2016 ፌብሩዋሪ 25, ሐሙስ

አዳም… (ኄኖክ ሥጦታው ናሁሰናይ)

አዳም…
(ኄኖክ ሥጦታው ናሁሰናይ)


"ጥፋት"፣ "ታዛዥነት" …
ቢጋጩ ከድንጋይ
                "ተቃጠልኩኝ" አትበል…
                 እሳት ፈጥረው ብታይ።
*
ፍላጎቱን ሳይኖር፣ "ሕግን" ያከበረ፣
በተጻፈው እንጂ፣ ራሱን መች ኖረ?!
*
አዳም ሰው አትስማ፣ ከትዛዝ ላይወጣ
"ሕግ ጣሰ" ይበል፤ "በበላው ተቀጣ"
የኖርከውን ሳይኖር፣ ያስብ ምን እንዳጣ!
*
አዳም ተለመነኝ፤ አንተ ኑረህ ብላ…፣ ቅጣት ምናባቱ

ያልበላው ይታዘዝ… ሕግን ማክበር "መብቱ…"
*
አዳም በአፈርህ፦
ብላ… ደግመህ ብላ… የሕግ አጥር ይፍረስ
"አምላክ ይጠራኻል"፤ ክልከላውን ስትጥስ!

2016 ፌብሩዋሪ 23, ማክሰኞ

በቮልስ ያጉረመረምንበት ሰርግ ትዝታ

ይህ ትዝታ ይደንቀኛል። ጋራጅ የተዋወቅኩት ሰው ሰርግ ላይ መላው የቮልስ ባሉካዎች በአጃቢነት ተጋብዘን ነበር። አጃቢ መኪኖች በጠቅላላ ቮልስ ዋገን ናቸው። እውነት ለመናገር በአገሪቱ ውስጥ ካሉ ሾልሶች አንድም የቀረ አይመስልም።

ሰርጉን ለማሳመር  አጃቢ የሆኑት ቮልሶች ራሳቸው በመካኒክ ታጅበው ነበር። በቮልስ የሚታጀብ ሰርግ ያለመካኒክ የማይታሰብ ነበር። (መካኒኮቹ መንገድ ላይ ለሚበላሽ መኪና ፈጣን ጥገና እያደረጉ ጉዞው ቀጠለ።)

ታዲያ ያኔ መናፈሻ ውስጥ የነበረ አሙቁልኝ አዝማሪ እንዲህ ብሎ ፈተለ፤

"ጉርምርሜ ና ጉርምርሜ
ያሆ በሌ፣ ያሆ በሌ ፣ ጉርምርምርምርም…
ባባው ቮልስዬ ፣
ያሆ ቮልስዬ፣ ያሆ ቮልስዬ… ጉርምርምርምርምርም… (ተቀብለን አስተጋባን)
አዝማሪው ቀጠለ፦

ሚስቱን  ያገኘው…
ያሆ በሌ…  ያሆ በሌ… ጉርምርምርምርምርም…
ጉርምርሜ በግሩ ሲያዘግም!"

(ይህኔ የምር አጉረመረምን)

2016 ፌብሩዋሪ 22, ሰኞ

የኄኖክ እልፍኝ HENOK'S PAD: hamot የግጥሞች-ስብስብ-በኄኖክ ስጦታው [PDF]

የኄኖክ እልፍኝ HENOK'S PAD: hamot የግጥሞች-ስብስብ-በኄኖክ ስጦታው [PDF]: hamot የግጥሞች-ስብስብ-በኄኖክ ስጦታው[PDF]

ሠአት ሠሪው

(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)

ሠአት ሠሪው ደጃፍ ላይ ቆሜያለሁ። ከውጭ ሆኖ ለሚመለከት ሰው ምንም የሚማርክ ውበት ላትመለከት ይችላል። የደጁን መስታወት ታክኮ የቆመው መደርደሪያ ያገለገሉ ሰዓታት ማረፊያ ሁነዋል። የተበላሹ፣ የተጠገኑ፣ የማይጠገኑ፣ ያልተጠገኑ፣… ሠአቶች ተሞልቷል። እኔ እራሴ ሁሌ የማያቸው ሰዓቶች እዚህ ምን እንደሚሰሩ አይገባኝም። አሰሪዎቹ ቢወስዷቸውና ሰዓት ሠሪው ያገልግሎቱን ቢያገኝ መምረጤን ግን አልሸሽግህም። 

መስታወቱ ላይ ሶስት ጥቅሶች አሉ። በእጅ የተሞነጫጨሩና ለንባብ የማይማርኩ ቢሆኑም፣ ከማንበብ የሚያግተኝ ነገር የለምና በታላቅ መስህብ ስሜት ተውጬ ተጠግቼ አነበብኳቸው፦

የመጀመሪያው እንዲህ ይላል፦

" ተመልከት ፤ እኔ ማንን የምጠብቅ ይመስልሃል? ጊዜ ከሌለህ እዚህ ምድር ላይ ሌላ ምንም ነገር አትጠብቅ!"

በለው ብሶት!! ሁለተኛውን አነበብኩት። 

"ሳምንቱን ሙሉ ክፍት ነው፤ የዕረፍት ቀናትን ጨምሮ" ይላል ።

አባባሉ የቁጥር መጭበርበር ያለበት ቢመስለኝም የሰዓት ሠሪው ቤት እዚሁ መሆኑ ታስቦ የተፃፈ መሆኑንና ደንበኞች ይህን ሊገነዘቡ የተቀመጠ (የቤት ስራ) መሆኑንአምኜ ወደሶስተኛው ጥቅስ አመራሁ።

ሶስተኛው ግን ለራሴም ገራሚ ነበር ፦

"ልክ እንደ ሰዓት የሚበላሽና እንደ ሰዓት ጠጋኝ የሚሰራ ሰዓት የለም!"

እናም ፣ እንዲህ እያልኩ ወደውስጥ ገባሁ፦

"የዛሬው ጥሩ ይመስላል፤ መቼስ እስከዛሬ ከለጠፍኳቸው ይሻላል!"

2016 ፌብሩዋሪ 21, እሑድ

☆እግረ-መንገድ

(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)
‪‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬

የምሰማው ሁሉ አልጥምህ ብሎኛል፡፡ የሬዲዮኑን ጣቢያ እየቀያየርኩ የሚጥመኝ ፕሮግራም ፍለጋ ጀመርኩ፡፡ ዘፋኙ ሁሉ ዘማሪ ሆኗልና! . . . ሬዲዮኑን ዘጋሁትና ቲቪ ከፈትኩ፡፡

በቲቪ፣ የአንድ አዲስ ምርት አምራች ድርጅት ማስታወቂያ እየተላለፈ ነበር፡፡ አስተዋዋቂው፣ ድምፁን ከሌላ ሰው የተዋሰው ይመስላል፡፡ በግነት በተዋቀረ ድምጽ እንዲህ እያለ ነበር፡-

“ልብ ይበሉ! ምርታችን በአይቱ አዲስ እና አስተማማኝነቱ የተረጋገጠ ነው!!”

በለው ውሸት!

“አዲስ እና አስተማማኝ” ማለት ምን እንደሆነ የገባቸው አልመሰለኝም፡፡ አዲስ ከሆነ አስተማማኝነቱ ገና አልተረጋገጠም ፤ የተረጋገጠ ለመሆን ከዚህ ቀደም የሚታወቅ መሆን አለበት፡፡ ይህን እንኳን አያስቡም፡፡

ተጨማሪ ውሸት ሽሽት ቲቪውን ዘጋሁትና ከቤት ወጣሁ፡፡ ትንሽ በእግሬ ዞር ዞር ብዬ ብመለስ እንደሚሻል በማሰብ ነበር አወጣጤ፡፡

ማምሻ ግሮሰሪ የማውቀው አንድ ሰው ከሩቁ “እንኳን አደረሰህ!” ሲለኝ፡፡ “እንኳን!” አልኩት ከሩቁ፡፡

“እንኳን ምን? ” አለና መልሶ ጠየቀኝ፡፡

“እንኳን ብቻ!” ብዬ መንገዴን ቀጠልኩ፡፡

“አይ አንቺ ሰው ፤ በጊዜ አግለሻል መሰል...” ሲል ከጀርባ ይሰማኛል፡፡ ሰው ግን በዓል ሲመጣ ብቻ ነው እንዴ “መድረሴ” ትዝ የሚለው?

መንገዱ ጭር ብሏል፡፡ አንድ ሰው ብቻ ከሩቅ ይታየኛል፡፡ የሆነ ነገር እያወራ እንደሆነ ያስታውቃል፡፡ እየቀረብኩት ስሄድ ምን እያለ እንደሆነ ተሰማኝ፡፡
“የበግ ቆዳ ያለው? ” እያለ ነበር፡፡

አጠገቤ ሲደርስ ወደኔ እያየ ጮክ ብሎ ፤ ”የበግ ቆዳ ያለው!” አለ፡፡ ዝም ብዬው አለፍኩ፡፡ “ሰዉ ዛሬ ምን ነክቶታል?! ” ስል አሰብኩ፡፡ እውነት የበግ ቆዳ ቢኖረኝ መንገድ ለመንገድ ይዤው የምዞር መስሎት ይሆን?!

ሳላውቀው ብዙ ርቀት በእግሬ ተጓዝኩ፡፡ .... አምስት ሴቶች ከሩቅ ይታዩኛል፡፡ ታክሲ እየጠበቁ መሆን አለበት፡፡ እየቀረብኳቸው ስሄድ አለባበሳቸውን ለየሁት፡፡ አራቱ ሴቶች ነጭ የአገር ባሕል ልብስ ለብሰሰዋል፡፡ አንዷ ግን በጅንስ ተወጣጥራለች፡፡ ፀሐዩን ሽሽት በዣንጥላ አናቷን ከልላለች ፡፡ ተስፋ ቆርጣ መሆን አለበት ከመሃከላች ወጥታ በእግሯ መጓዝ ስትጀምር አየኋት፡፡

ነጭ የለበሱት አራቱ ካሉበት አልተንቀሳቀሱም፡፡ በአጠገባቸው ሳልፍ ከመሃከላቸው አንዷ፡- “ወንድም ፤ ሰዓት ይዘሃል? ” ስትል ተሰማኝ፡፡

“አዎ!” አልኳትና መንገዴን ቀጠልኩ፡፡ ልጅቱ ስንት ሰዓት እንደሆነ እንድነግራት እየጠበቀች ነበር መሰለኝ፡፡ ግን የጠቀየቀችኝ ሰዓት መያዜን ነው፡፡ እርሱንም “አዎ” ብያታለሁ፡፡

ዣንጥላ የያዘችው ሴት ከፊት ከፊቴ ስትሄድ አየሁ፡፡ የሚገርም ጀርባ አላት፡፡ እውነት የተፈጥሮ ከሆነ መቀመጫዋ ያምራል፡፡ (ሴቱ እንደ ውስጥ ሱሪ የሚጠለቅ አርቴፊሻል መቀመጫ መጠቀም ጀምረዋል አሉ! ) ይሁን ፡፡ መጠቀማቸው ክፋት የለውም፡፡ የሚቆረቁር ወንበር ላይ ሲቀመጡ እንዳይቆረቁራቸው ከሆነ መልካም ነው፡፡ (ምቾት በሌለው ወንበር ላይ ረጅም ሰዓታት ለሚቀመጡ ወንዶችም ይህ ዘዴ ይጠቅማል መሰል፡፡ )

ሰውነቷ ያምራል፡፡ ዕድሜዋን ለመገመት ሞከርኩ፡፡ በጥቂት ዓመታት ብትበልጠኝ ነው፡፡ “ታላቄ” እንደሆነች ሳስብ አንድ አባባል ትዝ አለኝ፡፡ “ከእያንዳንዷ ታላቅ ሴት ጀርባ መቀመጫዋን የሚያይ ወንድ አይጠፋም!” ሆሆሆ . . . ለጀመሪያ ጊዜ ፈገግ አልኩ፡፡
‪‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬
“ልመለስ!? ወይስ መንገዴን ልቀጥል!?” . . . ስል አመነታሁ፡፡ ሉፒዶ (ሽፍደት) ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ ይህ ተፈጥሮ ግን መገለጫው ብዙ ነው፡፡ እያንዳንዱ ሰው እንደየምልከታው ግንዛቤ የሽፍደት አካል መረጣውም ይለያል፡፡

የሰውነት አካላት ሁሉ የዚህ ምልከታ ውጤት ናቸው፡፡ በርግጥ መቀመጫዋ የሚያምር ሴት አይቶ “አሪፍ መቀመጫ አላት” ያለ ሁሉ ይህቺን ሴት ተመኛቷታል ማለት አይደለም፡፡ ማድነቅም ሌላው ተፈጥሮ ነውና፡፡ ከፊቴ ያለችውም ሴት ለእኔ እንደዚሁ ናት፡፡ ያየሁትን ማራኪ ሰውነት አለማድነቅ እንደማልችለው ሁሉ፣ ያደነቅኩትን ማራኪ ሰውነት ሁሉም አልመኝም፡፡ ይህም ተፈጥሮአዊ ነው!

ጥቂት መንገድ የመግፋት ሃሳብ አጋደለና መጓዜን ቀጠልኩ፡፡ ከፊቴ ግን ታላቅ ውሳኔ የሚሻ ነገር እየተውረገረገ ነው፡፡ ከቤቴ የወጣሁት ዳሌ ለመከተል አልነበረም፡፡ አሁን ግን ባጋጣሚ ዳሌ ተከታይ ከመሆንም አልፌ አድናቆት ገላጭ አባባል ቀማሪም እየሆንኩ ነው፡፡ ʿይህን ታላቅ ዳሌ እስከምን ድረስ ነው የምከተለው?! ከዚህ በላይ ከመከተል፣ ዳሌዋን ስካን ማድረግ ይቀላል፡፡ʾ ስል አሰብኩ፡፡

በነገራችን ላይ ፤ ከኋላ መሆን መከተል ነው ያለው ማነው?! (ከእረኛን ተመልከቱ፡፡ ከብቶቹን የሚያግደው ከፊት ከፊታቸው እየሄደ አይደለም፡፡ በጉዞ ላይ ያሉ ከብቶች ካያችሁ ፣ ከኋላቸው እረኛ መኖሩን አትዘንጉ) በዚህ ምሳሌ ብቻ ተገፋፍቼ ለዚህ ታላቅ ዳሌ እረኛ የሆንኩት እንዳይመስልብኝ ስል ርምጃዬን አፍጥኜ አለፍኳት፡፡ አሁን ተራው የርሷ ነው፡፡

ሴቶች ግን . . . ወንድን ከጀርባው ሲመለከቱት ምኑን ይሆን ቀድመው የሚያት?! (ዋሌቱ እንደማይሆን ግን ርግጠኛ ነኝ፡፡)

አልፌያት ጥቂት እንደተራመድኩ ፡- “ይቅርታ፣ አንድ ጥያቄ ልጠይቅህ እችላለሁ?” የሚል ድምጽ ሰማሁ፡፡ እኔን እንደሆነ ርግጠኛ ሆኜ ፊቴን አዞርኩና ልናገር ስል አንድ ነገር አገደኝ፡፡ ዳሌ ዳሌዋን ሳይ ያላየሁት ሌላ ሰው የስልክ እንጨት ፖል ተደግፎ ቆሞ ነበር ለካ፡፡ እሱን ነበር የጠየቀችው፡፡ እምም . . . ተረፈች፡፡ እንኳንም እኔን አልጠየቀች!

በጣም ከሚያናድዱኝ ጥያቄዎች አንዱ ይህ ነው፡፡ “አንድ ጥያቄ ልጠይቅህ?” ብሎ መጠየቅ በራሱ አንድ ጥያቄ ነው፡፡ እንዲህ ብለው የሚጀምሩ ሰዎች ሌላም ችግር አለባቸው፡፡ ያስፈቀዱት አንድ ጥያቄ ለመጠየቅ ሆኖ ሳለ መልሱን ተከትለው ተከታታይ ጥያቄ ማዥጎድጎዳቸው ነው፡፡

የመጀመሪያውን ፈገግታ የፈጠረው ስሜት በምን ፍጥነት ጥሎኝ እንደጠፋ እንጃ፡፡ ብሽቅ!

መቼስ በበዓል ቀን ታክሲ ከመጠበቅ ታክሲ መሸከም ይቀላል፡፡አውቶቢስ ፊርማታ ሳገኛ ቆምኩ፡፡ በእግሬ የመጣሁትን መንገድ በእግሬ የመመለስ አቅም አልነበረኝም፡፡ ታክሲ ቢጠፋ እንኳን ባስ እንደማላጣ ርግጠኛ ነበርኩ፡፡

(ሞራል)፡-
ጥቂት ሰዎች የባሷን መምጫ በጉጉት ይጠብቃሉ፡፡ እኔም እነርሱ ወደሚያዩበት አቅጣጫ አፍጥጫለሁ፡፡ አልፌያት የመጣኋት ቆንጂዛ አልፋኝ ከሄደች ቆይታለች ፡፡ (ማሳለፍ ትልቅ ችሎታ ነው፡፡ ማለፍም፡፡) አለማለፍ ግን ደካማነት፡፡ አለማድነቅ ስሜትን ለሌላው አለማሳወቅ ነው፡፡ ለራስ የተሰማን የአድናቆት ስሜት መሸሸግም ያው አልሸሹም ዞር አሉ ነገር፡፡ የአድናቆት ስሜትን ለሌላው ለማሳወቅ ሲባል ግን እንደኔው ሁሉ ተረጋግተው የሚጓዙትን ሰዎች መልከፍ ግን በነፃው መንገድ ላይ ነፃነትን ከመንፈግ አይተናነስም!!

አድናቆት በሰፊ ቦታ ጠባብነትን ማግዘፍ ሳይሆን ሌላ ስፋትን መጨመር ነው ብዬ አምናለሁና፡፡ ስለዚህም በማለፍ አምናለሁ፡፡ በማሳለፈፍም፡፡

ማሳሰቢያ፡- የእግረ መንገድ ወግ እንደ መዋቅር የተጠቀምኩበት መንገድ፣ ቅርፅ እንጂ እውነተኛ ገጠመኝ አይደለም፡፡ ምልከታን የመግለጫ አንድ መንገድ እንጂ፡፡

ከሳንቲሞች መኻል የአንድ "ብር" ስሞታ

(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ) 

የአንድ "ብር" ስሞታ

አንድ ብር ሳንቲሞች መካከል የቀላቀለውን አዲስ ማንነቱን ይዞ ነበር የተገኘው። ከል የለበሰ ያህል እየተሰማው፣ ቅሬታውን እንዲህ ሲል ለሳንቲሞች አሰማ፦

"…ህይወቴ ምስቅልቅል ብሏል። ወይ ከብሮች መካከል አልተመደብኩም። ወይም ለይቶልኝም ከሳንቲሞች መንደር ጠቅልዬ አልገባሁም ። እኮ እኔ ነኝ?

"ማንነቴን የሚንቁ በዝተዋል። የአምስት ሳንቲም መለያ የነበረው መርፌ የመግዛት አቅሟን ያሰጣት ቅፅል ስም ዛሬ የኔ መጠሪያ ሆኗል። "ባለብሩ ዳቦ" ተብሎ በግርማ ሞገሱ የሚታወቀው የጥንቱ መጠሪያዬ ዛሬ ተረት ሆኗል። ባለብሩ ዳቦም  እንደዛው።

"ውሎና አገልግሎቴ ሙዳየ ምፅዋት ውስጥ ከሆነ ቆየ። ለማኝና መፅዋች ሲቀባበሉኝ መዋል ሳያንሰኝ፣ ከታክሲ ረዳቶች መዳፍ ገብቼ ከበርና መስኮት ጋር ስታሽና ከእናንተ ሳንቲሞች መካከል ስፋጭ መዋል ታከተኝ። እኮ እኔ ማነኝ?! ስሜስ የማነው! ?"

"አይዞህ አንድ ብር " አለ አምስት ሳንቲም— በስላቅ። "ገና ምኑን አየህና ትማረራለህ?" ሲል አስር ሳንቲም አከለበት።

አንድ ሳንቲም በኩራት ወደ ስሙኒና ሽልንግ እየተመለከተ፤ "አምስትና አስር ሳንቲምን አትስማቸው። አንተን የምትመስለው እኛን ነው። እነሱን ተዋቸውና እኛን አማክረን" አለ ጸአዳ ነጭ ጥርሱን እያሳየ።

አምስት እና አስር ሳንቲም አንድ ሳንቲም ላይ እኩል አንቧረቁበት፦ "አንተ ደግሞ የምን ቤት ነህ?! ዋጋ ቢስ!!"

ሃምሳ ሳንቲም ተቆጣ ። "ፀጥታ! አንድ ብር ዛሬ እንደማናችንም ሆኗል። ይህ ብር የሁላችንንም መልክ እና ግብር ተላብሶ ከመኻከላችን ተገኝቶ ብሶቱን እያካፈለን ነው። እንስማው። …" አለና ጭቅጭቁን አብርዶ ወደ አንድ ብር ፊቱን መለሰ።

"አይዞህ አንድ ብር። ዛሬ ቀን ጥሎህ ከኛ መኻል ቢቀላቅልህም አትዘን ። አሁን ካቆምክበት መቀጠል ትችላለህ…" 

አንድ ብር ልቡ በኻዘን ተነክቶ ብሶቱን በዜማ ማተት ጀመረ…(ዜማው በእንባው ከመታጀቡ በቀር ፣ቁርጥ የሸዋንዳኝ ዘፈንን ይመስል ነበር)


"ስሜስ የማነው?! ላምጪው ምን ከፈለ?!
ሳንቲም ሲጠራ ፣ አፌ አቤት እያለ!!―"
.*
*
*
*
"እኔ እንደዚህ፣
እስኪነሳኝ አቅም
ተዋርጄ አላውቅም"


ማንደፍሮሽ

(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)

እውነተኛ ስሟ "ማንደፍሮሽ" ነው። እኔና መሰል አብሯ አደግ ጓደኞቼ ግን ፣ በቁልምጫ "ማኔ" እያልን እንጠራታለን። የመንደራችን ሴት ልጆች እንኳን በአካል አይተዋት ይቅርና፣ ገና ስሟ ሲጠራ በፍርሃት ይርዳሉ። ምግብ አልበላም ብለው ሲያስቸግሩ "ማኔን እንዳልጠራት!" ማለት በቂ ነው። ታዲያ እኩዮቿ ብቻ ሳይሆን ታናናሽ ወንድሞቻችንም ቢሆኑ የ"ማኔ" ስም ከተጠራ፣ የቀረበላቸውን ምግብ ጥርግ አድርገው እየበሉ አድገዋል።

ታዲያ ዛሬ ድረስ የሚገርመኝ ነገር ቢኖር የማኔ እንዲህ የመፈራት መንስኤ ነበር። በርግጥ ከወንድ ጋር የሚያመሳስላት ምንም አካላዊ መለያ የላትም። በእነዚህ ሁሉ የጓደኝነት ዓመታት፣ እንደወንድ  ለመምሰልም ምንም አይነት ጥረት ስታደርግ ማየቴንም እጠራጠራለሁ።

ልጅ እያለን ኩሽና ውስጥ እቃቃ ስንጫወት የሆነው ሁሉ አይረሳኝም። "አንቺ ሴት ነሽ፤ ለምን ከመሰሎችሽ ጋር አትጫወቺም" ብለን ጠይቀናት ነበር። መልሷ ግን የከፋ ነበር። በሁለት እጆቿ ያፈሰችውን አመድ ዐይናችን ውስጥ ሞጅራ ሮጠች። ከዛኔ ጀምሮ ነው መሰል፣ ይኸው አድገን እንኳን አንጠይቃትም።

በሌላ ጊዜ ደግሞ፣ ወንድነታችንን ተጠቅመን የበላይነታችንን እንድታምን ለማድረግ በጉልበት ልናስገብራት ሞክረን ነበር። በትግል እንደምንጥላት ተማምነን ብቻ ለብቻ ድብድብ እንድትገጥመን ጠራናት ። ብቻ፣ እንኳን እኔ አቡቹን አልሆንኩ። በመላተም ብዛት ጠንካራ የሆነ የሚመስለው አቡቹ  ጉድ አደረገን!!! ተዝረክርኮ አዝረከረከን። በወቅቱ፣ የመጀመሪያው ተጋጣሚ አቡቹ ነበር። (እንኳን እኔ አልነበርኩ።) ለትግል እንዲመቸው እግሩን አንፈራጦ በመቆም ዝግጅት ላይ ሳለ ድንገት ከማኔ የተሰነዘረው ርግጫ ብልቱ ላይ አረፈና ለሳምንታት የአልጋ ቁራኛ ሆነ። ከዛ ቀድሞ ግን እኛ የበላይነቱን ሚና ያለምንም ማቅማማት ለማኔ አስረከብን። ምክንያቱም ማኔ፣ በቅፅበታዊ ምት እና የት ቦታ ላይ መማታት እንዳለባት ተክናለችና።

ከወንዶች ጋር መሆን ትመርጣለች። (በተለይ ከኔ ጋር) ።

ማኔ ወንድ አይደለችም። ወንድም እንዳልሆነች እናውቃለን። "እኔ ሰው ነኝ!" ያለችን ቀን ምን ማለቷ እንደሆን ባይገባንም፣ ያለምንም ማቅማማት "ነሽ!" ብለናታል። ምስኪን አቡቹ! ገና ከማገገሙ፣ አላራምድ ያለውን የታፋ ስር ንፍፊት ተቋቁሞ እንደተነሳ፣ "እኔ ሰው ነኝ!" ስትል፤ "አዎ ነው!" ማለቱ ሳይቀር ትዝ ይለኛል። (ሲያስቅ... የሰው ፆታው ምንድነው? )

ሴትነቷን እየፈራን እንድናስታውስ የሚያደርገን አስገዳጅ ሁኔታ የሚፈጠረው ከስንት አንዴ ነው። እስከዛሬ፣ "ሴቷ ወንድማችን" ብሎ የጠራት አንድ ሰው ብቻ ነው። እሱም "ፎርጃ" ይሰኛል። (ቅፅል ስሙ ነው፤ የትምህርት ቤት ስሙ ረጅም ነው። ቃል በቃል ባላስታውሰውም፣ 'ፈርቼ ማለድኩት እሱን ሰጠኝ ለኔ ጃንደረባው…') አይነት ነገር ይመስለኛል። ፎርጃ፣ የቅፅበታዊ ጥቃቷ ሰለባ ነበር። እስካሁንም ነው። (ዛሬ አቡቹ አግብቶ ወልዷል) ። በርግጥ የልጁ አባት እርሱ እንደሆነ ያመንው በግድ ነው። (ያሉትን ነው ያልኩት)

ከዚህ ቀደም፣ (ወንዱ እህታችን) ያለው ፎርጃ ግን በሃኪም መውለድ እንደማይችል እንደተነገረው ካወቅን በኋላ የሁላችንም ጥያቄ ይህ ነው… 'እውን አቡቹ መውለድ የቻለው እንደኛው ሁሉ እሱም በሆነውና በሚሆነው ስላመነ ነው?! ወይስ… እንደ ፎርጃ ፣ ሃኪም ስላላየው?!"

ማኔ በሁሉም የልጅነት ጨዋታዎቻችን ውስጥ የመረጠችውን የመሆን ስልጣኗ ዛሬ ላይ ቆም ብዬ ሳስበው ይደንቀኛል። "ባል እና ሚስት" ስንጫወት እሷ የምታገባው እኔን ብቻ ነበር። እሷ ባል ስትሆን፣ እኔ ደግሞ ሚስቷ እሆናለሁ፡፡ የባልና ሚስት የጨዋታው ስርዓት በርሷ የበላይነት ተጀምሮ ያበቃል፡፡ እንደ ሚስትነቴ ምግብ የማዘጋጀት፣ ልጆችን የማጠብ፣ ቤቱን የማፀዳዳት …. ተግባራትን እከውናለሁ፡፡

ልጆቻችን ሆነው የሚጫወቱት አቡቹ እና ፎርጃ ናቸው፡፡ (እስካሁን ድረስ ማን እንዳረገዘ፣ ማን እንዳስረገዘ ባይገባኝም)፡፡ ፎርጃ እንደሴት ልጅ እንዲጫወት የምታደርገው ፎርጃን ነው፡፡ አቡቹ ደግሞ ወንዱ ልጃችን እንዲሆን ሚና ይሰጣቸዋል፡፡ ታዲያ በማኔ የሚታዘዘው አቡቹ ነው፡፡ ማኔ ትእዛዝ በመዛኙ ተመሳሳይ ናቸው፡፡ አቡቹን ጠርታ የባህርዛፍ ፍሬ (ሳንቲም መሆኑ ነው) ቆጥራ እየሰጠችው፡-

"አቡቹዬ፣ ከቃሲም ሱቅ የአስር ሳንቲም ስኳርና የስሙኒ ቡና ግዛልኝ" ትለዋለች፡፡

"እሺ፣ እማዬ" ካለ አለቀለት፡፡ የማኔ ቅፅበታዊ ምት ጭንቅላቱ ላይ ይዘንብበታል፡፡ በኩርኩም  ገጭ! ገጭ!  ገጭ! ... "እሺ አባዬ፣ ረስቼው ነው አባዬ! ይቅርታ አባዬ!" እስኪል ድረስ ኩርኮማዋን አታቆምም፡፡ አቡቹ ጥሎበት ድንገተኛ ኩርኩም ሲቀምስ ምድር ዓለሙ ስለሚዞርበት "አትምቺኝ..." ብሎ ማለቃቀስ ይመርጣል፡፡ እንዲህ ሲሆን የእናትነት ሚናዬን ተጠቅሜ ያስቀጣውን ጥፋት ልነግረው እሞክራለሁ፡፡ "አቡቹ፣ አባትህን እንዴት እማዬ ትላለህ..." ይህኔ "አባዬውን" ያዥጎደጉደዋል፡፡

ማኔ አባትነቷን አስከብራ ስታበቃ፣ "በል ፣ ሁለተኛ እንዳይለምድህ! አሁን ከቃሲም ሱቅ ግዛልኝ ያልኩህን በቶሎ ገዝተህ ና!" ካለችው በኋላ እንደ ሴት ልጅ ሆኖ ወደሚጫወተው ፎርጃ በመዞር እንዲህ ትላለች፡-
"ወንድምሽ እንዳይፈራ አብረሽው ሁኚ..."

ሁሌም ለሚስትነት እኔን እንደምትመርጥ አይገባኝም ነበር። በኋላ እንደገባኝ ከሆነ፣ አቡቹና ፎርጃ ለርሷ "ገና ልጆች" ናቸው፤ (ሚስት ለመሆን ገና አላደጉም)፡፡

በሌላ ጊዜ አንድ ጊዜ እንዲህ ሆነ፡፡ የሆነ ጊዜ ግን እየፈራሁ፡- "ዛሬም ሚስት የምሆነው እኔ ነኝ?" ብዬ ጠየኳት፡፡

"እና መጀመሪያ ሚስቴ እንድትሆን ስመርጥህ እስከመጨረሻው ድረስ ባልህ እንደሆንኩ አታውቅም?!" ብላ ተቆጣች፡፡ አ-ቤ-ት ቁጣዋ! አንድ ጊዜ የምታሳየው የቁጣ ገፅታ፣ ሶስት ሆነን አንሸከመውም፡፡ "እሺ" አልኩ፡፡ ምክንያቱም፣ በዚያ የልጅነት ዕድሜ የተቀረፀብኝ የ"እምቢታ" ትርጓሜው ግልፅ ነበር፡፡ "እንቢ" ማለት... በባሎች ዘንድ እንደጥፋት ተቆጥሮ በ"ሚስቶች" ላይ ለሚያደርጉት ያልታሰበ "ቅጣት" ምክንያት ይመስለኝ ነበር፡፡ (በዚህ ዘመን "ቅጣት" የሚለው ቃል "ጥቃት" በሚል ተቀይሯል፡፡)

የሚስትነት ሚናን ይዤ ስተውን፣ ትዕዛዝ መፈፀም የኔ ግዴታ ሲሆን ማዘዝ እና ማሽቆጥቆጥ ደግሞ የማኔ ስልጣን ነበር፡፡ ታዲያ በጨዋታ መሃል "ጎመን ገዝተህ ና፤ ደግሞ እነዛ መንገድ ዳር የሚቆሙ ሴቶች ካስቸገሩህ ፊት አትስጣቸው!" ብላ ታዘኛለች፡፡

የመንገድ ዳር ተሰብስበው የሚቆሙ የመንደራችን ወንዶች፣ ሴቶች ባለፉ ባገደሙ ቁጥር በነገር መተንኮስ (መላከፍ) ዋንኛው የአራድነት መገለጫቱ  ዛሬም ድረስ ቢቀጥልም፣ በማኔ ዘንድ ግን የተገላቢጦሽ ነው፡፡ ምንም ጨዋታው እቃቃ ቢሆንም፣ ምንም ጨዋታው ባልና ሚስት ቢሆንም… የዓለም ነባራዊ አካሄድ በማኔ ፊውራሪነት ተለውጧል፡፡ በተላካፊ  ሴቶች መግቢያ እና መውጫ አጥተው የተማረሩ ወንዶች እንደ አንዱ ሆኜ "ሴቶች እንዳይተናኮሉኝ" እየተጠነቀቀኩ የታዘዝኩትን ለመፈፀም መተወኔና ማሰብ በራሱ ለማኔ ያለኝ አድናቆት ይበልጥ ይንራል፡፡

የማኔ ባል መሆን እየተመኘሁ፣ ሚስቷ መሆኔን ያመንኩበትን ዓለም ምን እንሚመስል በምናቤ ለመሳል ሞከርኩ፡፡ "ማጅራት መቺ አለ፤ በጊዜ ልግባ…" ሲባል መስማት የተለመደ ነው፡፡ ዛሬም ድረስ ሴት ማጅራት መቺ አላውቅም፡፡ ሰው መጅራት መቺንም ሆነ ዘራፊን ሽሽት በጊዜ ቤቱ ለመግባት ከተጣደፈ፣ ከወንዶች ከሚሰነዘር አደጋ እራሱን ላለማጋለጥ ለመሆኑ ርግጥ ነው፡፡ እናም ወንዶች ለሁለቱም ፆታዎች የስጋት ምንጭ ናቸው፡፡

ከማኔ ጋር ከተዋወቅንበት ሶስት አስርት አመታት ተቆጠሩ። ያለጥርጥር ከ15 ዓመታት በኋላ ነው ያገኘኋት። አድራሻችንን አፈላልጋ እዚህ እንድንገናኝ በስልክ የቀጠረችን ራሷ ማኔ ናት፡፡ አቡቹና ፎርጃ እስኪመጡ እየጠበቅን ነው፡፡ ስለርሷ ያለኝ ግንዛቤ ባይለወጥም፣ አስተያየቴ ግን ተለውጦ ነበር። እንዴት አባቷ አምሮባታል?!? የሌለ ውስዋስ ለኳሽ ሆና ታየችኝ። የተሰማኝን ስሜት ግን ለመናገር አቅም አልነበረኝም። ምክንያቱም ፣ ማን እንደሆነች እድሜ ዘመኔን ሙሉ እንዳልረሳ አድርጋ ነግራኛለች።

ያቀራረበን እድሜ አራርቆናል፡፡ መልሶም አገናኝቶናል፡፡  እድሜ  የለወጠው ብዙ ነው፡፡ እቃቃ መጫወቻዎቻችን ተበትነዋል፡፡ በልጅነት የተጀመረው የባልና የሚስት ጨዋታ ይቀጥል አይቀጥል አይታወቅም…

"ሶስት ኪሎ ሙዝ በስስ ፌስታል…"

(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)

መገናኛ ድልድዩ ስር ሙዝ በቅርጫ ሞልተው የሚሸጡ ነጋዴዎች፣ "ሶስት ኪሎ ሙዝ አስር አስር ብር!" እያሉ ነበር።

ሙዙ ያስጎመዣል። ፞ጠ፞ቃ፞ጠ፞፞፞ቆ፞ የሚባለው አይነት ነው። አላስቻለኝም። ሶስት ኪሎ አስመዘንኩ። በነጭ ስስ ፌስታል አንጠልጥዬ ወደ ታክሲ ተራ አመራሁ።

ታክሲ ውስጥ እንደገባሁ ማምሻ ግሮሰሪ የማውቀውና በአንድ ወቅት ፈንጂ አምካኝ እንደነበረ የነገረኝን ጎልማሳ አገኘሁት። ከጎኑ ተቀመጥኩ። ሰላም ተባብለን ስናበቃ ወሬው ወደሙዝ ተቀየረና ስለጥቅሙ ያትትልኝ ጀመር።

"አሁን ወቅቱ የሙዝ ነው። ሙዝ አፕሬቲቭ ውስጥ የሚገባው ለሀንጎቨር እንደሆነ ታውቃለህ? ይገርምሃል፣ ሙዝን ለመጀመሪያ ጊዜ ለመብልነት ያዋሉት… "

ይህን ሁሉ ማብራሪያ እየሰማሁ ዝም ማለት ስላላስቻለኝ ሁለት ሙዝ አውጥቼ አንድ ሰጠሁት።  ወዲያው አቀለጣጥፎ ከበላ በኋላ ድገመኝ አይነት አስተያየት ሲመለከተኝ ጊዜ ሁለተኛውን ሰጠሁት።

"ይገርምሃል፣ ይህኛው አይነት ሙዝ ኦርጋኒክ አይደለም። ትክክለኛው ሙዝ ከነልጣጩ ነው የሚበላው…"

ይህ ሰው የሚቀደደው ሲጠጣ ብቻ ይመስለኝ ነበር። (ለነገሩ አሁንም ጠጥቶ ሊሆን ይችላል)
በዚህ መሃል ሂሳብ እየሰበሰበ ያለው የታክሲው ረዳት "እንብላ ባህል እኮ ነው" አለ። አንድ ሙዝ አውጥቼ ሰጠሁት። ሙዙን ተቀብሎ ዞር አላለም። ሂሳብ እንድንከፍል እየጠበቀ ነበር። አስር ብር አውጥቼ ሰጠሁት።

"የት ናችሁ? የሁለት ሰው ነው?" ረዳቱ ጠየቀኝ። ምንም ምርጫ የለኝም። እንኳን አብሮ ለጠጣ አብሮ ለበላም ይከፈላል።

ከታክሲው ስወርድ እንደ ተራ አስከባሪ ከታክሲ ተራ የማይጠፋው መኮንን ተቀበለኝ። የሰፈራችን ደላላ ነው።

"እሸት እና ቆንጆ አይታለፍም" እያለ ሙዙ ላይ አፈጠጠ። ላስቲኩን ከፈትኩለትና ሁለት አወጣ። (ማነበር ያ… "ሙዝ የፋብሪካ ውጤት መሆኑን ሳስበው ሁሌም ዲይንቅ ይለኛል" ያለው? )

ሙዙ እጄ ላይ እየቀለለ ነው። እኮ አሁንስ ተስፋዬ ማነው?! ጥቁር ላስቲክ አይደለምን?! ቀጥታ ወደሱቅ አመራሁ። ጥቁር ላስቲክ ልገዛ። የጀበና ቡና ደንበኛዬ ሱቁ ደጅ ላይ ቆማ አየኋት።

ፈገግታዋ ልዩ ነው። እኔንና በፌስታል የየሰዝኩትን ሙዝ አፈራርቃ እያየች…

ኦዉው…!!