈጥሯዊ የሆነ የማንነት መገለጫ?!

ለአገር መሞት ነው ጀግንነት? ወይስ ፣ በሰው መገደል ነው ጀግንነት?!

እራሱ «ጀግንነት» ምንድነው?!

ክብር ነው?
ስሜት ነው ?
ወይስ
ሌላ?

ጀግና ማለት፣ ላመነበት አላማ የተገደለ ነው?! ወይስ… የገደለ?!

ገድሎ የሞተው ፣ ሞቶ ካሸነፈው የሚለየው በምንድነው?
በሕይወት?
በሞት?
በድል?
በሽንፈት?

. .
.
.
.
.
.
.
.
. .
ከጦርነቱ የተረፈ በርግጥ ጀግና ነው ?!

.
.
በርግጥ የቱ ነው ጠባብ?!

አገር ከዓለም ይጠባል?!

ዓለም ከአገር ይሰፋል?!

አስፍቶ ለተመለከተው በርግጥ ዓለም የአገር አካል ናት? ወይስ

ዓለም ከሰፈር ትጠባለች?!

እናም፣ ጥያቄው ማብቂያ የለውም። መልሱ ግን ይብሳል¡

“ቀልድ የማያውቁ ቀልዶች”

“ቀልድ የማያውቁ ቀልዶች”

“ብሶት ሲኾመጥጥ የቀልድ ቡኾ ይሆናል።”

አባባሉ የአለማየሁ ገላጋይ ነው። ከዚህ በታች ላሉት “ቀልድ የማያውቁ ቀልዶች” መግቢያ የተጠቀመው።

✧✧✧
ወጣቱ የጋራ መፀዳጃ ውስጥ ቁጭ ብሏል። ብዙ ሰዎች እየመጡ ያንኳኳሉ፦

“ሰው አለ!” ወጣቱ ነበር። እንዲህ እየመለሰ ከተቀመጠበት ሳይነሳ፣ ከገባበት ሳይወጣ ብዙ ቆየ። በሁኔታው ብስጭትም፣ ህመምም የተሰማቸው አዛውንት ድምፃቸውን ጎላ አድርገው፦

“ማነህ የኔ ልጅ፣ መቼም ሽንት ቤቱ የጋራችን ነው። እኛም ልንጠቀም ነው አመጣጣችን። ለረጅም ጊዜ ስለቆየህ ምን አለ ብትወጣ?” አሉት።

ወጣቱ ከውስጥ ሆኖ ንቅንቅ ሳይል “ቢወጣስ የት ይኬዳል?”
✧✧✧

ሴትዮዋ ጤፍ አስፈጭተው በመመለስ ላይ ናቸው። ተሸካሚው ከፊት ከፊት እየሄደ ቤታቸውን በውል በወለማወቁ ፣ “ቤትዎ በየት በኩል ነው?” ሲል አቅጣጫ ይጠይቃቸዋል።

ሴትየዋ ለፀብ እንደተዘጋጀ ወገባቸውን ይዘው፦
“ምን አልክ? ቤቴን ነው የጠየኸኝ? እንዴት ያለኸው ነህ? የአንድ ሺ አምስት መቶ ብር ጤፍ እቤት ይቀመጣል? ቀጥታ ወደባንክ! ከዛ እየተቀነሰ ነው የሚቦካው”
✧✧✧

አባወራው ቤተሰቡን መመገብ ተስኖታል። ስለዚህ ያገኙትን ለልጆቹ እያቃመሱ ከባለቤቱ ጋር ጦም ማደር ግድ ሆነ። በይበልጥ ሚስቱ እጅግ ተጎሳውላለችና ቤተሰቡ ለጎረቤት አፍ እንደተጋለጠ አባወራው ጠርጥሯል። ስለዚህ አንድ ዘዴ ዘይዶ ጠዋት ሽማግሌ ሰበሰበ፦

“ምንድነው ችግሩ?” አሉ ሽማግሌዎች።

“ይኸው አንደምታዩት ነው። ብዪ እላለሁ፣ ብዪ እላለሁ…” አለ አሉ።

ሚስት አልተማከረች ኖሮ “የታል የሚበላው?” ብትል

“ሳገኝ አልኩሽ’ንጂ” አለ አሉ።
✧✧✧

አንድ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ፣ በህብረተሰቡ የኑሮ ውድነት ደረጃ ላይ የአሰሳ ጥናት እያካሄደ ነው አሉ። ጥናት አድራጊው ወደ አንድ ሊስትሮ ጠጋ ብሎ አንዳንድ የመግባቢያ ጥያቄዎችን ካቀረበ በኋላ ፦

“እስኪ አሁን ደግሞ ወደ ቀን ወጪህ እንግባ”

“እሺ”

“ጠዋት ቁርስህን ምን ትበላለህ?”

“ሻይ በዳቦ”

“ምሳህንስ?”

“ባይ በዳቦ”

ጥናት አጥኚው፣ ልጁ በደሰቦና በሻይ ከዋለ እራቱን አጠራቅሞ በደንብ ሊበላ ነው ብሎ “እሺ ማሙሽዬ እራትህንስ?” ቢለው ልጁ ድንግጥ እያለ፦

“በልቶ ለመተኛት?!” ሲል መልሶ ጠየቀው…።
✧✧✧

"ቀልድ የማያውቁ ቀልዶች"
ዓለማየሁ ገላጋይ
"ኢህአዴግን እከሳለሁ" የወግ ስብስብ መጽሐፍ የተቀነጨበ

እሑድ 28 ፌብሩዋሪ 2016

የ“ሸኖ ቤት ሃሳቦች”

‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬የ“ሸኖ ቤት ሃሳቦች”
(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)

‪‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬
የ“ሸኖ ቤት ሃሳቦች” የማንበብ ሱስ የተጠናወተኝ ሁለተኛ ደረጃ ተማሪ ሳለሁ ነበር፡፡ በርግጥ ብዙዎቹ ሃሳቦች በጨዋ ቋንቋ “ፀያፍ” ተብለው የሚነገሩ ቢሆንም ብሶትና ምክርን በጨዋ ገለፃ የሚቀርቡ ሃሳቦችም አይታጡም፡፡ ያም ሆኖ ሕዝብ የሚጠቀምባቸው መፀዳጃ ቤቶች ስገባ በግድግዳው ላይ የተጻፉ ጽሑፎችን ማንበብ ያዝናናኛል፡፡

ሸኖ ቤትን ለመውደድ የፎክሎር ተማሪ መሆን አይጠይቅም፡፡ ከማይረቡ መፅሐፍት የተሻለ ምልከታን እና ሂዩመርን በሸኖ ቤት ሃሳቦች መቃረሜ በራሱ ለመፀዳዳት የማባክነውን ጊዜ የሚክስ ቁምነገር አላጣበትምና፡፡

“የዘርሲዎች ፍቅር” የተሰኘው ልቦለድ መፅሃፍ ላይ አንድ ገፀባሕርይ አስታውሳለሁ፡፡ በተለይ መፀዳጃ ቤት ስገባ ብዙ ጊዜ ትዝ ይለኛል፡፡ (አብሮኝ ይገባል - - ብል ይቀላል፡፡) ይህ ሰው ቁምነገርን የሚቃርመው ከመፀዳጃ ቤት ነው፡፡ ግድግዳ ላይ የሚጻፍ ግራፊቲ አልነበረም የሚያነበው፡፡ ሰዎች “ካካቸውን” የጠረጉበትን ወረቀት ሰብስቦ ኪሱ በመክተት እና በማንበብ ነበር፡፡

እነዚህ የግድግዳ ላይ ጽሁፎች ስለምንስ ይጻፋሉ? ግባቸው ምንድነው? ... ምክንያቱን እርሱት፡፡ ከየት መጡ የሚለው ምርምር አያሳስበኝም፡፡ ባለቤት አልባነታቸው በራሱ በቂ ምክንያት ነው፡፡ ምክንያት ከስም ይጀምራልና፡፡ ማንነቱን ለማወጅ የመፀዳዳት ባህሉን አደባባይ ላይ ከሚፈጣጥም ሰው ምንም አልጠብቅም፡፡ ማንነቱን በመጸዳጃ ቤት ግድግዳ ላይ የሚያሰፍር ማንነቱ ያልታወቀ ሰው ግን ታዳሚ ነኝ፡፡ (እስቲ ዛሬ የተመረጡ ትውስታዎቼን በሹካ ጨልፌ ላካፍላችሁ፡፡)

ለመጀመሪያ ጊዜ ካነበብኳቸው ውስጥ የሚመደብ የመፀዳጃ ቤት ሃሳብ እንዲህ የሚል ነበር፡-

“God is dead!” -Nietzshce
“Nietzshce is dead!” -God

ያኔ ይህን ሳነብ ያልገባኝ ብዙ ነገር ነበር፡፡ በርግጥ ኒቼ “እግዚአብሔር ሞቷል” በሚለው ግንዛቤው ዛሬም ድረስ (ሞቶም) ያወዛግባል፡፡ በሕይወት በነበረበት ጊዜ “እግዚአብሔር ሞቷል ፤ ሰዎችም ነፃ ወጥተዋል...” እያለ መስበኩን የተረዳሁትም ከጥቅሱ በኋላ ነበር፡፡ አመታት አልፈው፡፡ የኒቼን ሞት ጠብቆ እግዚአብሔር እንዲህ ማለቱን ግን መፀዳጃ ቤት እንደ ትንቢት ቀድሞ አሳውቆኛል፡፡ ጥበብ ከጲላጦስ መፅሐፍ ላይ ይህን ጥቅስ ሳነበው አልደነቀኝም፡፡ ጥቅሱን ሲያስታውሰኝ ግን የሆነ ነገር ግን ሸቶኝ ነበር፡፡ ያም ጠረን፣ ይህን አባባል ያነበብኩበት መፀዳጃ ቤት አጉል ጠረን ነበር፡፡

በአንድ ኮሌጅ መጸዳጃ ቤት ውስጥ ያነበብኩት ደግሞ እንዲህ የሚል መልዕክት ግድግዳው ላይ ተፅፎ አነበብኩ፡- “ምን ግድግዳው ላይ ታፈጣለህ!? አርፈህ አትፀዳዳም!?” ሆሆሆ... ሰዉ ጨምሯል!

በሌላ ዩኒቨርስቲ መፀዳጃ ቤት ውስጥም እንዲህ አይነት ትዕዛዝ አጋጥሞኝ እንደነበር አልረሳውም፡፡ በደቃቅ ጽሑፍ የተጻፈ መልዕክት ከመጸዳጃው በር ላይ ሰፍሮ አየሁና ከቅምጤ በመጠኑ ብድግ ብዬ ላነብ ስሞክር ያገኘሁት መልዕክት አስደንግጦ “የሚያስቀምጥ” ነበር፡፡ሃሳቡ እንዲህ የሚል ነበር፡- “ሰው ማለት አንተ ነህ፡፡ አሁን ወደነበርክበት ተመልሰህ አርፈህ እራ! ” የሚል ትዕዛዝ ፡፡

የሸኖ ቤት ግድግዳ ላይ ከተፃፉ ሃሳቦች ሌላው የማርከኝ እንዲህ የሚል ነው ፡-

“ቺክህን ጥሩ ነገሮች እንዴት እንደምታሳያት በማሰብ አትጨናነቅ፡፡ አሁን እየጣልክ ያለውን እንቁላል ግን ጠብሰህ እንዳታበላት አደራ! ስትጨርስ ውሃ ድፋበትና ከሌሎች እይታ ሰውረው!”

የሸኖ ቤት ግድግዳ ሃሳቦች አንዳንዴም ፍልስፍና ይቃጣቸዋል፡፡ በአንድ የሕዝብ መፀዳጃ ቤት ውስጥ ያነበብኩትሃሳብ ለዚሁ ምስክር ነው፡፡ እንዲህ ይላል፡-

[“መኖር ማለት፣ በምታባክነው ጊዜ የምታጣው ብኩንነት ነው፡፡ ለመኖር ስትል ከምታባክናቸው ሰዓታት ትልቁን ቦታ የሚይዘው ምን እንደሆነ ታውቃለህ?”

“አውቃለሁ” ካልክ ተሳስተሃል! በዚህ ሰዓት ማራት አልነበረብህም!!”]

ትውስታዬን ተደብቄ በተጠቀምኩበት የሴቶች መጸዳጃ ቤት ግድግዳ ላይ ባነበብኩት ልቋጭ፡፡

“በወንዶች ከሚነገሩ ብ-ዙ ውሸቶች መሃከል የማላምነው “ሮም በአንድ ቀን አልተገነባችም” የሚሉትን ብቻ ነው፡፡”

ማክሰኞ 23 ፌብሩዋሪ 2016

በቮልስ ያጉረመረምንበት ሰርግ ትዝታ

ይህ ትዝታ ይደንቀኛል። ጋራጅ የተዋወቅኩት ሰው ሰርግ ላይ መላው የቮልስ ባሉካዎች በአጃቢነት ተጋብዘን ነበር። አጃቢ መኪኖች በጠቅላላ ቮልስ ዋገን ናቸው። እውነት ለመናገር በአገሪቱ ውስጥ ካሉ ሾልሶች አንድም የቀረ አይመስልም።

ሰርጉን ለማሳመር  አጃቢ የሆኑት ቮልሶች ራሳቸው በመካኒክ ታጅበው ነበር። በቮልስ የሚታጀብ ሰርግ ያለመካኒክ የማይታሰብ ነበር። (መካኒኮቹ መንገድ ላይ ለሚበላሽ መኪና ፈጣን ጥገና እያደረጉ ጉዞው ቀጠለ።)

ታዲያ ያኔ መናፈሻ ውስጥ የነበረ አሙቁልኝ አዝማሪ እንዲህ ብሎ ፈተለ፤

"ጉርምርሜ ና ጉርምርሜ
ያሆ በሌ፣ ያሆ በሌ ፣ ጉርምርምርምርም…
ባባው ቮልስዬ ፣
ያሆ ቮልስዬ፣ ያሆ ቮልስዬ… ጉርምርምርምርምርም… (ተቀብለን አስተጋባን)
አዝማሪው ቀጠለ፦

ሚስቱን  ያገኘው…
ያሆ በሌ…  ያሆ በሌ… ጉርምርምርምርምርም…
ጉርምርሜ በግሩ ሲያዘግም!"

(ይህኔ የምር አጉረመረምን)

ሰኞ 22 ፌብሩዋሪ 2016

ሠአት ሠሪው

(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)

ሠአት ሠሪው ደጃፍ ላይ ቆሜያለሁ። ከውጭ ሆኖ ለሚመለከት ሰው ምንም የሚማርክ ውበት ላትመለከት ይችላል። የደጁን መስታወት ታክኮ የቆመው መደርደሪያ ያገለገሉ ሰዓታት ማረፊያ ሁነዋል። የተበላሹ፣ የተጠገኑ፣ የማይጠገኑ፣ ያልተጠገኑ፣… ሠአቶች ተሞልቷል። እኔ እራሴ ሁሌ የማያቸው ሰዓቶች እዚህ ምን እንደሚሰሩ አይገባኝም። አሰሪዎቹ ቢወስዷቸውና ሰዓት ሠሪው ያገልግሎቱን ቢያገኝ መምረጤን ግን አልሸሽግህም። 

መስታወቱ ላይ ሶስት ጥቅሶች አሉ። በእጅ የተሞነጫጨሩና ለንባብ የማይማርኩ ቢሆኑም፣ ከማንበብ የሚያግተኝ ነገር የለምና በታላቅ መስህብ ስሜት ተውጬ ተጠግቼ አነበብኳቸው፦

የመጀመሪያው እንዲህ ይላል፦

" ተመልከት ፤ እኔ ማንን የምጠብቅ ይመስልሃል? ጊዜ ከሌለህ እዚህ ምድር ላይ ሌላ ምንም ነገር አትጠብቅ!"

በለው ብሶት!! ሁለተኛውን አነበብኩት። 

"ሳምንቱን ሙሉ ክፍት ነው፤ የዕረፍት ቀናትን ጨምሮ" ይላል ።

አባባሉ የቁጥር መጭበርበር ያለበት ቢመስለኝም የሰዓት ሠሪው ቤት እዚሁ መሆኑ ታስቦ የተፃፈ መሆኑንና ደንበኞች ይህን ሊገነዘቡ የተቀመጠ (የቤት ስራ) መሆኑንአምኜ ወደሶስተኛው ጥቅስ አመራሁ።

ሶስተኛው ግን ለራሴም ገራሚ ነበር ፦

"ልክ እንደ ሰዓት የሚበላሽና እንደ ሰዓት ጠጋኝ የሚሰራ ሰዓት የለም!"

እናም ፣ እንዲህ እያልኩ ወደውስጥ ገባሁ፦

"የዛሬው ጥሩ ይመስላል፤ መቼስ እስከዛሬ ከለጠፍኳቸው ይሻላል!"

እሑድ 21 ፌብሩዋሪ 2016

☆እግረ-መንገድ

(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)
‪‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬

የምሰማው ሁሉ አልጥምህ ብሎኛል፡፡ የሬዲዮኑን ጣቢያ እየቀያየርኩ የሚጥመኝ ፕሮግራም ፍለጋ ጀመርኩ፡፡ ዘፋኙ ሁሉ ዘማሪ ሆኗልና! . . . ሬዲዮኑን ዘጋሁትና ቲቪ ከፈትኩ፡፡

በቲቪ፣ የአንድ አዲስ ምርት አምራች ድርጅት ማስታወቂያ እየተላለፈ ነበር፡፡ አስተዋዋቂው፣ ድምፁን ከሌላ ሰው የተዋሰው ይመስላል፡፡ በግነት በተዋቀረ ድምጽ እንዲህ እያለ ነበር፡-

“ልብ ይበሉ! ምርታችን በአይቱ አዲስ እና አስተማማኝነቱ የተረጋገጠ ነው!!”

በለው ውሸት!

“አዲስ እና አስተማማኝ” ማለት ምን እንደሆነ የገባቸው አልመሰለኝም፡፡ አዲስ ከሆነ አስተማማኝነቱ ገና አልተረጋገጠም ፤ የተረጋገጠ ለመሆን ከዚህ ቀደም የሚታወቅ መሆን አለበት፡፡ ይህን እንኳን አያስቡም፡፡

ተጨማሪ ውሸት ሽሽት ቲቪውን ዘጋሁትና ከቤት ወጣሁ፡፡ ትንሽ በእግሬ ዞር ዞር ብዬ ብመለስ እንደሚሻል በማሰብ ነበር አወጣጤ፡፡

ማምሻ ግሮሰሪ የማውቀው አንድ ሰው ከሩቁ “እንኳን አደረሰህ!” ሲለኝ፡፡ “እንኳን!” አልኩት ከሩቁ፡፡

“እንኳን ምን? ” አለና መልሶ ጠየቀኝ፡፡

“እንኳን ብቻ!” ብዬ መንገዴን ቀጠልኩ፡፡

“አይ አንቺ ሰው ፤ በጊዜ አግለሻል መሰል...” ሲል ከጀርባ ይሰማኛል፡፡ ሰው ግን በዓል ሲመጣ ብቻ ነው እንዴ “መድረሴ” ትዝ የሚለው?

መንገዱ ጭር ብሏል፡፡ አንድ ሰው ብቻ ከሩቅ ይታየኛል፡፡ የሆነ ነገር እያወራ እንደሆነ ያስታውቃል፡፡ እየቀረብኩት ስሄድ ምን እያለ እንደሆነ ተሰማኝ፡፡
“የበግ ቆዳ ያለው? ” እያለ ነበር፡፡

አጠገቤ ሲደርስ ወደኔ እያየ ጮክ ብሎ ፤ ”የበግ ቆዳ ያለው!” አለ፡፡ ዝም ብዬው አለፍኩ፡፡ “ሰዉ ዛሬ ምን ነክቶታል?! ” ስል አሰብኩ፡፡ እውነት የበግ ቆዳ ቢኖረኝ መንገድ ለመንገድ ይዤው የምዞር መስሎት ይሆን?!

ሳላውቀው ብዙ ርቀት በእግሬ ተጓዝኩ፡፡ .... አምስት ሴቶች ከሩቅ ይታዩኛል፡፡ ታክሲ እየጠበቁ መሆን አለበት፡፡ እየቀረብኳቸው ስሄድ አለባበሳቸውን ለየሁት፡፡ አራቱ ሴቶች ነጭ የአገር ባሕል ልብስ ለብሰሰዋል፡፡ አንዷ ግን በጅንስ ተወጣጥራለች፡፡ ፀሐዩን ሽሽት በዣንጥላ አናቷን ከልላለች ፡፡ ተስፋ ቆርጣ መሆን አለበት ከመሃከላች ወጥታ በእግሯ መጓዝ ስትጀምር አየኋት፡፡

ነጭ የለበሱት አራቱ ካሉበት አልተንቀሳቀሱም፡፡ በአጠገባቸው ሳልፍ ከመሃከላቸው አንዷ፡- “ወንድም ፤ ሰዓት ይዘሃል? ” ስትል ተሰማኝ፡፡

“አዎ!” አልኳትና መንገዴን ቀጠልኩ፡፡ ልጅቱ ስንት ሰዓት እንደሆነ እንድነግራት እየጠበቀች ነበር መሰለኝ፡፡ ግን የጠቀየቀችኝ ሰዓት መያዜን ነው፡፡ እርሱንም “አዎ” ብያታለሁ፡፡

ዣንጥላ የያዘችው ሴት ከፊት ከፊቴ ስትሄድ አየሁ፡፡ የሚገርም ጀርባ አላት፡፡ እውነት የተፈጥሮ ከሆነ መቀመጫዋ ያምራል፡፡ (ሴቱ እንደ ውስጥ ሱሪ የሚጠለቅ አርቴፊሻል መቀመጫ መጠቀም ጀምረዋል አሉ! ) ይሁን ፡፡ መጠቀማቸው ክፋት የለውም፡፡ የሚቆረቁር ወንበር ላይ ሲቀመጡ እንዳይቆረቁራቸው ከሆነ መልካም ነው፡፡ (ምቾት በሌለው ወንበር ላይ ረጅም ሰዓታት ለሚቀመጡ ወንዶችም ይህ ዘዴ ይጠቅማል መሰል፡፡ )

ሰውነቷ ያምራል፡፡ ዕድሜዋን ለመገመት ሞከርኩ፡፡ በጥቂት ዓመታት ብትበልጠኝ ነው፡፡ “ታላቄ” እንደሆነች ሳስብ አንድ አባባል ትዝ አለኝ፡፡ “ከእያንዳንዷ ታላቅ ሴት ጀርባ መቀመጫዋን የሚያይ ወንድ አይጠፋም!” ሆሆሆ . . . ለጀመሪያ ጊዜ ፈገግ አልኩ፡፡
‪‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬
“ልመለስ!? ወይስ መንገዴን ልቀጥል!?” . . . ስል አመነታሁ፡፡ ሉፒዶ (ሽፍደት) ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ ይህ ተፈጥሮ ግን መገለጫው ብዙ ነው፡፡ እያንዳንዱ ሰው እንደየምልከታው ግንዛቤ የሽፍደት አካል መረጣውም ይለያል፡፡

የሰውነት አካላት ሁሉ የዚህ ምልከታ ውጤት ናቸው፡፡ በርግጥ መቀመጫዋ የሚያምር ሴት አይቶ “አሪፍ መቀመጫ አላት” ያለ ሁሉ ይህቺን ሴት ተመኛቷታል ማለት አይደለም፡፡ ማድነቅም ሌላው ተፈጥሮ ነውና፡፡ ከፊቴ ያለችውም ሴት ለእኔ እንደዚሁ ናት፡፡ ያየሁትን ማራኪ ሰውነት አለማድነቅ እንደማልችለው ሁሉ፣ ያደነቅኩትን ማራኪ ሰውነት ሁሉም አልመኝም፡፡ ይህም ተፈጥሮአዊ ነው!

ጥቂት መንገድ የመግፋት ሃሳብ አጋደለና መጓዜን ቀጠልኩ፡፡ ከፊቴ ግን ታላቅ ውሳኔ የሚሻ ነገር እየተውረገረገ ነው፡፡ ከቤቴ የወጣሁት ዳሌ ለመከተል አልነበረም፡፡ አሁን ግን ባጋጣሚ ዳሌ ተከታይ ከመሆንም አልፌ አድናቆት ገላጭ አባባል ቀማሪም እየሆንኩ ነው፡፡ ʿይህን ታላቅ ዳሌ እስከምን ድረስ ነው የምከተለው?! ከዚህ በላይ ከመከተል፣ ዳሌዋን ስካን ማድረግ ይቀላል፡፡ʾ ስል አሰብኩ፡፡

በነገራችን ላይ ፤ ከኋላ መሆን መከተል ነው ያለው ማነው?! (ከእረኛን ተመልከቱ፡፡ ከብቶቹን የሚያግደው ከፊት ከፊታቸው እየሄደ አይደለም፡፡ በጉዞ ላይ ያሉ ከብቶች ካያችሁ ፣ ከኋላቸው እረኛ መኖሩን አትዘንጉ) በዚህ ምሳሌ ብቻ ተገፋፍቼ ለዚህ ታላቅ ዳሌ እረኛ የሆንኩት እንዳይመስልብኝ ስል ርምጃዬን አፍጥኜ አለፍኳት፡፡ አሁን ተራው የርሷ ነው፡፡

ሴቶች ግን . . . ወንድን ከጀርባው ሲመለከቱት ምኑን ይሆን ቀድመው የሚያት?! (ዋሌቱ እንደማይሆን ግን ርግጠኛ ነኝ፡፡)

አልፌያት ጥቂት እንደተራመድኩ ፡- “ይቅርታ፣ አንድ ጥያቄ ልጠይቅህ እችላለሁ?” የሚል ድምጽ ሰማሁ፡፡ እኔን እንደሆነ ርግጠኛ ሆኜ ፊቴን አዞርኩና ልናገር ስል አንድ ነገር አገደኝ፡፡ ዳሌ ዳሌዋን ሳይ ያላየሁት ሌላ ሰው የስልክ እንጨት ፖል ተደግፎ ቆሞ ነበር ለካ፡፡ እሱን ነበር የጠየቀችው፡፡ እምም . . . ተረፈች፡፡ እንኳንም እኔን አልጠየቀች!

በጣም ከሚያናድዱኝ ጥያቄዎች አንዱ ይህ ነው፡፡ “አንድ ጥያቄ ልጠይቅህ?” ብሎ መጠየቅ በራሱ አንድ ጥያቄ ነው፡፡ እንዲህ ብለው የሚጀምሩ ሰዎች ሌላም ችግር አለባቸው፡፡ ያስፈቀዱት አንድ ጥያቄ ለመጠየቅ ሆኖ ሳለ መልሱን ተከትለው ተከታታይ ጥያቄ ማዥጎድጎዳቸው ነው፡፡

የመጀመሪያውን ፈገግታ የፈጠረው ስሜት በምን ፍጥነት ጥሎኝ እንደጠፋ እንጃ፡፡ ብሽቅ!

መቼስ በበዓል ቀን ታክሲ ከመጠበቅ ታክሲ መሸከም ይቀላል፡፡አውቶቢስ ፊርማታ ሳገኛ ቆምኩ፡፡ በእግሬ የመጣሁትን መንገድ በእግሬ የመመለስ አቅም አልነበረኝም፡፡ ታክሲ ቢጠፋ እንኳን ባስ እንደማላጣ ርግጠኛ ነበርኩ፡፡

(ሞራል)፡-
ጥቂት ሰዎች የባሷን መምጫ በጉጉት ይጠብቃሉ፡፡ እኔም እነርሱ ወደሚያዩበት አቅጣጫ አፍጥጫለሁ፡፡ አልፌያት የመጣኋት ቆንጂዛ አልፋኝ ከሄደች ቆይታለች ፡፡ (ማሳለፍ ትልቅ ችሎታ ነው፡፡ ማለፍም፡፡) አለማለፍ ግን ደካማነት፡፡ አለማድነቅ ስሜትን ለሌላው አለማሳወቅ ነው፡፡ ለራስ የተሰማን የአድናቆት ስሜት መሸሸግም ያው አልሸሹም ዞር አሉ ነገር፡፡ የአድናቆት ስሜትን ለሌላው ለማሳወቅ ሲባል ግን እንደኔው ሁሉ ተረጋግተው የሚጓዙትን ሰዎች መልከፍ ግን በነፃው መንገድ ላይ ነፃነትን ከመንፈግ አይተናነስም!!

አድናቆት በሰፊ ቦታ ጠባብነትን ማግዘፍ ሳይሆን ሌላ ስፋትን መጨመር ነው ብዬ አምናለሁና፡፡ ስለዚህም በማለፍ አምናለሁ፡፡ በማሳለፈፍም፡፡

ማሳሰቢያ፡- የእግረ መንገድ ወግ እንደ መዋቅር የተጠቀምኩበት መንገድ፣ ቅርፅ እንጂ እውነተኛ ገጠመኝ አይደለም፡፡ ምልከታን የመግለጫ አንድ መንገድ እንጂ፡፡

ማንደፍሮሽ

(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)

እውነተኛ ስሟ "ማንደፍሮሽ" ነው። እኔና መሰል አብሯ አደግ ጓደኞቼ ግን ፣ በቁልምጫ "ማኔ" እያልን እንጠራታለን። የመንደራችን ሴት ልጆች እንኳን በአካል አይተዋት ይቅርና፣ ገና ስሟ ሲጠራ በፍርሃት ይርዳሉ። ምግብ አልበላም ብለው ሲያስቸግሩ "ማኔን እንዳልጠራት!" ማለት በቂ ነው። ታዲያ እኩዮቿ ብቻ ሳይሆን ታናናሽ ወንድሞቻችንም ቢሆኑ የ"ማኔ" ስም ከተጠራ፣ የቀረበላቸውን ምግብ ጥርግ አድርገው እየበሉ አድገዋል።

ታዲያ ዛሬ ድረስ የሚገርመኝ ነገር ቢኖር የማኔ እንዲህ የመፈራት መንስኤ ነበር። በርግጥ ከወንድ ጋር የሚያመሳስላት ምንም አካላዊ መለያ የላትም። በእነዚህ ሁሉ የጓደኝነት ዓመታት፣ እንደወንድ  ለመምሰልም ምንም አይነት ጥረት ስታደርግ ማየቴንም እጠራጠራለሁ።

ልጅ እያለን ኩሽና ውስጥ እቃቃ ስንጫወት የሆነው ሁሉ አይረሳኝም። "አንቺ ሴት ነሽ፤ ለምን ከመሰሎችሽ ጋር አትጫወቺም" ብለን ጠይቀናት ነበር። መልሷ ግን የከፋ ነበር። በሁለት እጆቿ ያፈሰችውን አመድ ዐይናችን ውስጥ ሞጅራ ሮጠች። ከዛኔ ጀምሮ ነው መሰል፣ ይኸው አድገን እንኳን አንጠይቃትም።

በሌላ ጊዜ ደግሞ፣ ወንድነታችንን ተጠቅመን የበላይነታችንን እንድታምን ለማድረግ በጉልበት ልናስገብራት ሞክረን ነበር። በትግል እንደምንጥላት ተማምነን ብቻ ለብቻ ድብድብ እንድትገጥመን ጠራናት ። ብቻ፣ እንኳን እኔ አቡቹን አልሆንኩ። በመላተም ብዛት ጠንካራ የሆነ የሚመስለው አቡቹ  ጉድ አደረገን!!! ተዝረክርኮ አዝረከረከን። በወቅቱ፣ የመጀመሪያው ተጋጣሚ አቡቹ ነበር። (እንኳን እኔ አልነበርኩ።) ለትግል እንዲመቸው እግሩን አንፈራጦ በመቆም ዝግጅት ላይ ሳለ ድንገት ከማኔ የተሰነዘረው ርግጫ ብልቱ ላይ አረፈና ለሳምንታት የአልጋ ቁራኛ ሆነ። ከዛ ቀድሞ ግን እኛ የበላይነቱን ሚና ያለምንም ማቅማማት ለማኔ አስረከብን። ምክንያቱም ማኔ፣ በቅፅበታዊ ምት እና የት ቦታ ላይ መማታት እንዳለባት ተክናለችና።

ከወንዶች ጋር መሆን ትመርጣለች። (በተለይ ከኔ ጋር) ።

ማኔ ወንድ አይደለችም። ወንድም እንዳልሆነች እናውቃለን። "እኔ ሰው ነኝ!" ያለችን ቀን ምን ማለቷ እንደሆን ባይገባንም፣ ያለምንም ማቅማማት "ነሽ!" ብለናታል። ምስኪን አቡቹ! ገና ከማገገሙ፣ አላራምድ ያለውን የታፋ ስር ንፍፊት ተቋቁሞ እንደተነሳ፣ "እኔ ሰው ነኝ!" ስትል፤ "አዎ ነው!" ማለቱ ሳይቀር ትዝ ይለኛል። (ሲያስቅ... የሰው ፆታው ምንድነው? )

ሴትነቷን እየፈራን እንድናስታውስ የሚያደርገን አስገዳጅ ሁኔታ የሚፈጠረው ከስንት አንዴ ነው። እስከዛሬ፣ "ሴቷ ወንድማችን" ብሎ የጠራት አንድ ሰው ብቻ ነው። እሱም "ፎርጃ" ይሰኛል። (ቅፅል ስሙ ነው፤ የትምህርት ቤት ስሙ ረጅም ነው። ቃል በቃል ባላስታውሰውም፣ 'ፈርቼ ማለድኩት እሱን ሰጠኝ ለኔ ጃንደረባው…') አይነት ነገር ይመስለኛል። ፎርጃ፣ የቅፅበታዊ ጥቃቷ ሰለባ ነበር። እስካሁንም ነው። (ዛሬ አቡቹ አግብቶ ወልዷል) ። በርግጥ የልጁ አባት እርሱ እንደሆነ ያመንው በግድ ነው። (ያሉትን ነው ያልኩት)

ከዚህ ቀደም፣ (ወንዱ እህታችን) ያለው ፎርጃ ግን በሃኪም መውለድ እንደማይችል እንደተነገረው ካወቅን በኋላ የሁላችንም ጥያቄ ይህ ነው… 'እውን አቡቹ መውለድ የቻለው እንደኛው ሁሉ እሱም በሆነውና በሚሆነው ስላመነ ነው?! ወይስ… እንደ ፎርጃ ፣ ሃኪም ስላላየው?!"

ማኔ በሁሉም የልጅነት ጨዋታዎቻችን ውስጥ የመረጠችውን የመሆን ስልጣኗ ዛሬ ላይ ቆም ብዬ ሳስበው ይደንቀኛል። "ባል እና ሚስት" ስንጫወት እሷ የምታገባው እኔን ብቻ ነበር። እሷ ባል ስትሆን፣ እኔ ደግሞ ሚስቷ እሆናለሁ፡፡ የባልና ሚስት የጨዋታው ስርዓት በርሷ የበላይነት ተጀምሮ ያበቃል፡፡ እንደ ሚስትነቴ ምግብ የማዘጋጀት፣ ልጆችን የማጠብ፣ ቤቱን የማፀዳዳት …. ተግባራትን እከውናለሁ፡፡

ልጆቻችን ሆነው የሚጫወቱት አቡቹ እና ፎርጃ ናቸው፡፡ (እስካሁን ድረስ ማን እንዳረገዘ፣ ማን እንዳስረገዘ ባይገባኝም)፡፡ ፎርጃ እንደሴት ልጅ እንዲጫወት የምታደርገው ፎርጃን ነው፡፡ አቡቹ ደግሞ ወንዱ ልጃችን እንዲሆን ሚና ይሰጣቸዋል፡፡ ታዲያ በማኔ የሚታዘዘው አቡቹ ነው፡፡ ማኔ ትእዛዝ በመዛኙ ተመሳሳይ ናቸው፡፡ አቡቹን ጠርታ የባህርዛፍ ፍሬ (ሳንቲም መሆኑ ነው) ቆጥራ እየሰጠችው፡-

"አቡቹዬ፣ ከቃሲም ሱቅ የአስር ሳንቲም ስኳርና የስሙኒ ቡና ግዛልኝ" ትለዋለች፡፡

"እሺ፣ እማዬ" ካለ አለቀለት፡፡ የማኔ ቅፅበታዊ ምት ጭንቅላቱ ላይ ይዘንብበታል፡፡ በኩርኩም  ገጭ! ገጭ!  ገጭ! ... "እሺ አባዬ፣ ረስቼው ነው አባዬ! ይቅርታ አባዬ!" እስኪል ድረስ ኩርኮማዋን አታቆምም፡፡ አቡቹ ጥሎበት ድንገተኛ ኩርኩም ሲቀምስ ምድር ዓለሙ ስለሚዞርበት "አትምቺኝ..." ብሎ ማለቃቀስ ይመርጣል፡፡ እንዲህ ሲሆን የእናትነት ሚናዬን ተጠቅሜ ያስቀጣውን ጥፋት ልነግረው እሞክራለሁ፡፡ "አቡቹ፣ አባትህን እንዴት እማዬ ትላለህ..." ይህኔ "አባዬውን" ያዥጎደጉደዋል፡፡

ማኔ አባትነቷን አስከብራ ስታበቃ፣ "በል ፣ ሁለተኛ እንዳይለምድህ! አሁን ከቃሲም ሱቅ ግዛልኝ ያልኩህን በቶሎ ገዝተህ ና!" ካለችው በኋላ እንደ ሴት ልጅ ሆኖ ወደሚጫወተው ፎርጃ በመዞር እንዲህ ትላለች፡-
"ወንድምሽ እንዳይፈራ አብረሽው ሁኚ..."

ሁሌም ለሚስትነት እኔን እንደምትመርጥ አይገባኝም ነበር። በኋላ እንደገባኝ ከሆነ፣ አቡቹና ፎርጃ ለርሷ "ገና ልጆች" ናቸው፤ (ሚስት ለመሆን ገና አላደጉም)፡፡

በሌላ ጊዜ አንድ ጊዜ እንዲህ ሆነ፡፡ የሆነ ጊዜ ግን እየፈራሁ፡- "ዛሬም ሚስት የምሆነው እኔ ነኝ?" ብዬ ጠየኳት፡፡

"እና መጀመሪያ ሚስቴ እንድትሆን ስመርጥህ እስከመጨረሻው ድረስ ባልህ እንደሆንኩ አታውቅም?!" ብላ ተቆጣች፡፡ አ-ቤ-ት ቁጣዋ! አንድ ጊዜ የምታሳየው የቁጣ ገፅታ፣ ሶስት ሆነን አንሸከመውም፡፡ "እሺ" አልኩ፡፡ ምክንያቱም፣ በዚያ የልጅነት ዕድሜ የተቀረፀብኝ የ"እምቢታ" ትርጓሜው ግልፅ ነበር፡፡ "እንቢ" ማለት... በባሎች ዘንድ እንደጥፋት ተቆጥሮ በ"ሚስቶች" ላይ ለሚያደርጉት ያልታሰበ "ቅጣት" ምክንያት ይመስለኝ ነበር፡፡ (በዚህ ዘመን "ቅጣት" የሚለው ቃል "ጥቃት" በሚል ተቀይሯል፡፡)

የሚስትነት ሚናን ይዤ ስተውን፣ ትዕዛዝ መፈፀም የኔ ግዴታ ሲሆን ማዘዝ እና ማሽቆጥቆጥ ደግሞ የማኔ ስልጣን ነበር፡፡ ታዲያ በጨዋታ መሃል "ጎመን ገዝተህ ና፤ ደግሞ እነዛ መንገድ ዳር የሚቆሙ ሴቶች ካስቸገሩህ ፊት አትስጣቸው!" ብላ ታዘኛለች፡፡

የመንገድ ዳር ተሰብስበው የሚቆሙ የመንደራችን ወንዶች፣ ሴቶች ባለፉ ባገደሙ ቁጥር በነገር መተንኮስ (መላከፍ) ዋንኛው የአራድነት መገለጫቱ  ዛሬም ድረስ ቢቀጥልም፣ በማኔ ዘንድ ግን የተገላቢጦሽ ነው፡፡ ምንም ጨዋታው እቃቃ ቢሆንም፣ ምንም ጨዋታው ባልና ሚስት ቢሆንም… የዓለም ነባራዊ አካሄድ በማኔ ፊውራሪነት ተለውጧል፡፡ በተላካፊ  ሴቶች መግቢያ እና መውጫ አጥተው የተማረሩ ወንዶች እንደ አንዱ ሆኜ "ሴቶች እንዳይተናኮሉኝ" እየተጠነቀቀኩ የታዘዝኩትን ለመፈፀም መተወኔና ማሰብ በራሱ ለማኔ ያለኝ አድናቆት ይበልጥ ይንራል፡፡

የማኔ ባል መሆን እየተመኘሁ፣ ሚስቷ መሆኔን ያመንኩበትን ዓለም ምን እንሚመስል በምናቤ ለመሳል ሞከርኩ፡፡ "ማጅራት መቺ አለ፤ በጊዜ ልግባ…" ሲባል መስማት የተለመደ ነው፡፡ ዛሬም ድረስ ሴት ማጅራት መቺ አላውቅም፡፡ ሰው መጅራት መቺንም ሆነ ዘራፊን ሽሽት በጊዜ ቤቱ ለመግባት ከተጣደፈ፣ ከወንዶች ከሚሰነዘር አደጋ እራሱን ላለማጋለጥ ለመሆኑ ርግጥ ነው፡፡ እናም ወንዶች ለሁለቱም ፆታዎች የስጋት ምንጭ ናቸው፡፡

ከማኔ ጋር ከተዋወቅንበት ሶስት አስርት አመታት ተቆጠሩ። ያለጥርጥር ከ15 ዓመታት በኋላ ነው ያገኘኋት። አድራሻችንን አፈላልጋ እዚህ እንድንገናኝ በስልክ የቀጠረችን ራሷ ማኔ ናት፡፡ አቡቹና ፎርጃ እስኪመጡ እየጠበቅን ነው፡፡ ስለርሷ ያለኝ ግንዛቤ ባይለወጥም፣ አስተያየቴ ግን ተለውጦ ነበር። እንዴት አባቷ አምሮባታል?!? የሌለ ውስዋስ ለኳሽ ሆና ታየችኝ። የተሰማኝን ስሜት ግን ለመናገር አቅም አልነበረኝም። ምክንያቱም ፣ ማን እንደሆነች እድሜ ዘመኔን ሙሉ እንዳልረሳ አድርጋ ነግራኛለች።

ያቀራረበን እድሜ አራርቆናል፡፡ መልሶም አገናኝቶናል፡፡  እድሜ  የለወጠው ብዙ ነው፡፡ እቃቃ መጫወቻዎቻችን ተበትነዋል፡፡ በልጅነት የተጀመረው የባልና የሚስት ጨዋታ ይቀጥል አይቀጥል አይታወቅም…

ረቡዕ 17 ፌብሩዋሪ 2016

"እሾህን በሾህ"

✧(ኄኖክ ስጦታው)
(የአጭር አጭር አጭር ልቦለድ)

ለእራት የሚሆን ነገር ለመግዛት ወደ ሱቅ አመራ። እንደ ሁልጊዜውም፣ ጎረቤቱ የአይጥ መርዝ እየገዛ ነበር። ከጎረቤቱ ቤት መርዝ በልተው እሱ ቤት ኮርኒስ ውስጥ የሚሞቱ አይጦች ሽታ ረፍት ነስቶታል።
"ለምን በወጥመድ አታጠምዳቸውም?" አለና መፍትሄ ይሆናል ያለውን ሃሳብ አቀረበለት። ለጎረቤቱ።
"ሞክሬ ነበር። ወጥመድ ማለት የአይጥ ገበታ ነው። አይጦቹ ወጥመዱ ላይ ያለውን ምግብ በልተው ይሄዳሉ። ጠዋት ስነሳ ወጥመዱ የሚይዘው እኔኑ ነው።"
ዝም አለ።
አስቦ ፣ አስቦ… አንድ መፍትሄ አገኘ። እናም ጎረቤቱ ዞር እስኪል ጠብቆ፦
"የአይጥ መድሃኒት አለ?" ሲል ጠየቀ። ለባለሱቁ።
"የለም። መርዝ ነው ያለው"
"እሱንም ቢሆን ስጠኝ"

እሑድ 9 ኖቬምበር 2014

ዱባና ልጅነት

(ኄኖክ ስጦታው)

#ዱባ
ልጅ ሆኜ የሰማሁት ዘፈን አለ። ስለዱባ እንዲህ ብሎ ነበር፦

"ሳይበላ ሳይጠጣ ይወፍራል ዱባ
ልቤ ተንከባሎ አንቺ መንደር ገባ "

ግጥሙን አድጌ ስረዳው ልብ እና የሚንከባለል ዱባ  ያገናኛቸው ቤት መምቻቸው "ባ" እንደሆነ ገባኝ። ዱባ ወጥ አልወድም።  የዘፈኑ ተፅእኖ ነው መሰል፣ ቤታችን ዱባ ወጥ ሲሰራ ገንዘብ የወጣበት አይመስለኝም ነበር ። ተንከባሎ ቤታችን የገባ ነበር የሚመስለኝ።

በልጅነት ዘመን የማልረሳው አንድ ገጠመኝ አለ። የእርሻ አስተማሪያችን ስለ አዝእርት ሲያስተምሩ እንዲህ ብለው ጠይቀው ነበረ፦

"ከጥራጥሬ ውስጥ የሚመደቡት ምን ምን ናቸው?"

ምድረ ተሜ ተራ በተራ እየተነሱ "ጓያ፣ ሽንብራ፣ ባቄላ…" እያሉ መለሱ። መምህሩ ወደኔ እያዩ፣ "ኄኖክ ፣ የምትጨምረው አለ?" ሲሉኝ ፣ ከመቀመጫዬ ተነስቼ "ዱባ" አልኩና ተቀመጥኩ። የተማሪው ሳቅ እና ያስተማሪው ድንጋጤ ተደምሮ፣ በስክሪብቶ ጫፍ ቂጡን እንደተወጋ ተማሪ አስፈንጥሮ አቆመኝ። (ድሮ ተንኮለኛ ተማሪ አጠገቡ የሚቀመጥ ተሜን ብድግ ሲል ያለቀ ስክሮብቶ አሹሎ እስኪቀመጥ ይጠብቅ ነበር። ያሁኑን ባላውቅም።)

መምህሩ በግርምት አፍጥጠው ፣ አፍጥጠው፣ አፍጥጠው… አይተውኝ ሲያበቁ፣ ባፍንጫቸው የንፋስ ሳቅ ("ህምፍ" አይነት) አሰምተው ዱባ ያልኩበትን ምክንያት ጠየቁኝ። ክፍሉ ረጭ አለ ። እንዲህ ረጭ ያለ ዝምታ ለመጨረሻ ጊዜ ያስተዋልኩት ያኔ ነበር።

ዱባ የጥራጥሬ ዝርያ ለመሆኑ የሰጠሁት አጭር ማብራሪያ፦

"የዱባ ፍሬዎች ፀሐይ ላይ ተሰጥተው ሲደርቁ፣ ተቆልተው ይበላሉ። ልክ እንደ ሽምብራና ባቄላ ማለት ነው።" ከማለቴ ክፍሉ በሳቅ ተናወጠ።

ምን  የሚሳቅ ነገር አግኝተው እንደሆነ ለማወቅ አይኖቼን በክፍል ጓደኞቼ ዙሪያ አንከራተትኩ። ሳያቸው ነው መሰል ይበልጥ መሳቅ ቀጠሉ። ከሁሉ ከሁሉ የገረመኝ፣ የመምህሩም አብሮ መሳቅ ነበር። መቆም እንዲህ ያስቃል?

መቀመጥ ሳይሻል አይቀርም።
ተቀመጥኩ።

ዓርብ 15 ኦገስት 2014

የጆገረረ ጆሮና ምናምን… (ኄኖክ ስጦታው)

ልጅቱ ቆንጆ ናት መሰለኝ። እንጃ…

ለሥራ የምመላለስበት ቢሮ ውስጥ ተቀምጫለሁ። ስልኬን አውጥቼ ማስታወሻውን ከፈትኩ። (ይህ ማስታወሻ ወሳኝ ግብዓቴ ነው። የዳየሪዬ ዋናው አካል ከዚህ ይጨለፋል። እና ከዚህ ቢሮ እስክወጣ ድረስ ለምን አልቆዝምበትም?

ጸሐፊዋ፤
ጉዳዬ እስኪፈፀምልኝ ድረስ ሰረቅ እያደረኩ ተመለከትኳት። ከንፈሯን ደማቅ ቀይ ቀለም ቀብታዋለች። 【የሊፒስቲክ ጥቅም ከንፈር ከማለስለስና ከማስዋብ አገልግሎት ባሻገር ምንም ጉዳት አያስከትልም?!】የከንፈር ቀለም የውሽማ ሸሚዝ ላይ ከታተመ በቶሎ ታጥቦ የማይለቀው ቀለሙ ብቻ አይደለም። የሚያስከትለው መዘዝም እንጂ። (ለብዙ ቤተሰብ መበጥበጥ ምክንያት ሲሆን ያላሳየ የኢቲቪ ድራማ ይኖር ይሆን?!)

በድንገት ቀና ብላ "ተጫወት" አለችና ወደትየባዋ ተመለሰች። በዚህ ቅፅበት ምን ልጫወት? እቃቃ ልጫወት? ከማይገቡኝ ጨዋታዎች አንዱ ይህ ነው። "ተጫወት" ።

  (አንዷ ናት አሉ፤ ፈረንጅ ተጃልሳ ነው። የቋንቋ ነገር አላግባባ ሲላቸው ሁለቱም ዝምታን መርጠው ይቀመጣሉ። ዝምታው እንዴት ይሰበር?! በመጨረሻ እርሷ እንዲህ አለች አሉ፦ "Play" ) ተጫወት፤ ተጫወቺ፤ እንጫወት፤ ፕሌይ …

የጸሐፊዋ ዓይን ያምራል። ፀጉሯ ያምራል። ፊቷ የኦቫል ቅርፅ አለው። ለብቻዬ ፈገግ አልኩ።  የፊቷ ቅርፅ ከትላልቅ አይኖቿ ጋር ተዳምሮ ጥንታዊ የብራና ላይ ስእል አስመስሏታል።  【ያሰብኩትን ከፊቴ ላይ አንብባ ይሆን?!】ሰረቅ አድርጌ አየኋት። እሷ'ቴ፤ አንዳቀረቀረች ነው።

በምን ፍጥነት ከትየባ ወደ ጥፍር ሙረዳ አንደተሸጋገረች አላውቅም። ጣቷ ያምራል። ውበቱን ግን የጥፍሯ ርዝማኔ ያደበዘዘው ይመስላል።

"ተጫወት" እስክትለኝል ድረስ አፈጠጥኩባት። ይገርማል። ጥፍሯ ላይ ተመስጣለች።
ጥፍር! 
የጥፍር እድገት ፍጥነትና፣ የወንድ ልጅ ጡት ሁሌም ይገርሙኛል። ጥፍርስ ይደግ፣ ይመንደግ። ቢያንስ ለሴቶች የውበት ሳሎን ባለሙያዎች የገቢ ምንጭ መሆኑን እያየን ነው። (ኧረ የማይገባኝ ነገር ፤ "እጅና እግር እንሠራለን" የሚሉ ፀጉር ቤቶች  ከጥፍር የዘለለ አንዳች ጥበብ ላይ ደርሰው ይሆን?!) ። ከደረሱ ድንቅ ነው። ካልደረሱም እሰየሁ። እኔም ያልደረስኩበትን በነፃነት እንድናገር በር ከፍተዋል። ውሻ በቀደደው ጅብ እንደሚገባ ፈሪ አበዎች ከገለጹ ዘንዳ እነሆኝ በረከት ለክፉ… የወንድ ልጅ ጡት ጥቅም ምንድነው?! አጥብቶ ሊያሳድግበት… ወይስ ራሱ ጠብቶ ሊመነደግበት?!

ጸሐፊዋ፣
በዚህ ዓመት በሀቀኝነት ያየሁዋት ባትኖርም፣ ሰርቄ ካየኋቸው ሴቶች ውስጥ ግን  "የአንበሳውን ድርሻ" ትወስዳለች። አሁን ከጥፍር ሙረዳ ወደ ወደትየባዋ ተመልሳለች። ጸሐፊዋ።

ጆሮዋን!
ኧረ ጆሮ! በአንድ ጆሮዋ ላይ ብቻ ስንት የጉትቻ ማንጠልጠያ ብስ እንዳለ ልቆጥር ሞክሬ አቅም አጣሁ። እውነት ለመናገር ያልተበሳው የጆሮዋ አካል ቢኖር እርሱም ተበሥቷል።

የጆሮ ጥቅም አናሳ እንደሆነ የገባኝም ዛሬ ነው። (አንድ ግጥም ትዝ አለኝ። ያኔ የጋዜጠኝነት ትምህርት ስንማር የቃላት ፈጠራን አስመልክቶ አንዱ መምህር "ልጂቱ ፣ የዘመነቺቱ " የሚለውን የደበበ ሰይፉን ግጥም በምሳሌነት አጣቀሰና የራሳችሁን ግጥም በፈጠራ ቃል ተጠቅማችሁ ጻፉ ሲል አዘዘን። ጫማዋን ጨምታ፣ ሱሪዋን ሶርታ፣ ቦርሳዋን ቦርሳ፣… ቲሽ!  ሁሉንም አዲስ ቃላት ደበበ ሰይፉ አደብይቶታል። አንዷ ክላስ ሜታችን ግን ለምሳሌነት ያልቀረበ ምርጥ የቃላት ፈጠራ ይዛ ቀረበች፦

"ጆሮዬም ይጆርር፣ እጅ እግሬ ይጀግረር
ጆሬዬም ይደንቋ፣ ከደነቋ አይቀር…"

አለችና ተሜን በፈጠራዋ አስደምማ እርፍ!!"

መምህራችን ግን አልተዋጠለትም። ወይ ደበበ ፣ ደበበ ሸትቶት አልዋጥ ብሎት ይሆናል እንጃ፤ የተገጀረረውን የቃል ፈጠራ ገርጅጆት አለፈው። ቺኳ ገጣሚት ተቆጫበረች። እናም አለፈ። እንኳን አለፈ።

ዛሬ ያየሁት ጆሮ የተበሳ እንዳልሆነ ሳስበው ታወሰችኝ። በርግጥም ጆሮ ይደነቋል! ! እጅ እግርም ይጀገረራል!!

የቢሮዋ "ጸሐፊ" ተጫወት የምትለኝ መስሎኝ ቀና ብዬ አየዃት። ኤጭ። "ተጀግርራለች፣ አልያም ደንቁታለች…