2018 ማርች 2, ዓርብ

ዋ! አድዋ! (ኄኖክ ስጦታው)

ዋ! አድዋ! 

 “Many died…[and] no one knows their names…but their names are written in Heaven, in the book of life…for they became martyrs…” The Mannawe Manuscript 
“ብዙዎች ሞቱ ... [እና] አንዳችም ስማቸውን የሚያውቅ ሰው የለም ... ነገር ግን ስማቸው በመንግሥተ ሰማያት፣ በህይወት መዝገብ ላይ ተጽፏል ... ሰማዕታት ስለሆኑ ...” 
*

አንድ ወቅት ላይ የኢጣሊያ መንግስት ስልጡን ለሆነው ህዝቡ አንድ እቅድ አቀረበ። የእቅዱ ስያሜ “የኢጣሊያ ክቡር ተልዕኮ” ይሰኛል። “ክቡር ተልእኮ” ምንድነው?!
ኢጣሊያ፣ የውስጥና የውጭ ችግሮቿን ለመፍታት ከነደፈቻቸው እቅዶች አንዱ በአፍሪካ ውስጥ ያላትን የቅኝ ግዛት ማስፋፋት ነበር። በ1860ዎቹ(እኤአ) ውስጥ በኢኮኖሚ መዋዠቅ ውስጥ ለተዘፈቀችው ኢጣልያ “ክቡር ተልእኮ” ታቀደ። የገጠር ነዋሪዎች እና በድህነት ውስጥ ያሉ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢጣልያውያን የተሻለ ሕይወት ለመፈለግ ሀገራቸው መሰደዳቸውን ለማስቀረት የኢጣሊያ ንጉሥ የሆኑት ንጉሥ ኡንቤርቶ በአፍሪካ የሚካሄደው ቅኝ አገዛዝን ይበልጥ ማስፋፋት ሁነኛ መፍትሄ ይሆን ዘንድ ተለሙ፤ እቅዳቸውም ከአገር ከመሰደድ ይልቅ ለአገር መሰደድ ላይ ያተኮረ ነበር። ስያሜውንም “የኢጣሊያ ክቡር ተልዕኮ” በሚል ገለፁት። ድህነት፣ ሥራ አጥነትና የውጪ አገራት ጣልቃ ገብነት ጫናን ለማስወገድ መፍትሄ ለመስጠት የቅኝ ተገዥ አገራትን በአፍሪካ ማስፋፋት እንደ ታላቅ መሳሪያ ተደርጎም የወረራው አቅጣጫ ኢትዮጵያ ላይ አተኮረ።” (A Plebano, Storia dela Fianza Italiana III, Turin, 1902)
የጦርነቱ መንስኤ

ሚያዚያ 1881 ዓ.ም. ንጉሥ ምኒልክና እቴጌ ጣይቱ ውጫሌ በሚባለው ቦታ ሳሉ የኢጣልያ ልኡክ የሆነው አንቶኔሊ፣ ንጉሥ ምኒልክን ለማግኘት ውጫሌ ድረስ በማምራት በኢጣሊያኖች የተረቀቀውን ውል አቀረበ። የውጫሌ ውል ሃያ አንቀጽ ያለውን ሲሆን በኢጣሊያ በኩል በንጉሥ ኡምቤርቶ ተወካይነት አንቶኔሊ ሲፈርም፣ በኢትዮጵያ በኩል ደግሞ በዳግማዊ ምኒልክ ተፈረመ። ስያሜውም “የውጫሌ ውል” ተባለ። 
ከዚህ ውል ውስጥ 17ኛው አንቀጽ በአማርኛው፣  “የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ከአውሮጳ ነገሥታት ለሚፈልጉት ጉዳይ ሁሉ በኢጣሊያ መንግሥት አጋዥነት መላላክ ይቻላቸዋል” ሲል፣ በኢጣሊያኛው ደግሞ “የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ከአውሮጳ መንግሥታት ለሚፈልጉት ግንኙነት በኢጣሊያ  መንግሥት አማካኝነት ማድረግ ይገባቸዋል” ይላል። ይህ አንቀጽ ውሎ አድሮ በሁለቱ ሀገሮች መካካል የአድዋ ጦርነት ተብሎ ለሚታወቀው ጦርነት መነሻ ምክንያት ሆኗል።
ውሉም እንደ ጸደቀ፣ “ኢትዮጵያ በኢጣሊያ ሥር ናት” የሚል ጽሑፍ በየጋዜጦቹ ላይ ታትሞ ወጣ። ይህንኑ መልዕክት የኢጣሊ ጠቅላይ ሚንስትር ክሪስፒ ጥቅምት አንድ ቀን 1882 ዓ.ም. ለአሜሪካና ለ12 አውሮጳ መንግሥታት አስታወቀ። በዚህ ሂደት ውስጥ ነበር ዳግማዊ ምኒልክ ሥርዓተ ንግሣቸውን ለማሳወቅ ደብዳቤ የጻፉላቸው መንግስታት፣ እንግሊዝና ጀርመን፣ ለአፄ ምኒልክ በጻፉት መልስ ላይ፣ በውጫሌ ውል መሠረት ግንኙነታችን በቀጥታ ሳይሆን በኢጣሊያን በኩል ብቻ ነው በሚል ያሳወቁት። ይህ ደግሞ አፄ ምኒልክን ይበልጥ አስቆጣ። የጣልያን አካሄድ የተለሳለሰ ቢመስልም ችግር ማስከተሉን የተመለከቱት አፄ ምኒልክ ጥር 19 ቀን 1882 ዓ.ም. ለኢጣልያው ንጉስ ኡምቤርቶ “ለአገሬ ውርደት እንደሆነ ደርሼበታለሁ…” የሚል መልእክት መላካቸውን “አፄ ምኒልክ እና የአድዋ ድል” የተሰኘው መፅሃፍ ይናገራል። 
*
አፄ ምኒልክ የውጫሌውን ውል በተዋዋሉ በአራተኛው ዓመት፣ ለአውሮጳ ኃያላን መንግሥታት የውጫሌን ውል ማፍረሳቸውን የካቲት 4 ቀን 1885 ዓ.ም. በደብዳቤ አስታወቁ። 
በህዳር 1886 ዓ.ም. የኢጣልያ ጠቅላይ ሚኒስትር የሆነው ክሪስፒ፣ አንቶኔሊን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጸሐፊ፣ ጄኔራል ባራቲየሪን ደግሞ አዲሱ የኤርትራ ገዢ አድርጎ ሾማቸው። ጄኔራል ባራቲየሪ በ1886 ዓ.ም. አጋማሽ ላይ ጦሩን እየመራ የኢትዮጵያን ግዛት ዘልቆ በመግባት የሰሜኑን ክፍል በኃይል መያዝ ጀመረ። 
ጄኔራል ባራቲየሪ በ1887 ዓ.ም. ለዕረፍት ወደ ሮም ሲመለስ በጣሊያን ፓርላማ ተገኝቶ ንግግር ከማድረጉ በፊት፣ አባላቱ ከመቀመጫቸው ተነሥተው የደመቀ ጭብጨባ በመስጠት ተቀብለውታል። ንጉሡ ኡምቤርቶም ድል አድራጊው ጄኔራል ባራቲየሪን በማድነቅ የጣልያን ኃይልን “የሠለጠኑ የበላይነት ኋላ–ቀር በሆኑ ላይ” በማለት አወድሰውታል። ጄኔራል ባራቲየሪም “በጥቅምት ወር ጦርነት ይኖራል። የእኛ የሠለጠነው አሥር ሺህ ጦር ከሃያ ሺህ እስከ ሰላሳ ሺህ የሚደርሰውን ያልሠለጠነ የኢትዮጵያ ጦር በቀላሉ ያሸንፈዋል፤ የኢትዮጵያውን ንጉሥ በቀፎ አድርጎ ሮም ያመጣዋል” ሲል በኩራት  ተናገረ። በቅኝ ግዛት መስፋፋት ምኞት ሕልም የሰከረው ፓርላማም ንግግሩን ከሰማ በኋላ የጄኔራሉ ዓላማ እንዲሳካለት ለአንድ ሺህ ተጨማሪ ወታደሮች መቅጠሪያ በጀት አፀደቀለት። ጄኔራል ባራቲየሪ በመስከረም 15 ቀን 1888 ዓ.ም. ተመልሶ ምፅዋ ገባ። በዘመኑ ከጣልያን የወገኑ ቅጥር ወታደሮችን ከአፍሪካ የመለመላቸው ሲሆን በቀን አንድ ሊሬ ከሽልንግ ይከፈላቸው እንደነበር  “The Battle of Adwa: African Victory in the Age of Empire” የተሰኘው መጽሐፍ ይነግረናል። 
ንጉሠ ነገሥት አፄ ምኒልክም የውጫሌውን ውል ሲያፈርሱ፣ ከኢጣሊያኖች ጋር ጦርነት የማይቀር መሆኑን አውቀውት ስለነበር፣ ወታደሮቻቸውን ማዘጋጀትና ዘመናዊ የጦር መሣሪያዎችን ከራሺያና ከፈረንሳይ በጅቡቲ በኩል ማስመጣት ቀጠሉ። በ1895 ዓ.ም. በአጠቃላይ ለዚህ ጦርነትዝግጅት አፄ ምኒልክ ከ70 -100 ሺህ የሚደርስ ዘመናዊ ጠብመንጃ እና 5 ሚሊዮን ጥይት መግዛት ችለው ነበር።
የክተት ዐዋጅ
የጦርነት አይቀሬነት ርግጥ ሲሆን ኢትዮጵያም ለፍልሚያ ተዘጋጀች። ዝነኛው የአፄ ምኒልክ የክተት አዋጅም ነጋሪት እየተጎሰመ ተለፈፈ።
“እግዚአብሄር በቸርነቱ እስካሁን ጠላት አጥፍቶ አገር አስፍቶ አኖረኝ፤ እኔም እስካሁን በእግዚአብሔር ቸርነት ገዛሁ፡፡ ከእንግዲህ ብሞትም ሞት የሁሉም ነውና ስለእኔ ሞት አላዝንም፡፡ ደግሞ እግዚአብሔር አሳፍሮኝ አያውቅም፤ ወደፊትም ያሳፍረኛል ብዬ አልጠራጠርም፡፡ አሁንም አገር የሚያጠፋ፤ ሃይማኖትን የሚለውጥ፣ በፊት እግዚአብሔር የወሰነልንን ባህር አልፎ መጥቷል፡፡ እኔም የአገሬን ከብት ማለቅ፤ የሰውን መድከም አይቼ እስካሁን ዝም ብለው ደግሞ እያለፈ እንደፍልፈል መሬት ይቆፍር ጀመር፡፡ አሁን ግን በእግዚአብሔር ረዳትነት አገሬን አሳልፌ አልሰጠውም፡፡ የአገሬ ሰው ከአሁን ቀደም የበደልሁህ አይመስለኝም፡፡ አንተም እስካሁን አላስቀየምኸኝም፡፡ ጉልበት ያለህ በጉልበትህ እርዳኝ። ጉልበት የሌለህ ለልጅህ፣ ለምሽትህ፣ ለሃይማኖትህ ስትል በሃዘንህ እርዳኝ፡፡ ወስልተህ የቀረህ ግን ኋላ ትጣላኛለህ፡፡ አልምርህም፡፡ ማርያምን ለዚህ አማላጅ የለኝም…”
(“አፄ ምኒልክና የኢትዮጵያ አንድነት” በተክለ ጻዲቅ መኩሪያ ገጽ 226)


የጦርነት ውሎ
ዘመቻው ጣይቱ ብጡል ከምኒልክ በላይ ግልተው የታዩበት ነበር። ጣይቱ ያስከተሉትን ጦር ይመሩ የነበሩት ባልቻ ከጦር መሪነታቸውም በተጨማሪ የምኒልክ ግምጃ ቤት ኃላፊ እና የዘውድ ጠባቂም ጭምር ነበሩ። ጣይቱ በሺህ የሚቆጠሩ ወታደሮች ብቻ ሳይሆን የሙዚቀኞች ቡድን ያቀፈ ስብስብ አካተው በሽለላና በፉከራ የታጀበ ቡድን ጭምር እንደነበር ታሪክ ይናገራል። 
ጦርነቱ የካቲት 23ቀን 1888 ዓ.ም. ማለዳ ተጀመረ። በወቅቱ ስለነበረው ሁኔታ “የተተከለው ድንኳን ሲታይ ከብዛቱ የተነሣ አፍሪቃ አውሮጳን ለመጠራረግ የተነሣች ይመስላል፡፡ የጦርነቱ ዕለት ኢትዮጵያውያኑ ደማቅ ቀለም ያለው ካባ ለብሰው፣ የነብርና ያንበሳ ቆዳ ለብሰው አዝማሪዎቹ እየዘፈኑ፣ ቄሶች፣ ልጆች፣ ሴቶች ሳይቀሩ ፀሐይዋ ፈንጠቅ ስትል በተራራው ላይ በታዩ ጊዜ የኢጣሊያን ጦር አሸበሩት፡፡”  ሲል ታሪክ ጸሃፊው በርክለይ ይገልፀዋል።
በጦርነቱ ላይ ከተሳተፉት የታሪክ ምስክሮች መካከል ፊታውራሪ ተክለ ሐዋርያት ተክለማሪያም አንዱ ሲሆኑ “ኦቶባዮግራፊ” በተሰኘው ማስታወሻቸው ላይ የጦርነቱን ውሎ እንዲህ ሲሉ ይተርኩልናል፦
“ጠመንጃ ሲንጣጣ ሰማን፤ መድፍ ወዲያው ያጓራ ጀመር። ተኩሱ እያደር እየባሰበት ተቃረብን። ዐረሮቹ ማፏጨት ጀመሩ። የቆሰሉ ሰዎች ተቀምጠው አገኘን።… ጦራችን ተደበላልቋል። ሰውና ሰው አይተዋወቅም።… ሴቶች በገንቦ ውሃ እያዘሉ፣ በበቅሎቻቸው እንደተቀመጡ፣ ለቁስለኞች ውሃ ያቀርባሉ። ሲነጋገሩ ሰማኋቸው። “ኧረ በጣይቱ ሞት” ይላሉ።… ነጋሪቱ ከግንባርም፣ ከጀርባም፣ ከቀኝም፣ ከግራኝ ይጎሸማል። የተማረኩ ጣልያኖች አየሁ። ወዲያው ምርኮኞቹ በዙ። አንዳንዶቹ ወታደሮች ሦስት ይበልጥም ጣልያኖች እየነዱ መጡ። በኋላ የምርኮኞች ብዛት ለዓይን የሚያሰለች ሆነ። ድል ማድረጋችንን አወቅሁት። ጣልያኖች መዋጋታቸውን ትተው ማርኩን እያሉ ይለምናሉ።” 
አክለውም፣ ጦርነቱ አልቆ እንኳን ወደግንባር የሚሄደው የሰው ብዛት እንደ ውሃ ሙላት እንደነበር ፊታውራሪ ተክለ ሐዋርያት ይገልፁታል። 

“The Battle of Adwa: African Victory in the Age of Empire” መጽሐፍ ስለጦርነቱ ሲገልፅ፦
“የጣልያን ሠራዊት በመገስገስ ላይ የነበሩትን የኦሮሞ ፈረሰኞች በተመለከተበት ወቅት የሚገባበት ጠፋው፡፡ ቀድሞ በሠራዊቱ ውስጥ ስለኦሮሞ ፈረሰኞች የተነገራቸው ኋላ ቀር እና ተራ ተዋጊዎች እንደሆኑ ነበር፡፡ በጦር ሜዳ ላይ የተመለከቱት ግን ፈረሰኞች እጅግ ፈጣን እና የተካኑ መሆናቸውን ነበር፡፡
“የጀ/ል አርሞንዲ የበታች ከኾኑት መካከል ጂዩቫኒ ቴዶኔ ለሠራዊታቸው መሸነፍ ቁልፉን ሚና የተጫወቱት የኦሮሞ ፈረሰኞች መሆናቸውን መስክሯል፡፡ የወቅቱን አስፈሪ ሁኔታ ሲገልፅም “ፈረሰኞቹ ወደ ሽለቆሁ ሲወርዱ በድንገት የገነፈለ ጥቁር ባህር ይመስሉ ነበር” ብሏል፡፡ በወቅቱ ሌ/ኮ አጎስቲኖ ቺጉ ፣ ሌ/ኮ ሎኔንዞ ከምፕያኖ ፣ ሌ/ኮ ጊሊዮ እንዲሁም በመጨረሻ ራሱ ጀነራል አሪሞንዲ አንድ በአንድ መግደላቸውን ጠቅሷል፡፡
“በርካታ የጦር መሪዎች ራሳቸውን አጥፍተዋል፡፡ ል/ኮ ጋሪባልዲ ቬናዞ እና ሌ/ኮ ማዞሌኒ የኦሮሞ ፈረሰኞችን ጦርና ጎራዴ በመፍራት በራሳቸው ሽጉጥ ራሳቸውን አጥፍተዋል፡፡ ቴዶኔ ሁኔታውን ሲገልፅ በተለይ ኮ/ል ፔናዚ መጀመሪያ የተኮሰው ጥይት ስላልገደለው ለኹለተኛ ጊዜ ደረቱን በራሱ ጥይት መምታቱን ገልጿል፡፡ ራሱ ታዶኔ ቆስሎ የተማረከ ሲሆን ጦርነቱም በዚያው ተጠናቋል፡፡” 
*
የአድዋ ጦርነት ድል አሸናፊ ይሆናል ተብሎ በተደመደመለት ኃያል መንግስት ተቃራኒ ሆነ። ድሉም በአሸናፊዎቹ ዘንድ ወራሪን መክቶ መመለስ ቢመስልም ውጤቱ ግን በሃያላን ሃገራት አስገድዶ ቅኝ የመግዛት ስርዓት እና ደካማ ሃገራትን ለመቀራመት በጉልበት የመግዛት ሂደት ውስጥ ለቅኝ ገዢዎችም ሆነ በቅኝ ተገዢነት ላሉት ሁሉ የማይታመንና አስደንጋጭ የዓለማችን ክስተት ለመሆን በቃ። “ጥቁር ሕዝቦች የባርነት ቀንበር ለመሸከምና ተገዢ ለመሆን የተፈጠሩ እንደሆኑ” ያምኑ የነበሩትንም ጭምር ቆም ብለው እንዲያስቡ ከማድረግም አልፎ ሽንፈታቸውን በግድ እየመረራቸው ለመመስከር አስገደደ። ይብስ ብሎም መጽሔቶች የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ዳግማዊ ሚኒሊክ የኢጣሊያን ንጉስ በጦር ሲወጉ የሚያሳይ የካርቱን ምስል አስደግፎ በመዘገብ አንድ ሃያል አገር “ኋላ ቀር “ እንደሆነ በሚታመን “ጥቁር ሕዝብ” መሸነፉን አወጀ። ይህኔ ነበር በግልጽ ለኢጣልያ ወግኖ የሚፅፈው የጆርጅ በርክሌይ ምስክርነት እንዲህ የቀል፦
“ከሰፊው የፖለቲካና የታሪክ ትንታኔ አኳያ የዐድዋ ጦርነት በአፍሪቃ ምድር አዲስ ኃይል መነሣቱን የሚያበስር ይመስላል። የዚህች አህጉር ተወላጆች፣ የማይናቅ ወታደራዊ ኃይል ሊሆኑ እንደሚችሉ ልናሰላስል ተገደናል።… ነገሩ አስቂኝ ቢመስልም፣ ይህ ሁኔታ (ማለትም ዐድዋ) ጨለማይቱ አህጉር በላይዋ ላይ ሥልጣኗን ባንሰራፋችው በአውሮጳ ላይ የምታደርገው አመፅ የመጀመሪያው ምእራፍ ነው…”
*
የታሪክ ተመራማሪው ባሕሩ ዘውዴ “የኢትዮጵያ ታሪክ” በተሰኘው ምርምራቸው ሥራቸው ላይ በገፅ 89 እንደገለፁት “ዐድዋ ልዩ ትኩረት ያሰጠው ጥቁሮች በነጮች ላይ የተጎናጸፉት የመጀመሪያው ዐቢይ ወታደራዊ ድል በመሆኑ ነው…።”
*

2018 ጃንዋሪ 18, ሐሙስ

ምስር ብሉ!

(ኄኖክ ስጦታው) 


ምስር ባህል ነው። ምስር እውቀት ነው። አኗኗራችን ከምስር ጋር ተቆራኝቷል። ባህላችን፣ ልምዶቻችን፣ የሥነምግባር ተግዳሮታቸረን፣ የመረጃና የእውቀት መለዋወጫ መንገዳችንም ጭምር ነው-ምስር። በሀዘንና ደስታችን ውስጥም አለ በሃዘን ቤት ምስር አለ። በለቅሶ ቤት ውስጥ ምስር አለ። ምስር የወጥ ግብኣት ብቻ አይደለም። የሃዘናችን ተካፋይና የደስታችንም ተጋሪ ጭምር እንጂ። 

አስደሳች ነገር ሲያጋጥመን “የምስራች!” እንላለን። “ምስር ብላ/ ብዪ)” አፀፋችን ነው።  በሃዘናችን ጊዜ ገበታ ነው። በሞት ለተለየን ሰው ሃዘን በተቀምጥን ጊዜም ለሃዘንተኞች የሚቀርብ የገበታ ስርዓታችን አካልም ሆኖ ዘመናት ተሻግሮ ዛሬ ላይ ደርሷል። 

ምስርን የነውራችን መሸፈኛና የጓዳ ውስጥ ገመናችን ቋንቋም ጭምር ነው። በአደባባይ ስንገልጠው ለማይገባቸው የተደበቀ፣ ለሚግባቡበት ግን የአደባባይ እውነታ ጭምር። ለሚያውቁት ብቻ የመግለጫ መግባቢያ መሳሪያችን ነው። በአዋቂዎች ዘንድ ሚስጥራዊ መግባቢያ በመሆንም ያገለግላል።

በአንዳንድ አካባቢዎች ባል “እራት ምንድነው?” ብሎ በየቀኑ ይጠይቃል። ምክንያቱ እራቱን ምን እንደሚበላ ማወቁ ላይ እንዳይመስላችሁ። “እራት ምስር ነው” ከተባለ፣ ምላሹ ሁለት ተቃራኒ ትርጓሜ ያላቸውን ንግግሮች አጣምሮ ይይዛል። አባወራው ቀኑን ሲማስን ደክሞት ከዋለና ቤቱ ገብቶ እራቱን በልቶ መተኛት ብቻ ከሆነ ፍላጎቱ መርዶ ነው። ከሚስቱ ጋር “እንትን” አምሮት ከሆነ ደግሞ የምስራች!
ምስር ብሉ

እኛ እኮ ቃለ-ጽዩፎች ነን። እንኳን ተገላልጠን ይቅርና ተከናንበን እንኳን ምግባራችን በተከናነቡ ቃላቶች ውስጥ የመገለጥ ክዋኔው ክብርን የሚያዋርድ ሳይሆን የሚያገዝፍ የሚሆንብን። በሃዘን ቤት ውስጥ ባል ያላቸው ሴቶች ይግባቡባቸዋል ተብለው ውስጥ ውስጡን በእድሜ ደርሰን ከታዘብነው ንቁሪያ መካከል አንዱ ይሄን ይመስላል፦

ሚስት ለአዘንተኛው ምስር ወጥ ጨላፊ ናት። ምራት ደግሞ እንጀራ አቅራቢ። እና ምራት በቅናት ርር ብላ ለሚስት “ከምስሩ በደንብ ጨልፊለት” ስትል በነገር ትወጋታለች። ሚስትም ቀላል ሰው አልነበረችምና፦
 ያንቺን እንጀራ በልቶ ሲጨርስ እጨልፍለታለሁ” አለች አሉ። 
እስቲ ምን እንደተባባሉ የገባው ሰው ስንት ይሆኝ?

ከተረታችን ውስጥ “እንትን” ምን እንደሆነ በማይታወቅበት ዘመን አንድ ምሳሌያዊ አባባል ተፈጥሮ ነበረ። የሚገርመው ነገር የዚህ “እንትን” ምንነት ዛሬም ድረስ ግልጥልጥ ብሎ አልታወቀም። ዘመን ገስግሶ፣ መግባባት በዕድሜና በአቻ መሆኑ በቀረበት የሳይበር ዘመን ላይ ደረስንና በተግባር ሊመለሱልን ለሚገቡ ጥያቄዎች ጉግል በማሰስ ብቻ ተቆነፃፅለን ስናበቃ “እሱን ትደርስበታለህ” ስንባል፣ “እሱን ስትገረፍ ታወራዋለህ” በማለት እድገትና መድረስ በማይፈታው መደነቋቆር ዘመን ውስጥ ከታላላቆቻችንና ከታናናሾቻችን እኩል ቁመት ይዘን ሳንግባባ መኖር ከጀመርን ሁለት አስርታት እየተቆጠሩም አይደል? ታዲያ ለዚህ መፍትሄው መንድነው?

ምስር ነዋ! ምስር ሃይል ነው! ምስር ብርታት ነው! ምስር አስተምህሮት የሚጠናበት አንዳች መላ መቀየሻ መንገድ ነው! ምስር አብሮነት ነው! ምስር ከላይ እንደተገለፀው “እንትን” ቀስር ነው! “እንትን” ማለት ግን ምንድን ነው? ብለን ብንጠይቅ ሁሉም ሰው በአንድ ድምፅ “እንትን ነዋ!” የሚል አይጠፋም። እንትን ግን ምስጢር ነው። በዘመናችን “እንትን” የሚለው ቃል ሳይወድ በግድ ትርጉም አልባ ቃል መሆኑ ቀርቶ ውስን ትርጓሜን ብቻ እንዲይዝ የተገደደ የግፍ እስረኛ ቃል ሆኗል! #እንትን_ይፈታ! 
  

አንድ ጥንታዊ ተረት አለ። የገበሬዎች የእርሻ ማሳ ላይ የዘሩትን አተር በድብቅ እየገባች የምትበላ አንዲት ጦጣ ነበረች። በዚህ ድርጊቷ የተማረሩ ገበሬዎች ተመካክረው አንድ ውሳኔ ላይ ደረሱ። “ማሳችን በጦጣ እየተደፈረ፣ ያሸተው ፍሬም እየተበላሸ ምርታችን ቀነሰ። ድካማችን መና ቀረ። ምን እናድርግ?” ሲሉም ተመካከሩ። “ምስር ዘርተን ለምን አንገላገልም?” ሲሉ አንድ አዋቂ አባት መፍትሄ አመላካቱ። እናም ሁሉም ተስማምተው በአተር ፋንታ ምስር ዘሩ። ታዲያ ሰብሉ ሲደርስ ለማዳዋ ጦጣ ወደሰብሉ በመግባት ምስሩን ትቀምሰዋለች። ፍሬው ከማነሱ የተነሳ እንኳን ለመብላት ለመያዝና ለመፈልፈል አልመች ቢላት በሰው ልጅ ተበሳጭታ ስተሰበቃ፤ 
“አተር መዝራት ወይ ብልሃት
ምስር መዝራት፣ ሥራ ማጣት!” በማለት ተረተች። 

የማይወዱትን ማጣጣል የሚወዱትን ነገር ከፍ ከፍ ማድረግ የሰው ልጅ ስር ሰደድ ጠባይ እንደሆነ ለማስተማርና ለማመላከት የቀረበ ቀላል የመወያያ ተረት እንደነበር ልብ ይሏል።


*****
ምስር፦
ለወጥ የሚኾን ፍሬው ዐነስተኛ አበባ እህል (ብርስን ምስር ([ግዕዝ])። በአፍሪቃ ሰሜን በሚዲቴራኔአን ባሕር ወሰን ያለ ከፍልስጥኤም ጋር የሚዋሰን ምስር በሚስራይም ምስር የተባለ የጥንት አንቲካ የሚገኝበት።

ምስር፦
ቃና የቀንድ ጡሩንባ የቀንድ መለከት በዐመት በዐል ቀን በንጉሥ ፊት የሚነፋ ነው ምስር ቡዋቡዋ ሠረገላ ማለት ነው የነፊው ትንፋሽ በቡዋቡዋው በሠረገላው ውስጥ እየተላለፈ ልዩ ልዩ ድምፀ ቃናን ስለሚአሰማ ምስር ቃና ተባለ ምስር ቡዋቡዋ ቃና ዜማ ([ዐረቢኛ])።ያይጥ ምስር ቅጠሉ ምስር የሚመስል ሐረጉ እንደ አደንጓሬ ሐረግ የሚሳብ ፍሬው ጠንካራ። ግብጥ ምስር አንድ ዐይነት ወጥ።

ብርስን (ግዕዝ ሲሆን ቃሉ ትርጓሜው ‘ምስር’ ነው)፦ በቁሙ ብርስን (መ፡ ፈ)፡፡ ስመ ሀገር ግብጥ የሚጽራይም ክፍል ሚጽር፡፡ ሊጣፍ የሚገባው በጻዴ ነው እንጂ በሳት ሰ፡ አይዶለም፡፡ ደለወ ምስር፡፡ ማዕልቃ ዘምስር፡፡

ቮልቴር ስለ ቃላት የሃሳብ መሸሸጊያ መሳሪያነት ሲናገር እንዲህ ብሎ ነበር፦ “ዋናው የቃል ጠቃሚነቱ ሃሳባችንን ለመሸሸግ ማገልገሉ ላይ ነው”

ለምሳሌ  በ“የምስራች” ውስጥ “ምስር ብላ” ተሸሽጓል። በምስር ውስጥ “ወሬ የለውም ፍሬ” የሚለው አስተምህሮ ተቀብሯል። የምስራች ወሬ ቢሆን ኖሮ “ወሬ- የለውም ፍሬ!” የሚለው ቃል ምስር ወጥ ሆኖ በተበላ ነበር። ወሬ የደቃቋን የምስር ፍሬ ያህል ዋጋ ከሌለው ታዲያ ስለምንስ “የምስራች!” ይበሰራል? በርግጥ ብስራት በሚለው ቃላት ውስጥ (ብስል-ዕራት እና ምስር) ተሸሽገው ይሆን? ወይስ ራሱ “ምስራች” የሚለው ቃል (ምስ-እራት) ከሚለው ተወልዶ? 

አያሌ “የምስራቾች ወሬ ሆነው ለፍሬ ሳይበቁ እንደሚያልፉ ምሳሌ የሚሆን ሰሚ ያጣ ተናጋሪ ምርር ብሎ እንዲህ ተናግሯል ሲሉ ሰማሁ፦

“ወሬኛ ሳይጠፋ ሞልቶ ተትረፍርፏል
ራብ የሚያስታግስ፣ የሚሰማኝ የታል?”

ምስር የወሬን ያክል አቅም ባይኖረውም ወሬን በተግባር (በቅንጣት ፍሬው አልመሽምሾታል። ወሬ አቅም አልባ እንደሆነ ከቅንጣት ያነሰው ፍሬ ምስክር ተጠርቷል። ምክንያቱም ዛሬ ስለ ምስር የማበስረው ገድሉን እንጂ ወሬ ብቻ ባለሞኑም ጭምር ነውና ተከተሉኝ፥ 

በአበው እና እመው አንደበት “ጦር ከፈታው፣ ወሬ የፈታው” እንደሚበልጥ ስነገረን እያደመጥን አድገናል። ያም ሆኖ ግን ወሬ የምስርን ያህል ቅንጣት ፍሬ የለውም። “ወሬ- የለውም ፍሬ!” ለአበባ የለውም ገለባ! ሲባል ያለምክንያት አልነበረም። ፍሬ ያለው ወሬ እንዳለ ጭምር ለማመላከት ነው። ያ ፍሬ ያለው ወሬ ደግሞ “የምስራች” ነው!
“የምስራች!”
ምስር ብሉ!
“የደገኛ ነወይ ወይስ የቆለኛ፣
የምሥራች ሞተች የሚል አማርኛ፣
እኛም ብንመረምር ሰውም ብንጠይቅ፣
የምሥራች ሞተች ተብሎም አያውቅ”

ጥንታዊ ከሆኑ ሰብሎች መካከል የሚመደበው ምስር የጥንታዊውን የግብርና አብዮት ካቀጣጠሉት ሰብሎች ውስጥ በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳል። በቅርቡ በግሪክ፣ በግብፅ እና በቱርክ የተገኙ የአርኪዮሎጂ ግኝቶች የሚመሰክሩትም ይሄንኑ እውነታ ነው። 

ከስምንት ሺህ አምስት መቶ አመት በፊት የሰው ልጆች ምስርን አምርተው ለምግብነት አውለውት የነበረ ከመሆኑም ባሻገር፣ በቅዱስ መፃሕፍትና በጥንታዊ መዛግብት ላይ ሳይቀር ብዙ ተብሎለታል። 

በመፅሐፍ ቅዱስ ውስጥ ኤሳው ብኩርናውን በምስር ማጣቱ አንዱ ምሳሌ ነው። ኤሳውና ያዕቆብ መንታ ወንድማማቾች ናቸው። ኤሳው ቀድሞ በመውለድ ይበልጠዋል። ኤሳው አዳኝ በመሆኑ አንድ ቀን ደክሞት ወደቤቱ ሲመለስ ያዕቆብ ምስር ወጥ እየሰራ ይደርሳል። የይስሐቅ የመጀመሪያ ልጅ የነበረው ኤሳው የብኩርና መብቱን በማራከሱ የተነሳ አንድ ቀን ኤሳው ተርቦ ሳለ ምግቡን ባየ ጊዜ ብኩርናውን (ውርሻው) መብቱን ለስጋ ድክመቱ አሳልፎ የሚሰጥበት አጋጣሚ ይፈጠራል። ይህም በዘፍጥረት 25:30 እንዲህ ተገልጿል።  

“ቶሎ በል እባክህ፣ በጣም ስለደከመኝ ከዚያ ከቀዩ ወጥ የተወሰነ ስጠኝ!” አለው። በዚህ ጊዜ ያዕቆብ “በመጀመሪያ የብኩርና መብትህን ሽጥልኝ!” አለው። ኤሳውም “እኔ ለራሴ ልሞት ደርሻለሁ! ታዲያ የብኩርና መብት ምን ይጠቅመኛል?” አለው። ያዕቆብም “በመጀመሪያ ማልልኝ!” አለው። እሱም ማለለት፤ የብኩርና መብቱንም ለያዕቆብ ሸጠለት። ከዚያም ያዕቆብ ለኤሳው ዳቦና ምስር ወጥ ሰጠው፤ እሱም በላ፣ ጠጣም፤ ተነሥቶም ሄደ። በዚህ መንገድ ኤሳው የብኩርና መብቱን አቃለለ።” ከዚያ በኋላ ስሙ ኤዶም (ቀይ) ተባለ። ቄእ ወጥ? ቀይ ምስር? (ብቻ ከሁለት አንዱን ነው)

ምስር በዋነኝነት ለሰው ልጅ ምግብነት ብቻ ሳይሆን በአንፃሩ ሲታይ አነስተኛ መጠን ቢሆንም ለእንስሳት መኖ ጥቅም ላይ ይውላል። በፕሮቲን የበለፀገ ሲሆን፣ ካርቦሃይድሬት 47-65% ፕሮቲን 20-33%፣ 2-4% መአድናት እና 2% ቅባት ይዟል። በተለምዶ “ደም ማነስ” የሚለው አገላለጽ በደም ውስጥ በቂ ሂሞግሎቢን አለመኖሩን የሚያመለክት ነው። በሂሞግሎቢን ሞለኪውል ውስጥ የሚገኙት አራት ወሳኝ የብረት አተሞች ከሌሉ በዚህ ሞለኪውል ውስጥ የሚገኙት የተቀሩት 10,000 አተሞች ምንም ፋይዳ አይኖራቸውም። ስለዚህ ጤናማ ምግብ በመመገብ በቂ የብረት ማዕድን ማግኘት በጣም አስፈላጊ ነው። በብረት ማዕድን የበለጸጉ የምግብ ዓይነቶች ውስጥ ዋንኛው ደግሞ ምስር ነው። 
*ምስር ለብርታት!
የአይረን (ብረት) እጥረት ለጤና መዛባትና ለአካላዊ መዳከም እንደሚያጋልጥ ተደርሶበታል። ምስር ብርታትን ለመጨመር ይጠቅማል። ልብ በሉ፤ በተለምዶ “ደም ማነስ” የሚለው አገላለጽ በደም ውስጥ በቂ ሂሞግሎቢን አለመኖሩን የሚያመለክት ነው። በሂሞግሎቢን ሞለኪውል ውስጥ የሚገኙት አራት ወሳኝ የብረት አተሞች ከሌሉ በዚህ ሞለኪውል ውስጥ የሚገኙት የተቀሩት 10,000 አተሞች ምንም ፋይዳ አይኖራቸውም። ስለዚህ ጤናማ ምግብ በመመገብ በቂ የብረት ማዕድን ማግኘት በጣም አስፈላጊ ነው። በብረት ማዕድን የበለጸጉ የምግብ ዓይነቶች ውስጥ ዋንኛው ምስር ነው። 
ምስር ብሉ!
ቀላሉ ነገር ምስር “እንትን” የከላከላል። እውነቴን ነው፤ ማለት ካንሰርን ይከላከላል! 
ምስር ብሉ!