2016 ፌብሩዋሪ 20, ቅዳሜ

ዝሆን ለምን…!?

(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)

"የተረገመ ዝሆን!!" አለ በሃዘን ልቡ ተነክቶ። "በቃ፣ ለመቅበሪያ ጉድጓድ ለመቆፈር ተጨማሪ ቀን እዚህ ላድር ነው" ሲል አሰበ።
*
*
*
*
*
("በድሮ በድሮ" ጃሉድ ስታይል) ስንቀይረው
*
*

"የተረገመ ዝሆን!!" ሲል በብስጭት አጉተመተመ ጉንዳኑ። "በቃ፣ አፈር ከሚበላው ተሸክሜ ብወስደውና ብንበላው ይሻላል" 
*
*
(ሞት አደላድሎ አፈር ካልተጫነኝ፣ 
ቃሌን አላጥፈውም ካንተ ጋ ኗሪ ነኝ።) 
*
*
ጉንዳኑ ሐዘን ልቡን አደማው።

እናም እውነታውን እያሰበ እንዲህ አለ…
"የተረገመ ዝሆን!! በፍቅር ላሳለፍኩት አንድ ሌሊት ስል እድሜዬን ሙሉ መቃብሩን ልቆፍር ነው ማለት ነው" 
*
*
*
በመቀጠልም ዝሆኑ ሃውልት ላይ የሚያሰፍረው አጭር ግጥም አዘጋጀ፦

"ለምን ሞተ ቢሉ 
ንገሩ ለሁሉ ሳትደብቁ ከቶ
ከዘመን ተኳርፎ፣ ዘመን ተጣልቶ"

2016 ፌብሩዋሪ 19, ዓርብ

ተራማጅ እሳቤ ፵፯

( ኄኖክ ሥጦታው ናኁሰናይ )

ውሃ…
*
ከፍታን መርጦ ሲጣበቅ፣ በረዶ ሆኖ ሲደድር
ውሃም ይወጣል ዳገት፣ ይወርዳል ሙቀቱ ሲንር።
*
በረዶ አቅላጩ ሙቀት፣ በድን አካል ካፈረሰ
ነዲድ ያገኘው አለት፣ ቀልጦ ቁልቁል ከፈሰሰ
መጠጠርስ እንደውሃ ፣
መቅለጥ …
መትነን…፣
 ሽቅብ መውጣት… ቁልቁል መውረድ…
(ቅዝቃዜ ፅሞና ነው። ርጋታን ለአፍታ ልውደድ)
ራስ…
ለራስ…
ከራስ…  ጋ
ጠምቶኛል ዘልቆ መዋኻድ
ከመትነን ከፍታ በታች፦
እንደበረዶ ጠጥሮ፣ ደግሞ እንደ ዥረት ለመውረድ።
*
ውሃ…
ወንዙ መንገድ ቀይሯል፣ የድርቅ ዱካውን ትቶ
ወዴት ወርዶ አለቀ? ከምድር ሰርጎ ገብቶ?
በሰማይ መንገዱ ተጓዘ? በትነት ሽቅብ ወጥቶ?
*
ራሴን ተጠማሁ…

በደረቀው መንገድ ላይ፣ ቆሜ ነበር ሃሳብ ጠምቶኝ
አሁን አቅጣጫው ሲገባኝ፣ የወንዙን መንገድ መረጥኩኝ
ወደሄደበት ብሄድ ነው፤ ጥቂት ውሃ የማገኝ።

ጠምቶኛል…

2016 ፌብሩዋሪ 17, ረቡዕ

"እሾህን በሾህ"

✧(ኄኖክ ስጦታው)
(የአጭር አጭር አጭር ልቦለድ)

ለእራት የሚሆን ነገር ለመግዛት ወደ ሱቅ አመራ። እንደ ሁልጊዜውም፣ ጎረቤቱ የአይጥ መርዝ እየገዛ ነበር። ከጎረቤቱ ቤት መርዝ በልተው እሱ ቤት ኮርኒስ ውስጥ የሚሞቱ አይጦች ሽታ ረፍት ነስቶታል።
"ለምን በወጥመድ አታጠምዳቸውም?" አለና መፍትሄ ይሆናል ያለውን ሃሳብ አቀረበለት። ለጎረቤቱ።
"ሞክሬ ነበር። ወጥመድ ማለት የአይጥ ገበታ ነው። አይጦቹ ወጥመዱ ላይ ያለውን ምግብ በልተው ይሄዳሉ። ጠዋት ስነሳ ወጥመዱ የሚይዘው እኔኑ ነው።"
ዝም አለ።
አስቦ ፣ አስቦ… አንድ መፍትሄ አገኘ። እናም ጎረቤቱ ዞር እስኪል ጠብቆ፦
"የአይጥ መድሃኒት አለ?" ሲል ጠየቀ። ለባለሱቁ።
"የለም። መርዝ ነው ያለው"
"እሱንም ቢሆን ስጠኝ"