2016 ፌብሩዋሪ 21, እሑድ

"ሶስት ኪሎ ሙዝ በስስ ፌስታል…"

(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)

መገናኛ ድልድዩ ስር ሙዝ በቅርጫ ሞልተው የሚሸጡ ነጋዴዎች፣ "ሶስት ኪሎ ሙዝ አስር አስር ብር!" እያሉ ነበር።

ሙዙ ያስጎመዣል። ፞ጠ፞ቃ፞ጠ፞፞፞ቆ፞ የሚባለው አይነት ነው። አላስቻለኝም። ሶስት ኪሎ አስመዘንኩ። በነጭ ስስ ፌስታል አንጠልጥዬ ወደ ታክሲ ተራ አመራሁ።

ታክሲ ውስጥ እንደገባሁ ማምሻ ግሮሰሪ የማውቀውና በአንድ ወቅት ፈንጂ አምካኝ እንደነበረ የነገረኝን ጎልማሳ አገኘሁት። ከጎኑ ተቀመጥኩ። ሰላም ተባብለን ስናበቃ ወሬው ወደሙዝ ተቀየረና ስለጥቅሙ ያትትልኝ ጀመር።

"አሁን ወቅቱ የሙዝ ነው። ሙዝ አፕሬቲቭ ውስጥ የሚገባው ለሀንጎቨር እንደሆነ ታውቃለህ? ይገርምሃል፣ ሙዝን ለመጀመሪያ ጊዜ ለመብልነት ያዋሉት… "

ይህን ሁሉ ማብራሪያ እየሰማሁ ዝም ማለት ስላላስቻለኝ ሁለት ሙዝ አውጥቼ አንድ ሰጠሁት።  ወዲያው አቀለጣጥፎ ከበላ በኋላ ድገመኝ አይነት አስተያየት ሲመለከተኝ ጊዜ ሁለተኛውን ሰጠሁት።

"ይገርምሃል፣ ይህኛው አይነት ሙዝ ኦርጋኒክ አይደለም። ትክክለኛው ሙዝ ከነልጣጩ ነው የሚበላው…"

ይህ ሰው የሚቀደደው ሲጠጣ ብቻ ይመስለኝ ነበር። (ለነገሩ አሁንም ጠጥቶ ሊሆን ይችላል)
በዚህ መሃል ሂሳብ እየሰበሰበ ያለው የታክሲው ረዳት "እንብላ ባህል እኮ ነው" አለ። አንድ ሙዝ አውጥቼ ሰጠሁት። ሙዙን ተቀብሎ ዞር አላለም። ሂሳብ እንድንከፍል እየጠበቀ ነበር። አስር ብር አውጥቼ ሰጠሁት።

"የት ናችሁ? የሁለት ሰው ነው?" ረዳቱ ጠየቀኝ። ምንም ምርጫ የለኝም። እንኳን አብሮ ለጠጣ አብሮ ለበላም ይከፈላል።

ከታክሲው ስወርድ እንደ ተራ አስከባሪ ከታክሲ ተራ የማይጠፋው መኮንን ተቀበለኝ። የሰፈራችን ደላላ ነው።

"እሸት እና ቆንጆ አይታለፍም" እያለ ሙዙ ላይ አፈጠጠ። ላስቲኩን ከፈትኩለትና ሁለት አወጣ። (ማነበር ያ… "ሙዝ የፋብሪካ ውጤት መሆኑን ሳስበው ሁሌም ዲይንቅ ይለኛል" ያለው? )

ሙዙ እጄ ላይ እየቀለለ ነው። እኮ አሁንስ ተስፋዬ ማነው?! ጥቁር ላስቲክ አይደለምን?! ቀጥታ ወደሱቅ አመራሁ። ጥቁር ላስቲክ ልገዛ። የጀበና ቡና ደንበኛዬ ሱቁ ደጅ ላይ ቆማ አየኋት።

ፈገግታዋ ልዩ ነው። እኔንና በፌስታል የየሰዝኩትን ሙዝ አፈራርቃ እያየች…

ኦዉው…!!

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ