2014 ኖቬምበር 9, እሑድ

ዱባና ልጅነት

(ኄኖክ ስጦታው)

#ዱባ
ልጅ ሆኜ የሰማሁት ዘፈን አለ። ስለዱባ እንዲህ ብሎ ነበር፦

"ሳይበላ ሳይጠጣ ይወፍራል ዱባ
ልቤ ተንከባሎ አንቺ መንደር ገባ "

ግጥሙን አድጌ ስረዳው ልብ እና የሚንከባለል ዱባ  ያገናኛቸው ቤት መምቻቸው "ባ" እንደሆነ ገባኝ። ዱባ ወጥ አልወድም።  የዘፈኑ ተፅእኖ ነው መሰል፣ ቤታችን ዱባ ወጥ ሲሰራ ገንዘብ የወጣበት አይመስለኝም ነበር ። ተንከባሎ ቤታችን የገባ ነበር የሚመስለኝ።

በልጅነት ዘመን የማልረሳው አንድ ገጠመኝ አለ። የእርሻ አስተማሪያችን ስለ አዝእርት ሲያስተምሩ እንዲህ ብለው ጠይቀው ነበረ፦

"ከጥራጥሬ ውስጥ የሚመደቡት ምን ምን ናቸው?"

ምድረ ተሜ ተራ በተራ እየተነሱ "ጓያ፣ ሽንብራ፣ ባቄላ…" እያሉ መለሱ። መምህሩ ወደኔ እያዩ፣ "ኄኖክ ፣ የምትጨምረው አለ?" ሲሉኝ ፣ ከመቀመጫዬ ተነስቼ "ዱባ" አልኩና ተቀመጥኩ። የተማሪው ሳቅ እና ያስተማሪው ድንጋጤ ተደምሮ፣ በስክሪብቶ ጫፍ ቂጡን እንደተወጋ ተማሪ አስፈንጥሮ አቆመኝ። (ድሮ ተንኮለኛ ተማሪ አጠገቡ የሚቀመጥ ተሜን ብድግ ሲል ያለቀ ስክሮብቶ አሹሎ እስኪቀመጥ ይጠብቅ ነበር። ያሁኑን ባላውቅም።)

መምህሩ በግርምት አፍጥጠው ፣ አፍጥጠው፣ አፍጥጠው… አይተውኝ ሲያበቁ፣ ባፍንጫቸው የንፋስ ሳቅ ("ህምፍ" አይነት) አሰምተው ዱባ ያልኩበትን ምክንያት ጠየቁኝ። ክፍሉ ረጭ አለ ። እንዲህ ረጭ ያለ ዝምታ ለመጨረሻ ጊዜ ያስተዋልኩት ያኔ ነበር።

ዱባ የጥራጥሬ ዝርያ ለመሆኑ የሰጠሁት አጭር ማብራሪያ፦

"የዱባ ፍሬዎች ፀሐይ ላይ ተሰጥተው ሲደርቁ፣ ተቆልተው ይበላሉ። ልክ እንደ ሽምብራና ባቄላ ማለት ነው።" ከማለቴ ክፍሉ በሳቅ ተናወጠ።

ምን  የሚሳቅ ነገር አግኝተው እንደሆነ ለማወቅ አይኖቼን በክፍል ጓደኞቼ ዙሪያ አንከራተትኩ። ሳያቸው ነው መሰል ይበልጥ መሳቅ ቀጠሉ። ከሁሉ ከሁሉ የገረመኝ፣ የመምህሩም አብሮ መሳቅ ነበር። መቆም እንዲህ ያስቃል?

መቀመጥ ሳይሻል አይቀርም።
ተቀመጥኩ።