መለያዎች

ልጥፎችን በመለያ መጣጥፍ በማሳየት ላይ። ሁሉንም ልጥፎች አሳይ
ልጥፎችን በመለያ መጣጥፍ በማሳየት ላይ። ሁሉንም ልጥፎች አሳይ

እሑድ 2 ፌብሩዋሪ 2020

“አብሾ “፥ “አፍልሆ”፥ መድሃኒት (ኄኖክ ስጦታው)



አለቃ ለማ ትዝታቸውን ለልጃቸው ለመንግስቱ ለማ(ለአብዬ መንግስቱ) ያጫወቱት ነው ፤ በመምህሩ አፍልሆ ስለተደረገለትና በቅኔ ተወዳዳሪ ስለሌለው አንድ ተማሪ ነው ጨዋታው። መምህሩ አለቃ ተጠምቆ ይሰኛሉ። የተማሪው ስም ሠረገላ ብርሃን የተሰኘ በኋላም የታወቀ የቅኔ አስተማሪ የሆነ ሰው ነው። አለቃ ለማ በጣፈጭ አንደበታቸው ለልጃቸው እየተረኩለት ነው።

“ተማሪያቸው ነው አፍልሆ አርገውለታል ይመስለኛል ተጠምቆ፥ መዳኒት ጸሎት በውሃ እሚደግም - ለቅኔ ብቻ አይደለ፤ ለዜማም ለመጣፍም እንዲያው ለሚጠናው ሁሉ ነው። በውሃ ስለተደገመ ነው አፍልሆ የተባለው. . . እገሌ ሰው ያህለዋል አይባልም ቅኔ በማሳመር - ቅኔው ሌላ ነዋ ባያሌው። ሲመራ! ወዲያው መምራት ነው። አራት ተማሪ አቅርቦ ይመራል የሚባለው እሱ ነው። መምህር ሆኖ፤ . . . እሱን እንዲህ ያደረገው አለቃ ተጠምቆ ናቸውና እኔም እንደሱ እሆናለሁ ብዬ ተነስቼ ሄድኩ ኸሳቸው። . . .” (መፅሐፈ ትዝታ ዘዓለቃ ለማ፤ ገፅ 79)

ስለ አብሾ (አፍልሆ) በቃል የተናገሩት ሊቀ ጉባኤ ፈቃደ ስላሴ ተፈራ ናቸው። አያሌ ጥያቄዎችን የሚመልስና ብዙ ጥያቄዎችን የሚያጭር መረጃ ሆኖ ለዚህ ዕሑፍ የጀርባ አጥንት ሆኖኛል። “በአገራችን የቤተክርስቲያን ምሁራን ዘንድ ትምህርት ይገልፃል፥ አእምሮ ይስላል እየተባለ በልዩ ልዩ ሁኔታዎች ተቀነባብሮ በተለያየ የእድሜ ደረጃ ላሉ ተማሪዎች የሚሰጥ መድሃኒት ሲሆን በተጨማሪ “ዘኢያገድፍ” እንዲይዝ የማይጥል፣ “መክሰተ ጥበብ” እና “መፍትሄ ሀብት” እየተባለ ይጠራል. . .” ሲሉም አክለውም ስለ አብሾ ምንነት ያብረራሉ።

ይህ ገለፃቸውን ለሚመረምር ሰው የአብሾን ጥቅም ከዕውቀት ገላጭ ከመሆኑ ጋር ብቻ እንዳልሆነ ይረዳል። የመጀመሪያው ደረጃ መድሀኒት “ዘኢያገድፍ” ተብሎ የተገለፀው በቤተክህነት ትምህርት ፊደለም ሆነ ቅኔ ለሚገድፉት የሚሰጥ ሲሆን የሚማሩትን በቃላቸው ቶሎ እንዲይዙ (እንዳይጥሉ) የማድረግ አቅም ያለው መድሃኒት እንደሆነ ግልፅ ነው። ሌላኛው “መክሰተ ጥበብ” የሚሰኘውም የቃላቱ ትርጓሜ እንደሚነግረን ጥበብ ገላጭ እንደሆነ ያመላክታል። ይህም ከዕውቀት አንድ ደረጃ ከፍታውን ወደ ጥበብ የሚያሳድግ መድሃኒት ነው።  ሶስተኛው “መፍትሄ ሀብት” ነው። ለነዋይ ማካበቻ ይረዳል ተብሎ የሚሰጥ መድሃኒት እንደሆነ ተረድቻለሁ።

[በተለይም የአብሾ አፍልሆ ለቅኔ ዘረፋ እድሜ ልክ የሚያነቃቃ አብነት ነው። እየተባለ ይጠጣል። በቃልም፥
ጠላ ያለጌሾ
ቅኔ ያለአብሾ . . . እየተባለ ይተረታል። አብሾ ሶስት አይነት ዝርያ ሲኖረው ጥቁር፥ ቀይና ነጭ ናቸው። ጥቁሩ በአገራችን በየትኛውም ቦታ በቅሎ የሚገኝ ሲሆን አስተናግር ተብሎ የሚታወቀውም ጥቁሩ ነው። (አብሾ የተሰጠው ተማሪ) . . . የሚነገረው ትምህርት የማይጠፋውና የሰማውን ነገር የማይረሳ ከሆነ ሆሳዕናው (መድሃኒቱ) ሰመረለት ይባላል። ካልሰመረለት የርኃወተ ሰማይ ቀን ጠብቆ እንደገና ይደረግለታል እየተባለ ይነገራል። (ርኃወተ ሰማይ የሰማይ መከፈት ነው) ይኸውም የሚሆነው በአመት አራት ጊዜ ሲሆን ጳጉሜ 3፥ ታህሳስ 13። የካቲት 4 እና ግንቦት ስምንት ቀን ነው። ]

ጥንታዊው የቤተክህነት መፅሐፍት መካከል፣ “ፅፀ ደብዳቤ” አንዱ ነው። በጥንታዊ አባቶቻችን በመድኃኒቶች ላይ የነበራቸውን ጥበብ በአውደ ነገሥት ላይ ሰፍረው ይገኛሉ። ከእነዚህም መድኃኒቶች ተራ ቁትር 56ኛው አብሾ (አብሶ) በሚል ስም ተጠርቷል። ስለሆሳእናው (መድሓኒቱ) ምንነት እና አድራጎት፣ በባህላዊና መንፈሳዊ ህክምና ጥበብ አማካኝነት ትምህርት ለማይዘልቀው ልጅ ሁነኛ መድሃኒት እንደሆነ እንዲህ ሲል ይገልፀዋል፦

[፶፮፤ አብሶ (ዕፀ ፋርስ አስተናግር) በበርኻ የበቀለ ነጩ ፍሬውን ደቍሶ በነጭ ሽንኵርት ብቻ በተደለዘ በርበሬ ሽሮ በነጭ ጤፍ እንጀራ እየፈተፈቱ መልክአ ኢየሱስን እየደገሙ ፯ ቀን ለክተው ለሕፃናት ቢያበሏቸው ትምህርት ከመ ቅጽበት ይገባቸዋል ፍቱን ነው። እንዲሁም ከመ ዘኢያገድፍም ፫ ቀን ጠዋት ጠዋት ማዋጥ ነው።]

ሊቀ ጉባኤ ፈቃደ ስላሴ ተፈራ ስለ መድሃኒቱ አዘገጃጀት ሰፋ ያለ ትንታኔን ሰጥተዋል።[“. . .የሚዘጋጀውም ከልዩ ልዩ እፅዋት ቅጠል፥ አበባ፥ ስርና ተቀፅላ በመሆኑ በማር ወይም ንፁህ ማር ወፍ ባልቀመሰው ውሃ (በጠዋት በተቀዳ ውሀ) በሞላ ብርሌ (በጥቁር ብርሌ) ውስጥ እስከ አንገቱ ውሃ ተሞልቶ ከተበጠበጠ በኋላ ለማፍሊያ የተዘጋጀ ፀሎት እየተፀለየበት አንድ ሱባኤ ይቆያል። እስከ ሰባት ቀን ይሰነብታል። ሱባኤው ሲያልቅ በሰባተኛው ቀን ተጠቃሚው ልጅ ወይም ደቀመዝሙር በባዶ ሆዱ ይጠጣዋል። ወዲያው እንደ ጠጣ ከሰው ተለይቶ ለሶስት ቀናት ብቻውን በአንድ ክፍል ውስጥ ይታቀባል/ ይቀመጣል። ከዚያም ለአንድ ሱባኤ ወይም ለሰባት ቀናት አልያም ለሰባት ሱባኤ ወይም ለአርባዘጠኝ ቀናት የተወሰኑ ምግቦችን እየበላ ማለትም የገብስ ቆሎ ፥ የገብስና የጤፍ እንጀራ በኑግ ጭማቂ በማጥቀስ እየበላና የኑግ ጭማቂ ብቻ እየጠጣ የሚያጠናውን ንግግር በማሰላሰል እንዲቆይ ምክር ይሰጠዋል። አደራረጉ የተለያየ ከመሆኑም በላይ የሚቀመሙትም እፅዋት እንደየመምህራኑ ጥናትና እንደየገቢሩ የተለያዩ ናቸው ይባላል. . .”]

መዛግብት ይህንን ቃል በምን መልኩ አንደፈቱት ተመልክቼ ነበር። አብሾ የመድሃኒት ስያሜ ሲሆን የተለያዩ አይነት አእምሮን አነቃቂ እፆች አማካኝነት ተቀምሞ ለመፍትሄነት ሲያገለግል የኖረ ጥንታዊ መድሐኒት እንደሆነ ይናገራሉ። ከኢትዮጵያ ውጪ የጥንት ስልጣኔ ግንባር ቀደም ተጠቃሽ በሆኑት ሩቅ ምስራቅ አገራትም ውስጥ ተመሳሳይ መድሀኒቶች እንዳሉ ይታወቃል። በቻይና፣ በሕንድ እና በጃፓን እውቀት ገላጭ፣ አእምሮን አብሪ የሆኑ ባህላዊና መንፈሳዊነትን ያጣመሩ ተመሳሳይ መድሃኒቶች እንዳሉ ጥናቶች ያረጋግጣሉ።

በቤተክርስቲያን ውስጥ ተወስኖ ስላለውና እንብዛም ጥናት ባልተደረገበት “አብሾ” ዙሪያ በቃልና በፅሁፍ ያገኘኋቸውን መረጃዎች ተቀነጣጥበውም ቢሆን ሰፍረው ይገኛሉ፤ ከነዚህም ውስጥ አለቃ ኪዳነወልድ ክፍሌ በመዕሀፈ ሰዋሰው አስተናግር ወይም ዕፀ ፋርስ አናግር አስለፍልፍ ስለሚሰኘው ዕፅ ምንነት ሲያብራሩ፥ ‘የቀመሰው ሰው ወደ ፊት የሚሆነውንና የሚያገኘውን ስለሚያናግር አስተናግር’ እንደሆነ ይጠቁሙናል።

ደስታ ተክለወልድ የአማርኛ መዝገበ ቃላት በተሰኘው መፅሐፋቸው ስለ ዕፁ
[ዕጠ፡ ፋርስ] ተመሳሳይ ሐሳብ አስፍረው አንብቤያለሁ። [የፍሬው ልብስ እሾህ ያለበት ተክልነት የሌለው የዱር እንጨት፤ ቅጠሉን በጎች ቢበሉት ራሳቸውን ያዞራል፤ ሰውም ቢቀምሰው ያሳብዳል። ባላገሮችም ዐጤ ፋሪስ ይሉታል። ይህ ሁለት አይነት እንጨት ባገዳ በቅጠል በፍሬ ልዩ ሲሆን ልብን በመንሳት ስለተባበረ ባንድ ስም ተጠራ። በካህናት ዘንድ ግን ሁለተኛው ከአንደኛው ተለይቶ አስተናግር ይባላል። ]

በቤተክህነት አካባቢ ያሉ አንድ አባት ስለ አብሾ ምንነት እንዲነግሩኝ ጠይቄ ነበር።  “ፍሬውን የቀመሱ ሁሉ ባለብሩህ አእምሮ ይሆናሉ። ትምህርት ገላጭ ነው። ትንቢትም ያናግራል። በጥንቃቄ ካልተደረገ ለእብደትና ለሞት የሚያበቃ ስካር ውስጥ ይጥላል” ሲሉ ሃሳቡን አጠናክረውታል። 
በተለምዶ አብሾ (አብሶ) ተብሎ የሚጠራው አንዱና ዋንኛው አድራጎታዊ መገለጫው ሲሆን አስተናግር ከተሰኘ ዕፅ ይቀመማል። አድራጎት አፍልሆ ተብሎ ይጠራል። በአንድ ቀን የሚፈላ አፍልሆ አለ ይባላል። የዚህም ቅመማ ከላይ እንደተገለፀው ሆኖ በተጨማሪም ዛጎል ተደቁሶ ይጨመርበታል። ዛጎል ፀሎት የሚደረግበትን መድሃኒት ቶሎ የማፍላት ሃይል ስላለው እለቱን እንዲፈላና እንዲገነፍል ያደርገዋል። እንደ ፈቃደ ስላሴ ተፈራ አባባል ከሆነ የዚህ አይነቱ አፍልሆ (ዛጎል የገባበት) ጥሩ እንዳልሆነ ሲነገር ሰምተዋል። ተማሪዎች ቅጠሉን አፍልተውና ከጤፍ እንጀራ ጋራ ፈትፍተው በቀመሱት ጊዜ አእምሯቸውን ለውጦ ማደሪያቸውን ያናጋል፤ ማርከሻውም የኑግ ልጥልጥ ወይም በሶ እንደሆነም ያምናሉ።

ቀዩ በቆላማ ቦታዎች አካባቢ በሚፈስ ወንዝና ወንዝ መጋጠሚያ ላይ ይገኛል። ነጩ አብሾ ከጎንደር በበሸሉና አባይ መጋጠሚያ በጎጃም በዚገም ወንዝና በአባይ መጋጠሚያ፥ በሸዋ በሙገርና በአባይ ወንዝ መጋጠሚያ ይበቅላል ሲሉ ፈቃደ ስላሴ ተፈራ ስለፍሬዎቹ አይነትና ጥቅም፣ ብሎም ጉዳት ጠቁመዋል። ከፍሬዎቹም ዓይነቶች ውስጥ ጥቅም ላይ የሚውሉት ቀዩ እና ነጩ ብቻ እንደሆኑ ይነገራል። አጠቃቀሙም የተለያየ ነው። አንዳንድ መምህራን ስለአብሾ መድሀኒት ሲናገሩ አብሾ ጠጥቶ ወይንም በልቶ እስከ አርባው ቀን አልክሆል መጠጥ መቅመስ ሰካራም ያደርጋል ይላሉ። ነገር ግን አርባው ቀን ካለፈ በኋላ አልኮል ቢጠጣም ምንም ጉዳት እንደማያስከትል ይናገራሉ። በተለይ አደራረጉን የማያውቁ መምህራንም ሆኑ ተማሪዎች ወይም ግለሰቦች አብሾ ጠጥተው ወይም አጠጥተው ወዲያው አልኮል ስለሚጋቱ ሰካራሞችና አልፈው ተርፈውም እብዶች ይሆናሉ።

“የአብሾ ነገር ሲነሳ አንድ ትዝ የሚለኝ ነገር አለ” ባሉት የሕይወት ገጠመኝ በሳቸው አንደበት እንዲህ ይተረካል፦
[በ1953 ዓ.ም በነሀሴ ወር በጎጃም ክፍለሀገር በደጋ ዳሞት አውራጃ ዋሸራ የቅኔ ትምህርት ቤት በነበርኩበት ጊዜ 3 ሰዎች አብሾ ሲጠጡ ጠብቀን ብለው እኔንና ጓደኛዬን ዛሬ የቅኔ መምህር ማሞ ሀብተ ማርያምን ከዋሸራ በግምት 15 ኪሎሜትር ርቆ በሚገ/ነው በአካባቢው ሰው በሌለበት በዮሀንስ ገዳም ወስደውን በአንድ ሰፊ ደጀ ሰላም ውስጥ ገብተን ሳለ ቀኑ መሸት ሲል አብሾውን በስንዴ ዳቦ ጋግረው ሶስቱም ከበሉ በኋላ በሩን በጥብቅ ዘግተን ፀሎት ጀመሩ። ከዚያ ፀሎቱን እየፀለዩ ለሁለት ሰአት ያህል እንደቆዩ አንዱ እሪ፥ እንሽሽ ያለንበት ቤት ተቃጥሏል አለና ውሸቱን አስተጋባ። ወዲያው ለመሸሽ ከግድግዳ ጋራ እየተላተመ ስለአስቸገረ እኛ እና ሁለቱ ያልሰከሩ ጓደኞቹ ከአንድ ወጋግራ ላይ በገመድ አሰርነው። ወዲያው ሁለተኛው ተማሪ አንዳንድ ትንቢት ብጤ ሲናገር ቆይቶ “ሸማ ስራዬን አላሰራ አላችሁኝ፥ ቁቲቴን ስጡኝ” እያለ ስላስቸገረን እንደፊተኛው ከአንድ ወጋግራ ላይ ሸብ አደረግነው። ወዲያው የቅዳሴ ዜማ እንደጀመረ አንቀላፋ። ሶስተኛወ ግን ስካር እንደጀመረው “ተው ና ውረድ ቡሬ” እያለ የአራሽ መሰል ንግግሩን ጀመረ። ከዚያም ቀጥሎ
የበሬው ውለታ ይገለፃል ማታ
እብቁ በግርግብ ውሃው በገበታ።
እያለ ሲያዜም ቆይቶ እንቅልፍ ወሰደው። ከዚያ በኋላ መጀመሪያ የሰከረው ሰው የቅኔ ዘረፋውን ቀጥሎ ዶሮ እስኪጮህ የጀመረ እስኪነጋ ድረስ እጅግ በጣም ብዙ ቅኔ ድርሰቶችን ሲደርስ አድሯል።

ከዚያ በኋላ ሶስቱ እንቅልፍ ወስዷቸው ቀኑን ከዋሉ በኋላ ሌሊቱን አድረው በሶስተኛው ቀን ሙሉ አእምሯቸው ተመልሶላቸዋል፥ አንዳንድ ጊዜ ሲገላበጡ እየጠራን እህል ውሃ እነዲቀምሱ ስንጠይቃቸው በጣም ይበሳጩ ነበር። የታሰሩትን ፈትተን ልብሳቸውን ሲጥሉ እያለበስን አስተኝተን ተራ በተራ ያለምንም ድንጋጤ ስንጠብቅ ሰንብተናል። ከዚህ ውስጥ አስገራሚው ሁኔታ ሰካራሞቹ እኛን ለመደብደብ አልሞከሩም። ስንቆጣቸው ቶሎ ደንግጠው ትእዛዛችንን ይቀበሉ ነበር።]

ማክሰኞ 5 ጁላይ 2016

"አምስቱ ሞኞችና ሌሎችም ታሪኮች…"

(ኄኖክ ስጦታው)

‘ሙሽራው በዘገየ ጊዜ ሁሉም እንቅልፍ ተጫጫናቸውና ተኙ።’
(የነቁት ግን ይህን  ለማንበብ ችለው ነበር)

ከአሥሩ ደናግላን መካከል አምስቱ ሞኞች ናቸው። አምስቱ ግን አንድ። አምስት ደናግል ብልሆች አንድ ብርሃንም ለመፍጠር መዘጋጀታቸውን የተመለከተ የዚህ ዘመን "አዛዥ" እንዲህ ሲል ሰማሁት፦

‘ለአንድ ኩራዝ አምስት ሰው ምን ያደርጋል?! አራታችሁ ተመለሱና ከአምስቱ ጎን ቁሙ!! ብርሃን ለመለኮስ አንድ ሰው ይበቃል!!! ዳይ!!!’

የተባረሩት አራቱ ብልሆችም፣ አምስቱን ጅሎች አስተባብረው ስሞታ ለማቅረብም ወደመምህራቸው አቀኑ። እንዲህ ሲሉ ጠየቁ፦

‘ጌታ ሆይ፣ ተርበህ ወይስ ተጠምተህ ወይስ እንግዳ ሆነህ ወይስ ታርዘህ ወይስ ታመህ ወይስ ታስረህ መቼ አይተን ሳናገለግልህ ቀረን?’

እርሱም ተናገረ። በርግጥ መልሱ ግልፅ ቢሆንም፣ ማንም አልሰማውም ነበር።  

‘ታዲያ ለምን ትጠይቁኛላችሁ? እኔስ ብሆን ያደረኩት ይህንኑ አይደል?!…’ 
☆   

ነገሩ እንዲህ ነው። አንድ የግብረ ገብ መምህር የዳርት ውድድር አዘጋጀ። ለተማሪዎቹ። ዳርቱ ነጭ ወረቀት ተለብጧል። ኢላማውን በነጩ ወረቀት ላይ የሚስለው እራሱ ተወዳዳሪው ነው። ለምሳሌ፣ በነጭ ወረቀት የተለበጠው ዳርት ላይ  የሚጠላውን ሰው ስም ይፅፋል። የፃፈውን ስም በፍላፀው አነጣጥሮ ከመታው ‘ጥላቱን ’ እንደተበቀለ ያህል ይረካል ።

ውድድሩ ከመጀመሩ በፊት ሁሉም ተማሪ  የራሱን ጥላቻ ለመውጋት ኢላማ ይሆነኛል ያለውን ታናናሽ ምልክቶችን በዳርቱ ላይ አኖረ ። ኢላማውን ለመውጋት አነጣጥረው የወረወሩት ሁላ የራሳቸውን ኢላማ ባይመቱም እንኳን፥ በስህተት የሌሎችን ኢላማ ክፉኛ ወጋግተውት ነበር።

እናም በመጨረሻ፣ የዳርቱን መጫወቻ የሸፈነው ነጭ ወረቀት ሲገለጥ የኢየሱስ ምስል ክፉኛ ተወጋግቶ ለሁሉም ታየ። ይህን ያደረጉት የግብረ ገብ  መምህሩ ነበሩ።

የራሱን ኢላማ  ለመምታት አነጣጥሮ የወረወረው ተሜ ሁላ እንዲህ የሚል ንግግር ከመምህሩ አንደበት ተላለፈለት፦

‘እውነት እላችኋለሁ፣ ከሁሉ ከሚያንሱት ከእነዚህ ወንድሞቼ ለአንዱ ያደረጋችሁት ሁሉ ለእኔ እንዳደረጋችሁት ይቆጠራል’
በሌላ ጊዜ፤ 

ሁለት አማኞች ስለ ሃይማኖት እያወሩ ነበር።

አንደኛው ለሌላው፣ "አንዳንዴ ፈጣሪን… ለምን ድህነት፣ ረሃብ፣ ኢፍትሐዊነት… በአለም ላይ ሊያስወግድ እንዳልቻለና የሆነ ነገር እንዲያደርግ በፀሎት ብጠይቀው እወድ ነበር።" ሲለው ሁለተኛው አማኝ ተገርሞ ፦

"ታዲያ እንዳትጠይቀው ምን አገደህ?!" ሲል ይጠይቀዋል ።

እናም፣ የመጀመሪያው አማኝ እንዲህ ሲል መለሰ፦ "አምላክ ፤ እነዚህኑ ጥያቄዎች እኔኑ መልሶ እንዳይጠይቀኝ ሰግቼ ነዋ!" 
።።።።።።።።።።።።።።

እኔም ይህን አልኩኝ፦

‘ከዚህ በኋላ የምትጠይቀኝን መልሼ እጠይቅሃለሁና ስትጠይቀኝ ተጠንቅቀህ  ጠይቅ!’

*መነሻ ሃሳብ (ማቴዎስ 25…)

ሐሙስ 26 ሜይ 2016

"የለ_ዓለም"

(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ) 

"ከዚህ ቀደም በሰው ልጅ በማንም ያልተሞከረ አዲስ ሃሳብ እና የአፃፃፍ ስልት እውን አለ?"

የአጻጻፍ ቅርፅ ሃሳብ የማስተላለፊያ መንገድ ነው። የስነጽሑፍ አላባዊያን የተውጣጡት፣ ከተለያዩ ቀደምት ፀሐፍት ስራዎች ተወራራሽ መዋቅረ ውጤት (ውበት) አንፃር መሆኑም የሚያሳየው ይሄንኑ ነው። 

ይነስም ይብዛ፣ እያንዳንዱ ሰው በተመሳሳይ ሃሳብ ላይ በተመሳሳይ መንገድ ንፅረተ—ዓለምን ለመግለፅ ቢሞክር አንዳች ልዩነት አያጣውም። kahlil gibran "jesus the son of man" ላይ ሃሳቡን ለማስተላለፊያነት ከተጠቀመበት ቅርፅ በዋንኛነት ሊገለፅ የሚችለው ተፅፎ ያነበበውን ታሪክ መድገም ወይም መተንተን አልነበረም። በአንፃሩ ግን ተፅፎ በነበረው ውስጥ ጥያቄ ጭሮበት ያለፈውን ታሪክ እስከ ምናቡ ጥግ አሰላስሎና ጥያቄ ለነበረው መልስ ሰጥቶ፣ ወይም፣ መልስ ለነበረው ታሪክ አንዳች መጠይቅ በመቀመርና ተጨማሪ ታሪክን በማዋቀር ላይ የተመሰረተ አጻጻፍ ስልት ነበር የተጠቀመው። 

ሌሎች ፃህፍት በርሱም ሆነ የፈጠራ ስራዎቹ ላይ "ተፅእኖ" እንዳላሳደሩ የሚናገሩት ውስጥ አዳም ረታ ተጠቃሽ ነው። ታዲያ መንገዱም ሆነ (እውነቱ) ከ"ከየት መጣ" ጥያቄ "እከሌ" ተብሎ የሚጠቀስ ተዛማጅ አካል አለመኖር አይደለም። በምን ወጣ እንጂ።

የፍቅር እስከ መቃብር መጽሐፍ እና ታይታኒክ ፊልም ታሪካዊ መዋቅራቸው ተመሳሳይ ነው ማለት፣ የታይታኒክ ፊልም በፍቅር እስከ መቃብር መፅሀፍ ላይ ተፅእኖ አሳድሯል ማለት ነው? 

ችግሩ የተዳቀሉ ቅርፆች ስርወ ምንጭ፣ እከሌ የሚባል አንድ ሰውን ለማመሳከር ከአለመቻል ይወለዳል። ይህ ውስብስብ "ወጥነት" ሳይሆን በግልፅ ቃል ‘ቅይጥነት’ ነው። ቅይጥ ውጤት ደግሞ በቀያጭ ግብአት ተፅእኖዎች ሊያመልጥ አይቻለውም። 

አዲስ ቅርፅ ከየት ተወለደ ጥያቄን ፍፁም የሚያደርገው ሐቅ ግን አለ። ሃሳብን (ጭብጥ) እንደ ፅንስ፣ ውልደቱንም እንደ ውበት (ቅርፅ) ብንወስደው የውሻ ልጅ ቡችላ…ነው፤ የቡችላስ አባቱ ማነው?! ያስረገዘው ነው ወይስ ያደረገው?! የቡችላ አባቶች ብዛት፣ የእናቱን ማንነት ከጥርጣሬ ላይ አይጥልም። 

የሐሳብ ምንጭም ሆነ ድርቅ፣ ሰው ነው። ምልከታ የማንም ሆነ የምንም፣ ከአንድ ገበታ አብረው እንደተመገቡ ሁለት ሰዎች ይመሰልብኛል። 
አበላሉ እንዳለ ሆኖ አወጣጡ ላይ ግን ብዙ ልዩነት አለ። 

አዲስ መንገድ ሆነ አዲስ ሃሳብ "የለ_አለም!"

ቅዳሜ 21 ሜይ 2016

ለምን አልስቅ?!

እስቃለሁ!
(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)

የክልከላ እና የተግሳፅ ህግ ተሸብበን ሳቅ አልባ ሆንን። የሳቅ መንስኤዎች በሙሉ ከጊዜ ወደጊዜ እየተመናመኑ መጡ። ሳቅ አጠር ሆነን የሚስቁትንም አሳቀቅን። የሚያስቀው አያስቀንም። ለቀልድም ሆነ ጨዋታ መራር ትርጉም ፍራቻ ቁጥብ ሆንን። የክልከላ ህግ ለስሜት ቅድመ ሳንሱርነት ተሹሞ በላያችን ላይ ሰለጠነ። ስሜት ፈንቅሎት እንዳይወጣ በሳቃችን ላይ ከመርግ የከበደ ጭፍግ ቆለልንበት።

የሚስቅና ሌሎችን ለማሳቅ የሚወድ እንደ "ተራ ቧልተኛ" ተቆጠረ። መሳቅም ሆነ ማሳቅ ከበደ። ለአሳሳቅ ስልት ተበጀለት።

እንዴት እንደማይሳቅ የሚመክሩ ጭፍግ መካሪዎች በዙ። ሳቃቸውን አፍነው የሚወቅሱ በዙ። በፍራቻ ተሸብሸው የሚገስፁ በዙ። በይሉኝታ ታፍነው ፊታቸውን የሚጨፈግጉ በዙ። በንዴት ቱግ ብለው የሚንጨረጨሩ በዙ። "አያስቅም" የሚሉ በዙ።

ሳቅ ጠፋን። አሳሳቅ ጠፋን። ከአዘኑት በላይ ያዘንን መሳይ፣ በሚስቁት ላይ የምንበሳጭ…  የተውሶ ፊቶች ጥርቅም ሆንን። ሳቅ ጠፋን! አሳሳቅ ጠፋን። በላያችን ላይ እንዴት እንደሚሳቅ የሚያስተምር ትምህርት ቤት ተከፈተ።

እናም ዛሬ ከዚህ በታች ያለውን ቀልድ ከአመት በኋላ ድጋሚ ሳነበው በድጋሚ ሳቅኩ።

————
አንድ ሰሞን በአንድ አገር ዋና ከተማ ውስጥ ብዙ የጦር መሳሪያ ስለጠፋ የቤት ለቤት ፍተሻ ተጀምሮ ነበር፡፡ ሁሉም ተፈትሾ፣ ተፈትሾ ጳጳሱ ቤት ይደረርስና እዛ ገብተው ሁሉንም ክፍሎች ፈትሸው ምንም ስላልተገኘ በስተመጨረሻ እሳቸው ወደ ተቀመጡበት ሄደው ሲፈትሹ በጣም ብዙ መሳሪያ ያገኛሉ፡፡ ፈታሾቹም ተገርመወው፡-

“ይሄን ሁሉ መሳሪያ ከየት አገኙት?” ብለው ሲጠይቋቸው ፡-

“ሚኒስትሩ በስለት ያስገባው ነው”

ዓርብ 20 ሜይ 2016

ቆይታ (ከቀብር አስፈፃሚዎቹ ጋር)


☞ኄኖክ ስጦታው

ለሞት ያለኝ ግንዛቤ ግልፅና አጭር ነው። ሞት እድገት ነው፤ መወለድም እድገት። "የሰው ልጅ ከሞት በኋላ ያለውን ካለማወቅ ፍራቻ አያሌ መሸሸጊያ ፈጥሯል" ያለው ዲካርት መሰለኝ ።

ጓደኞቼ "እንሳለም" ብለው ሚካኤል ቤተክርስቲያን ጋር መኪናዋን አቆሙ።"ዛሬኮ አርሴማና ተክልዬ ይነግሳሉ፤ አትሳለምም?"

"አልሳለምም፤ እናንተ ደርሳችሁ እስክትመጡ ቀብር አስፈፃሚዎቹ መደብር ውስጥ እጠብቃችኋለሁ።"

ወደ ሬሳ ሳጥን መሸጫና ማደሻ መደብር አመራሁ። ብዙ አይነት የአስክሬን ሳጥኖች ተደርድረዋል። ሁለት አይነት አበቦች (በወረቀት ተሰርተው ቀለም የተነከሩ እና ከበቀሉበት የተዘነጠፉሸአበቦች) ደጃፉ ላይ አየሁ። ፊትለፊት ሆነው እይታዬን ያልሳቡት ለምን ይሆን? ስልኬን አውጥቼ ፎቶ ማንሳት ጀመርኩ።

ሰዎች እንዳላዩ ሆነው ከሚያልፏቸው ነገሮች አንዱ እንደዚህ አይነት መደብሮችን ነው። መደብሩ በራፍ ላይ አበቦች አሉ። ከአበቦቹ በላይ ያሉት በላይ በላያቸው የተደራረቡ ሳጥኖች ግን አበቦቹን ጋርዷቸዋል። አ አ!  አይደለም። አስክሬን ሳጥኑ ከፊት ካልሆነ በቀር አበቦቹን እንዴት ከዕይታ ሊጋርዳቸው ይቻለዋል?

"ሄይ፣ ፎቶ ማንሳት ክልክል ነው!" የሚል ድምፅ ሰማሁ። ሁለት ወጣቶች ወደኔ መጡ።

ፎቶ ማንሳት ክልክል መሆኑን የሚገልፅ ምንም ምልክት የለም። ለምን ክልክል እንደሆነ ጠየኩ።

"የአስክሬን ሳጥኖቹ ዲዛይን ይሰረቅብናል። አይቻልም።"

"የሳጥኑ ዲዛይን ከሌላው በምን እንደሚለይ ማወቅ እችላለሁ?"

"የማትገዛ ከሆነ ብነግርህ ምን እጠቀማለሁ?"

"እኔ ባውቅ ምንስ የምታጣው ነገር አለ?"

"ለምንህ ነው ማወቅ የምትፈልገው?" ሲል ሌላኛው ጠየቀኝ።

"በቃ፣ ደስ ይለኛል። ሳጥኖቹን በቅርብ ሆኜ ባይ፣ አብሬያችሁ ውዬ ቀብር ባስፈፅም ደስ ይለኛል። በተለይ ከሳጥኖቹ መሐል የማስታወሻ ፎቶ ብነሳ… ደስ ይለኛል" አልኩ። እውነቴን ነበር።

እርስ በራሳቸው ተያዩና ፈገግ አሉ። ወደ ውስጥ እንድገባ ፈቀዱልኝና ትልቅ አልበም እንድመለከት ጋበዙኝ።
ለጨዋታ መጀመሪያ ያክል "ስራ እንዴት?" አልኩ።

"እግዚአብሔር ይመስገን"
(ምሥጋና ጥሩ ነው) 😱

የሚያምር የሬሳ ሳጥን አየሁና ዋጋውን ጠየኩ፦

"12ሺ ብር።" አለ።

"ዋጋው እንደዚህ የተወደደበት ምክንያት ምንድነው?"

"በኤምዲኤፍ ነው የተሰራው። እንደምታየው የሳጥኑ የላይኛው ክፍል ሙሉ መስታወት ነው። አስክሬኑ በሱፍ ሽክ ተደርጎ ይገነዛል።"

"ዋጋው አስክሬኑ የሚለብሰውን ሱፍ ጨምሮ ነው? "

"ልብሱን ቤተሰብ ነው የሚያዘጋጀው።"

"ለሴቶች ሲሆንስ?"

"አይቀንስም"

ሳቅኩ።
"ዋጋውን አልነበረም የጠየኩህ። አስክሬኑ የሴት ከሆነ ምን አይነት ልብስ ነው የምትገነዘው?"

እርስ በራሳቸው ተያዩ። መቼስ ሱፍ አያለብሱ።
ሁለተኛው መለሰልኝ፦
"የአገር ባህል ልብስ ሊሆን ይችላል። እነዚህ ባለሙሉ መስታወት ሳጥኖችን ግን እስካሁን የተጠቀምነው ለወንዶች ነው።"

"የአሜሪካ ሳጥንም አለን።" አለ ሌላኛው።

"የትኛው ነው?"

"እዚህ የለም። አልበሙ ላይ ላሳይህ…።" አልበሙን ተቀብሎኝ ገለጥ ገለጥ አድርጎ "ይኸው!" አለ።

ያምራል።

"ዋጋው ምን ያህል ነው?"

"35 ሺ ብር"

"እ?"
ደገመልኝ። በሰላሳ አምስት ሺህ ብር የ1972 አዲስ ብራንድ አፍሮ ቮልክስ መሸመት የሚችል ብር እንደሆነ አሰብኩት። የገረመኝ ግን ሌላ ነበር፦
"ሳጥን አስመጪ አለ ማለት ነው?"

"አስመጪ የለም። ከአሜሪካ አስክሬን ይመጣበትና የአገር ውስጥ ሳጥን ላይ ብር ጨምረን ከቤተሰቦቹ ላይ እንገዛዋለን።"

"እዝጎ!" (አልኩ በውስጤ)

ዓርብ 6 ሜይ 2016

ልዩነቱ ግልፅ ነው

ዮናስ ጨርጨር ስጋ ቤት ምሳ ልበላ ገብቼ ሳለ…ቴዲ አፍሮ ፊት ለፊቴ ካለው ጠረጴዛ ላይ ተቀምጦ ሥጋ እየበላ ነው።
ልዩነታችን አሰብኩት።
ግልፅ ነው!
እኔ ስጋ ቆራጩን አውቀዋለሁ፤ እሱን ግን ስጋ ቆራጩ ያውቀዋል 

ረቡዕ 2 ማርች 2016

ጥያቄ ጥያቄ ጥያቄ

አንዳንዴ፣ ራሴን እንዲህ ስል እጠይቀዋለሁ፦
ሰፊውን አለም  ማን አጠበበው?

እውነት ጀግና ማለት ለአገሩ የሞተ ነው?  የገደለ?

ለአገር መሞት ማለት፣  በሌላው መገደል ብቻ ነው? ወይስ መግደል?

የመሞት ዓላማው ከመግደል በመጠኑም ቢለይም ስንኳን ፣ ሰውን ያክል አምሳያ መግደል በርግጥ ጀግነት ነው?  ወይስ አረመኔነት? ወይስ ተፈጥሯዊ የሆነ የማንነት መገለጫ?!

ለአገር መሞት ነው ጀግንነት? ወይስ ፣ በሰው መገደል ነው ጀግንነት?!

እራሱ «ጀግንነት» ምንድነው?!

ክብር ነው?
ስሜት ነው ?
ወይስ
ሌላ?

ጀግና ማለት፣ ላመነበት አላማ የተገደለ ነው?! ወይስ… የገደለ?!

ገድሎ የሞተው ፣ ሞቶ ካሸነፈው የሚለየው በምንድነው?
በሕይወት?
በሞት?
በድል?
በሽንፈት?

. .
.
.
.
.
.
.
.
. .
ከጦርነቱ የተረፈ በርግጥ ጀግና ነው ?!

.
.
በርግጥ የቱ ነው ጠባብ?!

አገር ከዓለም ይጠባል?!

ዓለም ከአገር ይሰፋል?!

አስፍቶ ለተመለከተው በርግጥ ዓለም የአገር አካል ናት? ወይስ

ዓለም ከሰፈር ትጠባለች?!

እናም፣ ጥያቄው ማብቂያ የለውም። መልሱ ግን ይብሳል¡

እሑድ 28 ፌብሩዋሪ 2016

የ“ሸኖ ቤት ሃሳቦች”

‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬የ“ሸኖ ቤት ሃሳቦች”
(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)

‪‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬
የ“ሸኖ ቤት ሃሳቦች” የማንበብ ሱስ የተጠናወተኝ ሁለተኛ ደረጃ ተማሪ ሳለሁ ነበር፡፡ በርግጥ ብዙዎቹ ሃሳቦች በጨዋ ቋንቋ “ፀያፍ” ተብለው የሚነገሩ ቢሆንም ብሶትና ምክርን በጨዋ ገለፃ የሚቀርቡ ሃሳቦችም አይታጡም፡፡ ያም ሆኖ ሕዝብ የሚጠቀምባቸው መፀዳጃ ቤቶች ስገባ በግድግዳው ላይ የተጻፉ ጽሑፎችን ማንበብ ያዝናናኛል፡፡

ሸኖ ቤትን ለመውደድ የፎክሎር ተማሪ መሆን አይጠይቅም፡፡ ከማይረቡ መፅሐፍት የተሻለ ምልከታን እና ሂዩመርን በሸኖ ቤት ሃሳቦች መቃረሜ በራሱ ለመፀዳዳት የማባክነውን ጊዜ የሚክስ ቁምነገር አላጣበትምና፡፡

“የዘርሲዎች ፍቅር” የተሰኘው ልቦለድ መፅሃፍ ላይ አንድ ገፀባሕርይ አስታውሳለሁ፡፡ በተለይ መፀዳጃ ቤት ስገባ ብዙ ጊዜ ትዝ ይለኛል፡፡ (አብሮኝ ይገባል - - ብል ይቀላል፡፡) ይህ ሰው ቁምነገርን የሚቃርመው ከመፀዳጃ ቤት ነው፡፡ ግድግዳ ላይ የሚጻፍ ግራፊቲ አልነበረም የሚያነበው፡፡ ሰዎች “ካካቸውን” የጠረጉበትን ወረቀት ሰብስቦ ኪሱ በመክተት እና በማንበብ ነበር፡፡

እነዚህ የግድግዳ ላይ ጽሁፎች ስለምንስ ይጻፋሉ? ግባቸው ምንድነው? ... ምክንያቱን እርሱት፡፡ ከየት መጡ የሚለው ምርምር አያሳስበኝም፡፡ ባለቤት አልባነታቸው በራሱ በቂ ምክንያት ነው፡፡ ምክንያት ከስም ይጀምራልና፡፡ ማንነቱን ለማወጅ የመፀዳዳት ባህሉን አደባባይ ላይ ከሚፈጣጥም ሰው ምንም አልጠብቅም፡፡ ማንነቱን በመጸዳጃ ቤት ግድግዳ ላይ የሚያሰፍር ማንነቱ ያልታወቀ ሰው ግን ታዳሚ ነኝ፡፡ (እስቲ ዛሬ የተመረጡ ትውስታዎቼን በሹካ ጨልፌ ላካፍላችሁ፡፡)

ለመጀመሪያ ጊዜ ካነበብኳቸው ውስጥ የሚመደብ የመፀዳጃ ቤት ሃሳብ እንዲህ የሚል ነበር፡-

“God is dead!” -Nietzshce
“Nietzshce is dead!” -God

ያኔ ይህን ሳነብ ያልገባኝ ብዙ ነገር ነበር፡፡ በርግጥ ኒቼ “እግዚአብሔር ሞቷል” በሚለው ግንዛቤው ዛሬም ድረስ (ሞቶም) ያወዛግባል፡፡ በሕይወት በነበረበት ጊዜ “እግዚአብሔር ሞቷል ፤ ሰዎችም ነፃ ወጥተዋል...” እያለ መስበኩን የተረዳሁትም ከጥቅሱ በኋላ ነበር፡፡ አመታት አልፈው፡፡ የኒቼን ሞት ጠብቆ እግዚአብሔር እንዲህ ማለቱን ግን መፀዳጃ ቤት እንደ ትንቢት ቀድሞ አሳውቆኛል፡፡ ጥበብ ከጲላጦስ መፅሐፍ ላይ ይህን ጥቅስ ሳነበው አልደነቀኝም፡፡ ጥቅሱን ሲያስታውሰኝ ግን የሆነ ነገር ግን ሸቶኝ ነበር፡፡ ያም ጠረን፣ ይህን አባባል ያነበብኩበት መፀዳጃ ቤት አጉል ጠረን ነበር፡፡

በአንድ ኮሌጅ መጸዳጃ ቤት ውስጥ ያነበብኩት ደግሞ እንዲህ የሚል መልዕክት ግድግዳው ላይ ተፅፎ አነበብኩ፡- “ምን ግድግዳው ላይ ታፈጣለህ!? አርፈህ አትፀዳዳም!?” ሆሆሆ... ሰዉ ጨምሯል!

በሌላ ዩኒቨርስቲ መፀዳጃ ቤት ውስጥም እንዲህ አይነት ትዕዛዝ አጋጥሞኝ እንደነበር አልረሳውም፡፡ በደቃቅ ጽሑፍ የተጻፈ መልዕክት ከመጸዳጃው በር ላይ ሰፍሮ አየሁና ከቅምጤ በመጠኑ ብድግ ብዬ ላነብ ስሞክር ያገኘሁት መልዕክት አስደንግጦ “የሚያስቀምጥ” ነበር፡፡ሃሳቡ እንዲህ የሚል ነበር፡- “ሰው ማለት አንተ ነህ፡፡ አሁን ወደነበርክበት ተመልሰህ አርፈህ እራ! ” የሚል ትዕዛዝ ፡፡

የሸኖ ቤት ግድግዳ ላይ ከተፃፉ ሃሳቦች ሌላው የማርከኝ እንዲህ የሚል ነው ፡-

“ቺክህን ጥሩ ነገሮች እንዴት እንደምታሳያት በማሰብ አትጨናነቅ፡፡ አሁን እየጣልክ ያለውን እንቁላል ግን ጠብሰህ እንዳታበላት አደራ! ስትጨርስ ውሃ ድፋበትና ከሌሎች እይታ ሰውረው!”

የሸኖ ቤት ግድግዳ ሃሳቦች አንዳንዴም ፍልስፍና ይቃጣቸዋል፡፡ በአንድ የሕዝብ መፀዳጃ ቤት ውስጥ ያነበብኩትሃሳብ ለዚሁ ምስክር ነው፡፡ እንዲህ ይላል፡-

[“መኖር ማለት፣ በምታባክነው ጊዜ የምታጣው ብኩንነት ነው፡፡ ለመኖር ስትል ከምታባክናቸው ሰዓታት ትልቁን ቦታ የሚይዘው ምን እንደሆነ ታውቃለህ?”

“አውቃለሁ” ካልክ ተሳስተሃል! በዚህ ሰዓት ማራት አልነበረብህም!!”]

ትውስታዬን ተደብቄ በተጠቀምኩበት የሴቶች መጸዳጃ ቤት ግድግዳ ላይ ባነበብኩት ልቋጭ፡፡

“በወንዶች ከሚነገሩ ብ-ዙ ውሸቶች መሃከል የማላምነው “ሮም በአንድ ቀን አልተገነባችም” የሚሉትን ብቻ ነው፡፡”

ማክሰኞ 23 ፌብሩዋሪ 2016

በቮልስ ያጉረመረምንበት ሰርግ ትዝታ

ይህ ትዝታ ይደንቀኛል። ጋራጅ የተዋወቅኩት ሰው ሰርግ ላይ መላው የቮልስ ባሉካዎች በአጃቢነት ተጋብዘን ነበር። አጃቢ መኪኖች በጠቅላላ ቮልስ ዋገን ናቸው። እውነት ለመናገር በአገሪቱ ውስጥ ካሉ ሾልሶች አንድም የቀረ አይመስልም።

ሰርጉን ለማሳመር  አጃቢ የሆኑት ቮልሶች ራሳቸው በመካኒክ ታጅበው ነበር። በቮልስ የሚታጀብ ሰርግ ያለመካኒክ የማይታሰብ ነበር። (መካኒኮቹ መንገድ ላይ ለሚበላሽ መኪና ፈጣን ጥገና እያደረጉ ጉዞው ቀጠለ።)

ታዲያ ያኔ መናፈሻ ውስጥ የነበረ አሙቁልኝ አዝማሪ እንዲህ ብሎ ፈተለ፤

"ጉርምርሜ ና ጉርምርሜ
ያሆ በሌ፣ ያሆ በሌ ፣ ጉርምርምርምርም…
ባባው ቮልስዬ ፣
ያሆ ቮልስዬ፣ ያሆ ቮልስዬ… ጉርምርምርምርምርም… (ተቀብለን አስተጋባን)
አዝማሪው ቀጠለ፦

ሚስቱን  ያገኘው…
ያሆ በሌ…  ያሆ በሌ… ጉርምርምርምርምርም…
ጉርምርሜ በግሩ ሲያዘግም!"

(ይህኔ የምር አጉረመረምን)

ሰኞ 22 ፌብሩዋሪ 2016

ሠአት ሠሪው

(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)

ሠአት ሠሪው ደጃፍ ላይ ቆሜያለሁ። ከውጭ ሆኖ ለሚመለከት ሰው ምንም የሚማርክ ውበት ላትመለከት ይችላል። የደጁን መስታወት ታክኮ የቆመው መደርደሪያ ያገለገሉ ሰዓታት ማረፊያ ሁነዋል። የተበላሹ፣ የተጠገኑ፣ የማይጠገኑ፣ ያልተጠገኑ፣… ሠአቶች ተሞልቷል። እኔ እራሴ ሁሌ የማያቸው ሰዓቶች እዚህ ምን እንደሚሰሩ አይገባኝም። አሰሪዎቹ ቢወስዷቸውና ሰዓት ሠሪው ያገልግሎቱን ቢያገኝ መምረጤን ግን አልሸሽግህም። 

መስታወቱ ላይ ሶስት ጥቅሶች አሉ። በእጅ የተሞነጫጨሩና ለንባብ የማይማርኩ ቢሆኑም፣ ከማንበብ የሚያግተኝ ነገር የለምና በታላቅ መስህብ ስሜት ተውጬ ተጠግቼ አነበብኳቸው፦

የመጀመሪያው እንዲህ ይላል፦

" ተመልከት ፤ እኔ ማንን የምጠብቅ ይመስልሃል? ጊዜ ከሌለህ እዚህ ምድር ላይ ሌላ ምንም ነገር አትጠብቅ!"

በለው ብሶት!! ሁለተኛውን አነበብኩት። 

"ሳምንቱን ሙሉ ክፍት ነው፤ የዕረፍት ቀናትን ጨምሮ" ይላል ።

አባባሉ የቁጥር መጭበርበር ያለበት ቢመስለኝም የሰዓት ሠሪው ቤት እዚሁ መሆኑ ታስቦ የተፃፈ መሆኑንና ደንበኞች ይህን ሊገነዘቡ የተቀመጠ (የቤት ስራ) መሆኑንአምኜ ወደሶስተኛው ጥቅስ አመራሁ።

ሶስተኛው ግን ለራሴም ገራሚ ነበር ፦

"ልክ እንደ ሰዓት የሚበላሽና እንደ ሰዓት ጠጋኝ የሚሰራ ሰዓት የለም!"

እናም ፣ እንዲህ እያልኩ ወደውስጥ ገባሁ፦

"የዛሬው ጥሩ ይመስላል፤ መቼስ እስከዛሬ ከለጠፍኳቸው ይሻላል!"

እሑድ 21 ፌብሩዋሪ 2016

☆እግረ-መንገድ

(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)
‪‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬

የምሰማው ሁሉ አልጥምህ ብሎኛል፡፡ የሬዲዮኑን ጣቢያ እየቀያየርኩ የሚጥመኝ ፕሮግራም ፍለጋ ጀመርኩ፡፡ ዘፋኙ ሁሉ ዘማሪ ሆኗልና! . . . ሬዲዮኑን ዘጋሁትና ቲቪ ከፈትኩ፡፡

በቲቪ፣ የአንድ አዲስ ምርት አምራች ድርጅት ማስታወቂያ እየተላለፈ ነበር፡፡ አስተዋዋቂው፣ ድምፁን ከሌላ ሰው የተዋሰው ይመስላል፡፡ በግነት በተዋቀረ ድምጽ እንዲህ እያለ ነበር፡-

“ልብ ይበሉ! ምርታችን በአይቱ አዲስ እና አስተማማኝነቱ የተረጋገጠ ነው!!”

በለው ውሸት!

“አዲስ እና አስተማማኝ” ማለት ምን እንደሆነ የገባቸው አልመሰለኝም፡፡ አዲስ ከሆነ አስተማማኝነቱ ገና አልተረጋገጠም ፤ የተረጋገጠ ለመሆን ከዚህ ቀደም የሚታወቅ መሆን አለበት፡፡ ይህን እንኳን አያስቡም፡፡

ተጨማሪ ውሸት ሽሽት ቲቪውን ዘጋሁትና ከቤት ወጣሁ፡፡ ትንሽ በእግሬ ዞር ዞር ብዬ ብመለስ እንደሚሻል በማሰብ ነበር አወጣጤ፡፡

ማምሻ ግሮሰሪ የማውቀው አንድ ሰው ከሩቁ “እንኳን አደረሰህ!” ሲለኝ፡፡ “እንኳን!” አልኩት ከሩቁ፡፡

“እንኳን ምን? ” አለና መልሶ ጠየቀኝ፡፡

“እንኳን ብቻ!” ብዬ መንገዴን ቀጠልኩ፡፡

“አይ አንቺ ሰው ፤ በጊዜ አግለሻል መሰል...” ሲል ከጀርባ ይሰማኛል፡፡ ሰው ግን በዓል ሲመጣ ብቻ ነው እንዴ “መድረሴ” ትዝ የሚለው?

መንገዱ ጭር ብሏል፡፡ አንድ ሰው ብቻ ከሩቅ ይታየኛል፡፡ የሆነ ነገር እያወራ እንደሆነ ያስታውቃል፡፡ እየቀረብኩት ስሄድ ምን እያለ እንደሆነ ተሰማኝ፡፡
“የበግ ቆዳ ያለው? ” እያለ ነበር፡፡

አጠገቤ ሲደርስ ወደኔ እያየ ጮክ ብሎ ፤ ”የበግ ቆዳ ያለው!” አለ፡፡ ዝም ብዬው አለፍኩ፡፡ “ሰዉ ዛሬ ምን ነክቶታል?! ” ስል አሰብኩ፡፡ እውነት የበግ ቆዳ ቢኖረኝ መንገድ ለመንገድ ይዤው የምዞር መስሎት ይሆን?!

ሳላውቀው ብዙ ርቀት በእግሬ ተጓዝኩ፡፡ .... አምስት ሴቶች ከሩቅ ይታዩኛል፡፡ ታክሲ እየጠበቁ መሆን አለበት፡፡ እየቀረብኳቸው ስሄድ አለባበሳቸውን ለየሁት፡፡ አራቱ ሴቶች ነጭ የአገር ባሕል ልብስ ለብሰሰዋል፡፡ አንዷ ግን በጅንስ ተወጣጥራለች፡፡ ፀሐዩን ሽሽት በዣንጥላ አናቷን ከልላለች ፡፡ ተስፋ ቆርጣ መሆን አለበት ከመሃከላች ወጥታ በእግሯ መጓዝ ስትጀምር አየኋት፡፡

ነጭ የለበሱት አራቱ ካሉበት አልተንቀሳቀሱም፡፡ በአጠገባቸው ሳልፍ ከመሃከላቸው አንዷ፡- “ወንድም ፤ ሰዓት ይዘሃል? ” ስትል ተሰማኝ፡፡

“አዎ!” አልኳትና መንገዴን ቀጠልኩ፡፡ ልጅቱ ስንት ሰዓት እንደሆነ እንድነግራት እየጠበቀች ነበር መሰለኝ፡፡ ግን የጠቀየቀችኝ ሰዓት መያዜን ነው፡፡ እርሱንም “አዎ” ብያታለሁ፡፡

ዣንጥላ የያዘችው ሴት ከፊት ከፊቴ ስትሄድ አየሁ፡፡ የሚገርም ጀርባ አላት፡፡ እውነት የተፈጥሮ ከሆነ መቀመጫዋ ያምራል፡፡ (ሴቱ እንደ ውስጥ ሱሪ የሚጠለቅ አርቴፊሻል መቀመጫ መጠቀም ጀምረዋል አሉ! ) ይሁን ፡፡ መጠቀማቸው ክፋት የለውም፡፡ የሚቆረቁር ወንበር ላይ ሲቀመጡ እንዳይቆረቁራቸው ከሆነ መልካም ነው፡፡ (ምቾት በሌለው ወንበር ላይ ረጅም ሰዓታት ለሚቀመጡ ወንዶችም ይህ ዘዴ ይጠቅማል መሰል፡፡ )

ሰውነቷ ያምራል፡፡ ዕድሜዋን ለመገመት ሞከርኩ፡፡ በጥቂት ዓመታት ብትበልጠኝ ነው፡፡ “ታላቄ” እንደሆነች ሳስብ አንድ አባባል ትዝ አለኝ፡፡ “ከእያንዳንዷ ታላቅ ሴት ጀርባ መቀመጫዋን የሚያይ ወንድ አይጠፋም!” ሆሆሆ . . . ለጀመሪያ ጊዜ ፈገግ አልኩ፡፡
‪‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬‬
“ልመለስ!? ወይስ መንገዴን ልቀጥል!?” . . . ስል አመነታሁ፡፡ ሉፒዶ (ሽፍደት) ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ ይህ ተፈጥሮ ግን መገለጫው ብዙ ነው፡፡ እያንዳንዱ ሰው እንደየምልከታው ግንዛቤ የሽፍደት አካል መረጣውም ይለያል፡፡

የሰውነት አካላት ሁሉ የዚህ ምልከታ ውጤት ናቸው፡፡ በርግጥ መቀመጫዋ የሚያምር ሴት አይቶ “አሪፍ መቀመጫ አላት” ያለ ሁሉ ይህቺን ሴት ተመኛቷታል ማለት አይደለም፡፡ ማድነቅም ሌላው ተፈጥሮ ነውና፡፡ ከፊቴ ያለችውም ሴት ለእኔ እንደዚሁ ናት፡፡ ያየሁትን ማራኪ ሰውነት አለማድነቅ እንደማልችለው ሁሉ፣ ያደነቅኩትን ማራኪ ሰውነት ሁሉም አልመኝም፡፡ ይህም ተፈጥሮአዊ ነው!

ጥቂት መንገድ የመግፋት ሃሳብ አጋደለና መጓዜን ቀጠልኩ፡፡ ከፊቴ ግን ታላቅ ውሳኔ የሚሻ ነገር እየተውረገረገ ነው፡፡ ከቤቴ የወጣሁት ዳሌ ለመከተል አልነበረም፡፡ አሁን ግን ባጋጣሚ ዳሌ ተከታይ ከመሆንም አልፌ አድናቆት ገላጭ አባባል ቀማሪም እየሆንኩ ነው፡፡ ʿይህን ታላቅ ዳሌ እስከምን ድረስ ነው የምከተለው?! ከዚህ በላይ ከመከተል፣ ዳሌዋን ስካን ማድረግ ይቀላል፡፡ʾ ስል አሰብኩ፡፡

በነገራችን ላይ ፤ ከኋላ መሆን መከተል ነው ያለው ማነው?! (ከእረኛን ተመልከቱ፡፡ ከብቶቹን የሚያግደው ከፊት ከፊታቸው እየሄደ አይደለም፡፡ በጉዞ ላይ ያሉ ከብቶች ካያችሁ ፣ ከኋላቸው እረኛ መኖሩን አትዘንጉ) በዚህ ምሳሌ ብቻ ተገፋፍቼ ለዚህ ታላቅ ዳሌ እረኛ የሆንኩት እንዳይመስልብኝ ስል ርምጃዬን አፍጥኜ አለፍኳት፡፡ አሁን ተራው የርሷ ነው፡፡

ሴቶች ግን . . . ወንድን ከጀርባው ሲመለከቱት ምኑን ይሆን ቀድመው የሚያት?! (ዋሌቱ እንደማይሆን ግን ርግጠኛ ነኝ፡፡)

አልፌያት ጥቂት እንደተራመድኩ ፡- “ይቅርታ፣ አንድ ጥያቄ ልጠይቅህ እችላለሁ?” የሚል ድምጽ ሰማሁ፡፡ እኔን እንደሆነ ርግጠኛ ሆኜ ፊቴን አዞርኩና ልናገር ስል አንድ ነገር አገደኝ፡፡ ዳሌ ዳሌዋን ሳይ ያላየሁት ሌላ ሰው የስልክ እንጨት ፖል ተደግፎ ቆሞ ነበር ለካ፡፡ እሱን ነበር የጠየቀችው፡፡ እምም . . . ተረፈች፡፡ እንኳንም እኔን አልጠየቀች!

በጣም ከሚያናድዱኝ ጥያቄዎች አንዱ ይህ ነው፡፡ “አንድ ጥያቄ ልጠይቅህ?” ብሎ መጠየቅ በራሱ አንድ ጥያቄ ነው፡፡ እንዲህ ብለው የሚጀምሩ ሰዎች ሌላም ችግር አለባቸው፡፡ ያስፈቀዱት አንድ ጥያቄ ለመጠየቅ ሆኖ ሳለ መልሱን ተከትለው ተከታታይ ጥያቄ ማዥጎድጎዳቸው ነው፡፡

የመጀመሪያውን ፈገግታ የፈጠረው ስሜት በምን ፍጥነት ጥሎኝ እንደጠፋ እንጃ፡፡ ብሽቅ!

መቼስ በበዓል ቀን ታክሲ ከመጠበቅ ታክሲ መሸከም ይቀላል፡፡አውቶቢስ ፊርማታ ሳገኛ ቆምኩ፡፡ በእግሬ የመጣሁትን መንገድ በእግሬ የመመለስ አቅም አልነበረኝም፡፡ ታክሲ ቢጠፋ እንኳን ባስ እንደማላጣ ርግጠኛ ነበርኩ፡፡

(ሞራል)፡-
ጥቂት ሰዎች የባሷን መምጫ በጉጉት ይጠብቃሉ፡፡ እኔም እነርሱ ወደሚያዩበት አቅጣጫ አፍጥጫለሁ፡፡ አልፌያት የመጣኋት ቆንጂዛ አልፋኝ ከሄደች ቆይታለች ፡፡ (ማሳለፍ ትልቅ ችሎታ ነው፡፡ ማለፍም፡፡) አለማለፍ ግን ደካማነት፡፡ አለማድነቅ ስሜትን ለሌላው አለማሳወቅ ነው፡፡ ለራስ የተሰማን የአድናቆት ስሜት መሸሸግም ያው አልሸሹም ዞር አሉ ነገር፡፡ የአድናቆት ስሜትን ለሌላው ለማሳወቅ ሲባል ግን እንደኔው ሁሉ ተረጋግተው የሚጓዙትን ሰዎች መልከፍ ግን በነፃው መንገድ ላይ ነፃነትን ከመንፈግ አይተናነስም!!

አድናቆት በሰፊ ቦታ ጠባብነትን ማግዘፍ ሳይሆን ሌላ ስፋትን መጨመር ነው ብዬ አምናለሁና፡፡ ስለዚህም በማለፍ አምናለሁ፡፡ በማሳለፈፍም፡፡

ማሳሰቢያ፡- የእግረ መንገድ ወግ እንደ መዋቅር የተጠቀምኩበት መንገድ፣ ቅርፅ እንጂ እውነተኛ ገጠመኝ አይደለም፡፡ ምልከታን የመግለጫ አንድ መንገድ እንጂ፡፡

ማንደፍሮሽ

(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)

እውነተኛ ስሟ "ማንደፍሮሽ" ነው። እኔና መሰል አብሯ አደግ ጓደኞቼ ግን ፣ በቁልምጫ "ማኔ" እያልን እንጠራታለን። የመንደራችን ሴት ልጆች እንኳን በአካል አይተዋት ይቅርና፣ ገና ስሟ ሲጠራ በፍርሃት ይርዳሉ። ምግብ አልበላም ብለው ሲያስቸግሩ "ማኔን እንዳልጠራት!" ማለት በቂ ነው። ታዲያ እኩዮቿ ብቻ ሳይሆን ታናናሽ ወንድሞቻችንም ቢሆኑ የ"ማኔ" ስም ከተጠራ፣ የቀረበላቸውን ምግብ ጥርግ አድርገው እየበሉ አድገዋል።

ታዲያ ዛሬ ድረስ የሚገርመኝ ነገር ቢኖር የማኔ እንዲህ የመፈራት መንስኤ ነበር። በርግጥ ከወንድ ጋር የሚያመሳስላት ምንም አካላዊ መለያ የላትም። በእነዚህ ሁሉ የጓደኝነት ዓመታት፣ እንደወንድ  ለመምሰልም ምንም አይነት ጥረት ስታደርግ ማየቴንም እጠራጠራለሁ።

ልጅ እያለን ኩሽና ውስጥ እቃቃ ስንጫወት የሆነው ሁሉ አይረሳኝም። "አንቺ ሴት ነሽ፤ ለምን ከመሰሎችሽ ጋር አትጫወቺም" ብለን ጠይቀናት ነበር። መልሷ ግን የከፋ ነበር። በሁለት እጆቿ ያፈሰችውን አመድ ዐይናችን ውስጥ ሞጅራ ሮጠች። ከዛኔ ጀምሮ ነው መሰል፣ ይኸው አድገን እንኳን አንጠይቃትም።

በሌላ ጊዜ ደግሞ፣ ወንድነታችንን ተጠቅመን የበላይነታችንን እንድታምን ለማድረግ በጉልበት ልናስገብራት ሞክረን ነበር። በትግል እንደምንጥላት ተማምነን ብቻ ለብቻ ድብድብ እንድትገጥመን ጠራናት ። ብቻ፣ እንኳን እኔ አቡቹን አልሆንኩ። በመላተም ብዛት ጠንካራ የሆነ የሚመስለው አቡቹ  ጉድ አደረገን!!! ተዝረክርኮ አዝረከረከን። በወቅቱ፣ የመጀመሪያው ተጋጣሚ አቡቹ ነበር። (እንኳን እኔ አልነበርኩ።) ለትግል እንዲመቸው እግሩን አንፈራጦ በመቆም ዝግጅት ላይ ሳለ ድንገት ከማኔ የተሰነዘረው ርግጫ ብልቱ ላይ አረፈና ለሳምንታት የአልጋ ቁራኛ ሆነ። ከዛ ቀድሞ ግን እኛ የበላይነቱን ሚና ያለምንም ማቅማማት ለማኔ አስረከብን። ምክንያቱም ማኔ፣ በቅፅበታዊ ምት እና የት ቦታ ላይ መማታት እንዳለባት ተክናለችና።

ከወንዶች ጋር መሆን ትመርጣለች። (በተለይ ከኔ ጋር) ።

ማኔ ወንድ አይደለችም። ወንድም እንዳልሆነች እናውቃለን። "እኔ ሰው ነኝ!" ያለችን ቀን ምን ማለቷ እንደሆን ባይገባንም፣ ያለምንም ማቅማማት "ነሽ!" ብለናታል። ምስኪን አቡቹ! ገና ከማገገሙ፣ አላራምድ ያለውን የታፋ ስር ንፍፊት ተቋቁሞ እንደተነሳ፣ "እኔ ሰው ነኝ!" ስትል፤ "አዎ ነው!" ማለቱ ሳይቀር ትዝ ይለኛል። (ሲያስቅ... የሰው ፆታው ምንድነው? )

ሴትነቷን እየፈራን እንድናስታውስ የሚያደርገን አስገዳጅ ሁኔታ የሚፈጠረው ከስንት አንዴ ነው። እስከዛሬ፣ "ሴቷ ወንድማችን" ብሎ የጠራት አንድ ሰው ብቻ ነው። እሱም "ፎርጃ" ይሰኛል። (ቅፅል ስሙ ነው፤ የትምህርት ቤት ስሙ ረጅም ነው። ቃል በቃል ባላስታውሰውም፣ 'ፈርቼ ማለድኩት እሱን ሰጠኝ ለኔ ጃንደረባው…') አይነት ነገር ይመስለኛል። ፎርጃ፣ የቅፅበታዊ ጥቃቷ ሰለባ ነበር። እስካሁንም ነው። (ዛሬ አቡቹ አግብቶ ወልዷል) ። በርግጥ የልጁ አባት እርሱ እንደሆነ ያመንው በግድ ነው። (ያሉትን ነው ያልኩት)

ከዚህ ቀደም፣ (ወንዱ እህታችን) ያለው ፎርጃ ግን በሃኪም መውለድ እንደማይችል እንደተነገረው ካወቅን በኋላ የሁላችንም ጥያቄ ይህ ነው… 'እውን አቡቹ መውለድ የቻለው እንደኛው ሁሉ እሱም በሆነውና በሚሆነው ስላመነ ነው?! ወይስ… እንደ ፎርጃ ፣ ሃኪም ስላላየው?!"

ማኔ በሁሉም የልጅነት ጨዋታዎቻችን ውስጥ የመረጠችውን የመሆን ስልጣኗ ዛሬ ላይ ቆም ብዬ ሳስበው ይደንቀኛል። "ባል እና ሚስት" ስንጫወት እሷ የምታገባው እኔን ብቻ ነበር። እሷ ባል ስትሆን፣ እኔ ደግሞ ሚስቷ እሆናለሁ፡፡ የባልና ሚስት የጨዋታው ስርዓት በርሷ የበላይነት ተጀምሮ ያበቃል፡፡ እንደ ሚስትነቴ ምግብ የማዘጋጀት፣ ልጆችን የማጠብ፣ ቤቱን የማፀዳዳት …. ተግባራትን እከውናለሁ፡፡

ልጆቻችን ሆነው የሚጫወቱት አቡቹ እና ፎርጃ ናቸው፡፡ (እስካሁን ድረስ ማን እንዳረገዘ፣ ማን እንዳስረገዘ ባይገባኝም)፡፡ ፎርጃ እንደሴት ልጅ እንዲጫወት የምታደርገው ፎርጃን ነው፡፡ አቡቹ ደግሞ ወንዱ ልጃችን እንዲሆን ሚና ይሰጣቸዋል፡፡ ታዲያ በማኔ የሚታዘዘው አቡቹ ነው፡፡ ማኔ ትእዛዝ በመዛኙ ተመሳሳይ ናቸው፡፡ አቡቹን ጠርታ የባህርዛፍ ፍሬ (ሳንቲም መሆኑ ነው) ቆጥራ እየሰጠችው፡-

"አቡቹዬ፣ ከቃሲም ሱቅ የአስር ሳንቲም ስኳርና የስሙኒ ቡና ግዛልኝ" ትለዋለች፡፡

"እሺ፣ እማዬ" ካለ አለቀለት፡፡ የማኔ ቅፅበታዊ ምት ጭንቅላቱ ላይ ይዘንብበታል፡፡ በኩርኩም  ገጭ! ገጭ!  ገጭ! ... "እሺ አባዬ፣ ረስቼው ነው አባዬ! ይቅርታ አባዬ!" እስኪል ድረስ ኩርኮማዋን አታቆምም፡፡ አቡቹ ጥሎበት ድንገተኛ ኩርኩም ሲቀምስ ምድር ዓለሙ ስለሚዞርበት "አትምቺኝ..." ብሎ ማለቃቀስ ይመርጣል፡፡ እንዲህ ሲሆን የእናትነት ሚናዬን ተጠቅሜ ያስቀጣውን ጥፋት ልነግረው እሞክራለሁ፡፡ "አቡቹ፣ አባትህን እንዴት እማዬ ትላለህ..." ይህኔ "አባዬውን" ያዥጎደጉደዋል፡፡

ማኔ አባትነቷን አስከብራ ስታበቃ፣ "በል ፣ ሁለተኛ እንዳይለምድህ! አሁን ከቃሲም ሱቅ ግዛልኝ ያልኩህን በቶሎ ገዝተህ ና!" ካለችው በኋላ እንደ ሴት ልጅ ሆኖ ወደሚጫወተው ፎርጃ በመዞር እንዲህ ትላለች፡-
"ወንድምሽ እንዳይፈራ አብረሽው ሁኚ..."

ሁሌም ለሚስትነት እኔን እንደምትመርጥ አይገባኝም ነበር። በኋላ እንደገባኝ ከሆነ፣ አቡቹና ፎርጃ ለርሷ "ገና ልጆች" ናቸው፤ (ሚስት ለመሆን ገና አላደጉም)፡፡

በሌላ ጊዜ አንድ ጊዜ እንዲህ ሆነ፡፡ የሆነ ጊዜ ግን እየፈራሁ፡- "ዛሬም ሚስት የምሆነው እኔ ነኝ?" ብዬ ጠየኳት፡፡

"እና መጀመሪያ ሚስቴ እንድትሆን ስመርጥህ እስከመጨረሻው ድረስ ባልህ እንደሆንኩ አታውቅም?!" ብላ ተቆጣች፡፡ አ-ቤ-ት ቁጣዋ! አንድ ጊዜ የምታሳየው የቁጣ ገፅታ፣ ሶስት ሆነን አንሸከመውም፡፡ "እሺ" አልኩ፡፡ ምክንያቱም፣ በዚያ የልጅነት ዕድሜ የተቀረፀብኝ የ"እምቢታ" ትርጓሜው ግልፅ ነበር፡፡ "እንቢ" ማለት... በባሎች ዘንድ እንደጥፋት ተቆጥሮ በ"ሚስቶች" ላይ ለሚያደርጉት ያልታሰበ "ቅጣት" ምክንያት ይመስለኝ ነበር፡፡ (በዚህ ዘመን "ቅጣት" የሚለው ቃል "ጥቃት" በሚል ተቀይሯል፡፡)

የሚስትነት ሚናን ይዤ ስተውን፣ ትዕዛዝ መፈፀም የኔ ግዴታ ሲሆን ማዘዝ እና ማሽቆጥቆጥ ደግሞ የማኔ ስልጣን ነበር፡፡ ታዲያ በጨዋታ መሃል "ጎመን ገዝተህ ና፤ ደግሞ እነዛ መንገድ ዳር የሚቆሙ ሴቶች ካስቸገሩህ ፊት አትስጣቸው!" ብላ ታዘኛለች፡፡

የመንገድ ዳር ተሰብስበው የሚቆሙ የመንደራችን ወንዶች፣ ሴቶች ባለፉ ባገደሙ ቁጥር በነገር መተንኮስ (መላከፍ) ዋንኛው የአራድነት መገለጫቱ  ዛሬም ድረስ ቢቀጥልም፣ በማኔ ዘንድ ግን የተገላቢጦሽ ነው፡፡ ምንም ጨዋታው እቃቃ ቢሆንም፣ ምንም ጨዋታው ባልና ሚስት ቢሆንም… የዓለም ነባራዊ አካሄድ በማኔ ፊውራሪነት ተለውጧል፡፡ በተላካፊ  ሴቶች መግቢያ እና መውጫ አጥተው የተማረሩ ወንዶች እንደ አንዱ ሆኜ "ሴቶች እንዳይተናኮሉኝ" እየተጠነቀቀኩ የታዘዝኩትን ለመፈፀም መተወኔና ማሰብ በራሱ ለማኔ ያለኝ አድናቆት ይበልጥ ይንራል፡፡

የማኔ ባል መሆን እየተመኘሁ፣ ሚስቷ መሆኔን ያመንኩበትን ዓለም ምን እንሚመስል በምናቤ ለመሳል ሞከርኩ፡፡ "ማጅራት መቺ አለ፤ በጊዜ ልግባ…" ሲባል መስማት የተለመደ ነው፡፡ ዛሬም ድረስ ሴት ማጅራት መቺ አላውቅም፡፡ ሰው መጅራት መቺንም ሆነ ዘራፊን ሽሽት በጊዜ ቤቱ ለመግባት ከተጣደፈ፣ ከወንዶች ከሚሰነዘር አደጋ እራሱን ላለማጋለጥ ለመሆኑ ርግጥ ነው፡፡ እናም ወንዶች ለሁለቱም ፆታዎች የስጋት ምንጭ ናቸው፡፡

ከማኔ ጋር ከተዋወቅንበት ሶስት አስርት አመታት ተቆጠሩ። ያለጥርጥር ከ15 ዓመታት በኋላ ነው ያገኘኋት። አድራሻችንን አፈላልጋ እዚህ እንድንገናኝ በስልክ የቀጠረችን ራሷ ማኔ ናት፡፡ አቡቹና ፎርጃ እስኪመጡ እየጠበቅን ነው፡፡ ስለርሷ ያለኝ ግንዛቤ ባይለወጥም፣ አስተያየቴ ግን ተለውጦ ነበር። እንዴት አባቷ አምሮባታል?!? የሌለ ውስዋስ ለኳሽ ሆና ታየችኝ። የተሰማኝን ስሜት ግን ለመናገር አቅም አልነበረኝም። ምክንያቱም ፣ ማን እንደሆነች እድሜ ዘመኔን ሙሉ እንዳልረሳ አድርጋ ነግራኛለች።

ያቀራረበን እድሜ አራርቆናል፡፡ መልሶም አገናኝቶናል፡፡  እድሜ  የለወጠው ብዙ ነው፡፡ እቃቃ መጫወቻዎቻችን ተበትነዋል፡፡ በልጅነት የተጀመረው የባልና የሚስት ጨዋታ ይቀጥል አይቀጥል አይታወቅም…

ረቡዕ 17 ፌብሩዋሪ 2016

"እሾህን በሾህ"

✧(ኄኖክ ስጦታው)
(የአጭር አጭር አጭር ልቦለድ)

ለእራት የሚሆን ነገር ለመግዛት ወደ ሱቅ አመራ። እንደ ሁልጊዜውም፣ ጎረቤቱ የአይጥ መርዝ እየገዛ ነበር። ከጎረቤቱ ቤት መርዝ በልተው እሱ ቤት ኮርኒስ ውስጥ የሚሞቱ አይጦች ሽታ ረፍት ነስቶታል።
"ለምን በወጥመድ አታጠምዳቸውም?" አለና መፍትሄ ይሆናል ያለውን ሃሳብ አቀረበለት። ለጎረቤቱ።
"ሞክሬ ነበር። ወጥመድ ማለት የአይጥ ገበታ ነው። አይጦቹ ወጥመዱ ላይ ያለውን ምግብ በልተው ይሄዳሉ። ጠዋት ስነሳ ወጥመዱ የሚይዘው እኔኑ ነው።"
ዝም አለ።
አስቦ ፣ አስቦ… አንድ መፍትሄ አገኘ። እናም ጎረቤቱ ዞር እስኪል ጠብቆ፦
"የአይጥ መድሃኒት አለ?" ሲል ጠየቀ። ለባለሱቁ።
"የለም። መርዝ ነው ያለው"
"እሱንም ቢሆን ስጠኝ"

እሑድ 9 ኖቬምበር 2014

ዱባና ልጅነት

(ኄኖክ ስጦታው)

#ዱባ
ልጅ ሆኜ የሰማሁት ዘፈን አለ። ስለዱባ እንዲህ ብሎ ነበር፦

"ሳይበላ ሳይጠጣ ይወፍራል ዱባ
ልቤ ተንከባሎ አንቺ መንደር ገባ "

ግጥሙን አድጌ ስረዳው ልብ እና የሚንከባለል ዱባ  ያገናኛቸው ቤት መምቻቸው "ባ" እንደሆነ ገባኝ። ዱባ ወጥ አልወድም።  የዘፈኑ ተፅእኖ ነው መሰል፣ ቤታችን ዱባ ወጥ ሲሰራ ገንዘብ የወጣበት አይመስለኝም ነበር ። ተንከባሎ ቤታችን የገባ ነበር የሚመስለኝ።

በልጅነት ዘመን የማልረሳው አንድ ገጠመኝ አለ። የእርሻ አስተማሪያችን ስለ አዝእርት ሲያስተምሩ እንዲህ ብለው ጠይቀው ነበረ፦

"ከጥራጥሬ ውስጥ የሚመደቡት ምን ምን ናቸው?"

ምድረ ተሜ ተራ በተራ እየተነሱ "ጓያ፣ ሽንብራ፣ ባቄላ…" እያሉ መለሱ። መምህሩ ወደኔ እያዩ፣ "ኄኖክ ፣ የምትጨምረው አለ?" ሲሉኝ ፣ ከመቀመጫዬ ተነስቼ "ዱባ" አልኩና ተቀመጥኩ። የተማሪው ሳቅ እና ያስተማሪው ድንጋጤ ተደምሮ፣ በስክሪብቶ ጫፍ ቂጡን እንደተወጋ ተማሪ አስፈንጥሮ አቆመኝ። (ድሮ ተንኮለኛ ተማሪ አጠገቡ የሚቀመጥ ተሜን ብድግ ሲል ያለቀ ስክሮብቶ አሹሎ እስኪቀመጥ ይጠብቅ ነበር። ያሁኑን ባላውቅም።)

መምህሩ በግርምት አፍጥጠው ፣ አፍጥጠው፣ አፍጥጠው… አይተውኝ ሲያበቁ፣ ባፍንጫቸው የንፋስ ሳቅ ("ህምፍ" አይነት) አሰምተው ዱባ ያልኩበትን ምክንያት ጠየቁኝ። ክፍሉ ረጭ አለ ። እንዲህ ረጭ ያለ ዝምታ ለመጨረሻ ጊዜ ያስተዋልኩት ያኔ ነበር።

ዱባ የጥራጥሬ ዝርያ ለመሆኑ የሰጠሁት አጭር ማብራሪያ፦

"የዱባ ፍሬዎች ፀሐይ ላይ ተሰጥተው ሲደርቁ፣ ተቆልተው ይበላሉ። ልክ እንደ ሽምብራና ባቄላ ማለት ነው።" ከማለቴ ክፍሉ በሳቅ ተናወጠ።

ምን  የሚሳቅ ነገር አግኝተው እንደሆነ ለማወቅ አይኖቼን በክፍል ጓደኞቼ ዙሪያ አንከራተትኩ። ሳያቸው ነው መሰል ይበልጥ መሳቅ ቀጠሉ። ከሁሉ ከሁሉ የገረመኝ፣ የመምህሩም አብሮ መሳቅ ነበር። መቆም እንዲህ ያስቃል?

መቀመጥ ሳይሻል አይቀርም።
ተቀመጥኩ።

ዓርብ 15 ኦገስት 2014

የጆገረረ ጆሮና ምናምን… (ኄኖክ ስጦታው)

ልጅቱ ቆንጆ ናት መሰለኝ። እንጃ…

ለሥራ የምመላለስበት ቢሮ ውስጥ ተቀምጫለሁ። ስልኬን አውጥቼ ማስታወሻውን ከፈትኩ። (ይህ ማስታወሻ ወሳኝ ግብዓቴ ነው። የዳየሪዬ ዋናው አካል ከዚህ ይጨለፋል። እና ከዚህ ቢሮ እስክወጣ ድረስ ለምን አልቆዝምበትም?

ጸሐፊዋ፤
ጉዳዬ እስኪፈፀምልኝ ድረስ ሰረቅ እያደረኩ ተመለከትኳት። ከንፈሯን ደማቅ ቀይ ቀለም ቀብታዋለች። 【የሊፒስቲክ ጥቅም ከንፈር ከማለስለስና ከማስዋብ አገልግሎት ባሻገር ምንም ጉዳት አያስከትልም?!】የከንፈር ቀለም የውሽማ ሸሚዝ ላይ ከታተመ በቶሎ ታጥቦ የማይለቀው ቀለሙ ብቻ አይደለም። የሚያስከትለው መዘዝም እንጂ። (ለብዙ ቤተሰብ መበጥበጥ ምክንያት ሲሆን ያላሳየ የኢቲቪ ድራማ ይኖር ይሆን?!)

በድንገት ቀና ብላ "ተጫወት" አለችና ወደትየባዋ ተመለሰች። በዚህ ቅፅበት ምን ልጫወት? እቃቃ ልጫወት? ከማይገቡኝ ጨዋታዎች አንዱ ይህ ነው። "ተጫወት" ።

  (አንዷ ናት አሉ፤ ፈረንጅ ተጃልሳ ነው። የቋንቋ ነገር አላግባባ ሲላቸው ሁለቱም ዝምታን መርጠው ይቀመጣሉ። ዝምታው እንዴት ይሰበር?! በመጨረሻ እርሷ እንዲህ አለች አሉ፦ "Play" ) ተጫወት፤ ተጫወቺ፤ እንጫወት፤ ፕሌይ …

የጸሐፊዋ ዓይን ያምራል። ፀጉሯ ያምራል። ፊቷ የኦቫል ቅርፅ አለው። ለብቻዬ ፈገግ አልኩ።  የፊቷ ቅርፅ ከትላልቅ አይኖቿ ጋር ተዳምሮ ጥንታዊ የብራና ላይ ስእል አስመስሏታል።  【ያሰብኩትን ከፊቴ ላይ አንብባ ይሆን?!】ሰረቅ አድርጌ አየኋት። እሷ'ቴ፤ አንዳቀረቀረች ነው።

በምን ፍጥነት ከትየባ ወደ ጥፍር ሙረዳ አንደተሸጋገረች አላውቅም። ጣቷ ያምራል። ውበቱን ግን የጥፍሯ ርዝማኔ ያደበዘዘው ይመስላል።

"ተጫወት" እስክትለኝል ድረስ አፈጠጥኩባት። ይገርማል። ጥፍሯ ላይ ተመስጣለች።
ጥፍር! 
የጥፍር እድገት ፍጥነትና፣ የወንድ ልጅ ጡት ሁሌም ይገርሙኛል። ጥፍርስ ይደግ፣ ይመንደግ። ቢያንስ ለሴቶች የውበት ሳሎን ባለሙያዎች የገቢ ምንጭ መሆኑን እያየን ነው። (ኧረ የማይገባኝ ነገር ፤ "እጅና እግር እንሠራለን" የሚሉ ፀጉር ቤቶች  ከጥፍር የዘለለ አንዳች ጥበብ ላይ ደርሰው ይሆን?!) ። ከደረሱ ድንቅ ነው። ካልደረሱም እሰየሁ። እኔም ያልደረስኩበትን በነፃነት እንድናገር በር ከፍተዋል። ውሻ በቀደደው ጅብ እንደሚገባ ፈሪ አበዎች ከገለጹ ዘንዳ እነሆኝ በረከት ለክፉ… የወንድ ልጅ ጡት ጥቅም ምንድነው?! አጥብቶ ሊያሳድግበት… ወይስ ራሱ ጠብቶ ሊመነደግበት?!

ጸሐፊዋ፣
በዚህ ዓመት በሀቀኝነት ያየሁዋት ባትኖርም፣ ሰርቄ ካየኋቸው ሴቶች ውስጥ ግን  "የአንበሳውን ድርሻ" ትወስዳለች። አሁን ከጥፍር ሙረዳ ወደ ወደትየባዋ ተመልሳለች። ጸሐፊዋ።

ጆሮዋን!
ኧረ ጆሮ! በአንድ ጆሮዋ ላይ ብቻ ስንት የጉትቻ ማንጠልጠያ ብስ እንዳለ ልቆጥር ሞክሬ አቅም አጣሁ። እውነት ለመናገር ያልተበሳው የጆሮዋ አካል ቢኖር እርሱም ተበሥቷል።

የጆሮ ጥቅም አናሳ እንደሆነ የገባኝም ዛሬ ነው። (አንድ ግጥም ትዝ አለኝ። ያኔ የጋዜጠኝነት ትምህርት ስንማር የቃላት ፈጠራን አስመልክቶ አንዱ መምህር "ልጂቱ ፣ የዘመነቺቱ " የሚለውን የደበበ ሰይፉን ግጥም በምሳሌነት አጣቀሰና የራሳችሁን ግጥም በፈጠራ ቃል ተጠቅማችሁ ጻፉ ሲል አዘዘን። ጫማዋን ጨምታ፣ ሱሪዋን ሶርታ፣ ቦርሳዋን ቦርሳ፣… ቲሽ!  ሁሉንም አዲስ ቃላት ደበበ ሰይፉ አደብይቶታል። አንዷ ክላስ ሜታችን ግን ለምሳሌነት ያልቀረበ ምርጥ የቃላት ፈጠራ ይዛ ቀረበች፦

"ጆሮዬም ይጆርር፣ እጅ እግሬ ይጀግረር
ጆሬዬም ይደንቋ፣ ከደነቋ አይቀር…"

አለችና ተሜን በፈጠራዋ አስደምማ እርፍ!!"

መምህራችን ግን አልተዋጠለትም። ወይ ደበበ ፣ ደበበ ሸትቶት አልዋጥ ብሎት ይሆናል እንጃ፤ የተገጀረረውን የቃል ፈጠራ ገርጅጆት አለፈው። ቺኳ ገጣሚት ተቆጫበረች። እናም አለፈ። እንኳን አለፈ።

ዛሬ ያየሁት ጆሮ የተበሳ እንዳልሆነ ሳስበው ታወሰችኝ። በርግጥም ጆሮ ይደነቋል! ! እጅ እግርም ይጀገረራል!!

የቢሮዋ "ጸሐፊ" ተጫወት የምትለኝ መስሎኝ ቀና ብዬ አየዃት። ኤጭ። "ተጀግርራለች፣ አልያም ደንቁታለች…

ሰኞ 4 ኦገስት 2014

"መንጭቆ ከማስነሳት" ማዶ… ኄኖክ ስጦታው


አሮጌ መኪና ለማሽከርከር አሪፍ ሹፌር መሆን አይጠበቅብህም፤ ልበ–ደንዳና መሆን ግን የግድ ነው። ደንዳና ልብ ከሞተር ቀጥሎ የመኪናው አንቀሳቃሽ ሃይል ነውና።

በምስኪኗ ቮልሴ ካስተናገድኳቸው ቅስም ሰባሪ ተረቦች የመጀመሪያው ዛሬ ሳስታውሰው ያስቀኛል። "አዲስ" የገዛኋትን መኪናዬ ለጓደኛዬ ላሳየው ያለበት ቦታ ድረስ እያሽከረከርኩ ሄድኩ። አንገቱን በሃዘኔታ እየናነቀ፦ "ይህቺ ቮልስ የተመረተችበት ፋብሪካ፣ አሁን ዲዲቲ ማምረቻ እንደሆነ ታውቃለህ?!" አለ። በጊዜው ተቆጫበርኩ። ተቀየምኩት መሰል። "ከዚህም የባሰ እንዳለ" የገባኝ ግን ወዲያው ነበር።

ባለመኪና ለመባል ቮልስ የሚገዛ ተሸውዷል። ምክንያቱም ማንም ባለመኪና አይለውም። እንበልና መኪናዋ የቆመችው መንገድ ዘግታ ቢሆንና ሹፌሩ ባይኖር "ማነው የዚህ መኪና ባለቤት" አይባልም። ባይሆን፣ "ይቺ ቮልስ የማናት" ይባል ይሆናል።
 

የሆነ ሰሞን፣ «አሮጌ መኪኖች ከመንገድ ይወጣሉ» የሚል ስር የለሽ ወሬ ሰምተን ሰጋን። የቮልስ መካኒካችን ስናማክረው ወሬውን እንዲህ ብሎ አጣጣለው። " አሮጌ መኪና ይገባል እንጂ መቼም አይወጣም። መንግስት እራሱ አሮጌዎቹን የሚተካበት አዲስ መኪና መች አለውና?"

(እውነቱን ነው፤ ሌሌሎች አርጅቶ የተጣለ ለእኛ ግን የክት ነው። ያገለገለ እቃ ዋጋውን የሚያጣበት የገበያ ደንብ በተናደባት አገር እንኳን ያገለገለ መኪና ቀርቶ የተለበሰ የውስጥ ሱሪም ዋጋ አለው።)


ሹፌሮች ቀበቶ ሳያደርጉ ማሽከርከር በትራፊክ ደንብ መተላለፍ እንደሚያስቀጣ ደንብ ወጣ። ታዲያ ያኔ፣ በቮልስ ባሉካዎች ዘንድ ታላቅ ድንጋጤ ተፈጠረ!

ቀበቶ ባልታሰበበት ዘመን የተመረቱ መኪናዎችን ባለቀበቶ ለማድረግ ሩጫ ተጀመረ። የደህንነት ቀበቶ ግን ዋጋው ጣሪያ ደርሶ ነበር። አንድ ወዳጃችን ግን ሁነኛ ዘዴ ፈለሰፈ። የሻንጣ ማንገቻን ቆርጦ እንደቤልት የመጠቀም መላ። የፈጠራ ባለመብት እንደሆነ የቮልስ ቺፍ መካኒኩ አረጋገጠለት።

"ዳሩ ምንያደርጋል" መሀል አደባባይ ላይ በትራፊክ ፖሊሶች ተያዘ። ትራፊኮቹ የፌክ ቀበቶውን ከመኪናው አስፈትተው አላገጡበት። "የደህንነት ቀበቶ ከሌለህ ማንገቻ ያለው ሱሪ ብታደርግ ይሻል ነበር¡" እንዳሉት ነገረን ። ሳቅን።

"ስንት ብር ተቀጣህ?" ሲል ከመሃከላችን አንዱ ጠየቀ።
"አልቀጡኝም። 'ብንቀጣህ ከሌላው ሹፌር እኩል ትሆናለህ፤ ብትቀጣ የምትከፍለውን ብር አሁኑኑ የደህንነት ቀበቶ ግዛበት'— ብለው ለቀቁኝ።"
 

«የአሮጌ መኪናህን መካኒክ ጓደኛህ አድርገው።» የቮልስ ፍቅር ማደሪያ ልቡ ያለው ያው ጋራጅ ነውና።

አንድ ሰሞን ቮልሴን ለማስጠገን ጋራጅ እመላለስ ነበር። ጋራጅ የሚያስኬደኝ የመኪናዋ መበላሸት ብቻም አልነበር ። ጤነኛ ስትሆንም ያሳስበኛል።【ሳትበላሽ ከሰነበተች በቀላሉ የማይጠገን ከባድ ብልሽት እንደሚጠብቀኝ እርግጥ ነው】።

ሌላው ጋራጅ ሳልሳለም እንዳልውል ያደረገኝ ምክንያት፣ ከቮልስ ባሉካዎችና መካኒኮች ጋር መወዳጀቴ ነበር። 

አያሌ ፍተላዎች ከጋራጅ ይወለዳሉ። ተረቦች ነፍ ናቸው። ከመካኒኮች ጋር መዋል ያስደስታል። ጨዋታቸው፣ ትርርቡ፣ ልግጡ፣ … አይጠገብም።

ሞተራቸው በቁልፍ የማይነሳና በግፊ ተመንጭቀው ከሚነሱ ቮልሶች የተቀዳ አንድ አባባል አለ። «መንጭቀው ይነሳል!»  የሚል። አንድ ቀን እዛው ጋራጅ ውስጥ በሃይል አስነጠስኩ። ማንም «ይማርህ» አላለኝም። በምትኩ ግን «መንጭቀው ይነሳል!» የሚል ድምፅ ተሰማኝ።

ይሄ ድምፅ እስከዛሬም ድረስ፤ የቆምኩ ሲመስላቸው እንድነሳ ከሚገፉኝ አነቃቂ ሰዎች አንደበት ይሰማኛል።

"መንጭቀው ይነሳል!!"

ሰኞ 7 ጁላይ 2014

"የሃብታም ልጅ " ፍለጋ

በኄኖክ ስጦታው

አብሮ አደጌ ነበር። አብረን ብናድግም ቅሉ፣ አብረን ግን አንድም ቀን ቁም ነገር ተጫውተን አናውቅም። እንደው ርግጫ ወደጨዋታ ከተጠጋጋም፣ ከተጫወትነው ትዝ የሚለኝ "ሹሌ" ብቻ ነው።

ዛሬ ይህ ሰው ያደኩበት መንደር "እግረኛ ትራፊክ" ሆኗል።

በየመንደሩ አያሌ እግረኛ ትራፊኮች አሉ። እንኴን አብሮ አደጋቸውን በመልክ የሚያውቁትን በፈለጣ የሚቀጡ።

ርግጥ ነው፤ የፈለጣ ቴክኒኮች "በስማ በለው" ከአንዱ ፈላጭ ወአሌላው ይተለፋሉ። ( እንደ ስነቃል በፅሑፍ አልሰፈሩም።)

የትውልድ መንደሬ አስቁሞ ፈላጭ ከየት መጣ ሳይባል ከች አለ። (መንገድ ዘጋብኝ ማለት ይቀላል መሰል!)

ፈገግታው ልዩ ነበር። (በናፍቆት የጦዘ ፈገግታ :D ) ፊቱ ላይ ያለው ፈገግታ… "ይሸጣል!" የሚል ማስታወቂያ ቢለጠፍበት የሸማቹን አጀብ አስቤ "አማተብኩ"።

ሰላምታ ተለዋውጠን፣ የፈገግታው ወላፈን በርዶ፣ እጅ ለእጅ መወዛወዛችን ጋብ ብሎ… ከዚህ ሁሉ በዋላ መንገድ ጀምረን ለጨዋታው አዝማች ፣ "ኑሮ እንዴት ነው?" ስለው… ፊቱ በመቅፅፈት ተፈጠፈጠ። (እደዚህ ዓይነት ተለዋዋጭ ፊት ማግኘት መታደል ነው¡)

"ምነው?" ብዬ ጠየቅኩት።

"ምን እዚህ አገር ላይ እየኖርክ ለብቻህ ለውጥ አታጣውም።…" አለና ለመጀመሪያ ጊዜ የምር የሚመስል ጨዋታ ያመጣ መሰለኝ። ቀጠለ:– "መቼስ ላንተ አልነግርህም፤ ዘመኑን ታውቀዋለህ፤ ካለው ተወለድ፤ ወይም ካለው ተጠጋ። ካልሆነ ግን በእንጀራ አባት እንደኔ ስትሰቃይ ትኖራለህ… " አለኝ።

(የሰበቡ ድምዳሜ ፈለጣ ነውና ዘለልኩት) ከሃብታም ቤተሰብ ተወልዶ ድህነቱን የሚያምን እርሱ ሃብታም እንደሆነ አምናለሁ።

የሃብት መለኪያው ባለን እና ፣ እንዳይኖረን ባረግነው እንጂ፣ በኖረን እና በእንዳይኖር ባረግነው ግብአት አይሰፈርም።

በመሰረቱ ሃብት ያከቸው ሃብታም ቢባል ቅሬታ የለኝም። "የሃብታም ልጅ" መባል ግን ከአድናቆትነቱ ይበልጥ ስድብነቱ ያመዝንብኛል። ያልሆነ፤ ግን ሆነዋል ከተባሉት የተወለደ በመወለድ ብቻ ያለው መመቻመች "የወራሽነት" መብት ነውና "እጩ ወራሽ" ቢባል ይመጥነዋል…


አብሯደጌ ቅፈላውን ገፋበት። "… አየህ፣ ሥራ የለም። ብራሞችም እኛ ችስታዎችን አያስጠጉንም።…"

የገንዘብ የማጣት ችግርን ማስታገሻ ስሞች የኅብረተሰብ ውስጣዊ ማንነት መገለጫ ከመሆን አይድኑም። አንድ ብር ዋጋ እንደዛሬ በአንድ ሳንቲም ሳይተካ በፊት እነ "ሺ ብሬ" ተወልደዋል። የብሩ ዋጋ እየወረደ ሲመጣ ደግሞ እነ "ሚሊዮን" ተወለዱ። አሞሌ ጨው ብር በነበረበት ዘመን የኖሩ ሰዎችን መጠሪያ ስም ብናጣራ "አሞሌ" እና "አሞሊት" ተብለው የሚጠሩ አይታጡም።
★ ★
አንድ የመጨረሻው የድህነት ወለል በታች ተነስቶ ወደ ታላቅ "ቅንጦት" የተሸጋገረ አባት፣ በ14 ዓመት ልጁ ይህን ጥያቄ ተጠየቀ:— "ድህነት ምንድነው?"

አባት መልሱን ወዲያው አልተናገረም
ድህነትን ሳያውቅ ለኖረው ልጁ በተግባር ሊያስተምረው አሰበ። እናም በጉብኝት ሰበብ ገጠር ወደሚኖሩት ዘመዶቹ ዘንድ ላከው። ልጁ ከሳምንት በኋላ ሲመለስ :—

"እንዴት ነበር ጉብኝት?" ሲል ጠየቀው።

"በጣም ደስ የሚል ጊዜ ነበር " አለ ልጁ።

"እና ምን ተገነዘብክ? " አባት ሌላ ጥያቄ አስከተለ።

"የላከኝ አገር የሚኖሩት ሰዎች እኛ ከምንኖረው የተለየ አኗኗር አላቸው። እኛ በግንብ በታጠረ ጠባብ ግቢ ውስጥ በብዙ ዘበኛ አገልጋዮች ተከበን እንኖራለን፤ እነርሱ ግን በነፃነትና ባልታጠረ ሰፊ ቦታ ላይ ይኖራሉ። አንዱ የሌላው ጠባቂ እንጂ፣ እንደኛ ዘበኛ አይቀጥሩም።

"እኛ ሁለት ውሾች አሉን፤ እነርሱ ግን ብዙ አላቸው። እኛ ሚጢጢ የዋና ገንዳ ስንቦራጨቅ፤ እነርሱ ግን ትልቅ ወንዝ ውስጥ ይዋኛሉ። እኛ ከገበያ የምንገዛቸውን አትክልቶች ፤ እነርሱ ግን ከጓሮ ይቀጥፋሉ። …"

"እና ድህነት ምን እንደሆነ አሁን ተመለሰልህ? " አለ አባት።

"በሚገባ ተመልሶልኛል። እኛ ምን ያህል ድሆች እንደሆንን አውቄያለሁ" አለ ልጁ።

★ ★

አብሮ አደጌ በቀላሉ እንደማይፋታኝ ገብቶኛል። የጀመረውን ሃሳብ ሳይጨርስ ወደሌላው የሚሻገርበት ፍጥነት ይደንቃል።

"… የምሬን ነው፤ አንዷን ልጥጥ ካልተጃለስኩ ከዚህ ሲዖል አልወጣም!" አለ።

"ወንድሜ፤ ገንዘብ አይቶ ከመጃለስ፣ ቁልቋል ታቅፎ ማደር ይቀላል።"
★ ★

አቋራጭ መንገድ ፍለጋ ረጅምና አስቸጋሪውን መንገድ መጓዝ መርጧል። ጥገኝነት የሕይወት መንገዱ ነው። ከሰዎች የሚፈልገው ብዙ ነው። ለሰዎች የሚሰጠው ግን ምንም።

እጅግ ሀብት ካላቸው ቤተሰብ የተወለደ አንድ ወዳጅ አለኝ። —‘የሃብታም ልጅ‘ ሲሉት ይቆጣል። "የሚያኮራው ሃብታም መሆን ነው።" ይላል። ዋናው ጥያቄ ይህ ነው:— ጥገኛ ሃብታም፣ ወይስ ጥገኛ ድሃ?

ሕይወት ሙሉ ናት። የጥገኝነት ተፅእኖ ግን የሌሎችን እንጂ የራሳችንን እንዳናይ ጋርዶናል። ጥገኛ ምሑር፣ ጥገኛ ነጋዴ፣ ጥገኛ ባል፣ ጥገኛ ሚስት፣ ጥገኛ ተማሪ፣ ጥገኛ ተከራይ፣ የጥገኛ ጥገኛ ተጠጊ · · ·

ጥገኝነትን የሙጥኝ ያሉ ግንዛቤዎች በንሮ ዘዬያችን ውስጥ ሰልጥነውብናል። የስብሰባ አዳራሾች "የኔም ሃሳብ እከሌ እንዳለው ነው—" በሚሉ ተሰብሳቢዎች ይጨናነቃሉ። የሊቃውንት ስም ካልጠሩ ከእውቀት መዝገብ የሚፋቁና የሚጎድሉ የሚመስላቸው "ምሁራን" ከስራቸው አያሌዎችን "ይቀርፃሉ"። መሪ ቢቃዥም ባይቃዥም፣ ለራሳቸው ያልገባቸውን ለማስፈፀም የሚታትሩ ትጉህ ሸምዳጅ "አስፈፃሚ" ጥገኞችም "ያሉበት ሁኔታ ነው ያለው¡"።

አዎ ጥገኞች ነን። ስንጠላ የጥላቻ፣ ስንወድም የውዴታ ጥገኛ ነን። ስንወለድ የወላጅ፣ ስናረጅም የልጆች ጥገኛ ነን። የተቃራኒ ዓለም ሰዎችም ነን። ቅሪት የቋጠረ እየፈራ፣ ቅሪት አልባው የሚጀግንበት። ለውጥ አልባ ጥገኞችም ነን። ስንወጣ የመውረድ፣ ስንወረደድ የመውጣት ውትብትብ ለመቀበል ያልበቃን ጥገኛ ድሆች።

ድሃው ማነው? ሃብታሙስ?

ድህነት የገንዘብ ከሆነ በሰለጠኑት አገራት ተሰደው ያሉ ወገኖች የመጨረሻውን ድሃ የማይሰራውን ስራ ሰርተው ሲመጡ ሃብታም የምንላቸው ለምንድነው? ሃብታም ስለነበሩ? ሃብታም ስለሆኑ? ወይስ እኛ ከእነርሱ በታች ድሃ ስለሆንን?

በፍፁም፤ ድህነት ስታስቲክ እንጂ እውነታ አይደለም። ሃብታምም ሆነ ድሃ ለቁጥር አይመቹም። "ከሃብታም" ጋር የተመሳሰሉ ድሆች "ከበርቴ" ይሰኛሉ። "ከድሃ" ጋር የተማሰሉም "ከበርቴዎች" እንዲሁ "ምንዱባን" ይባላሉ። የቱ ነው ትክክል? ቆጣሪው ወይስ ተቆጣሪው?

በእድሜ ዘመኑ ከፍሎ በማይጨርሰው ብድር ተዘፍቆ ሃብታም ከተሰኘው አባት ለተወለደ ልጅ ሃብት ምንድነው? እድሜ ዘመኑን ድህነቱን አምኖ በጠኔ ከሚጠበስ ቤተሰብ ለተወለደ ልጅስ ድህነት ምኑ ነው?

ረቡዕ 11 ጁን 2014

አክስት አዛሉ - (ኄኖክ ስጦታው)

አክስት አዛሉ


እውነተኛ ስሟአዛለችይሰኛል፡፡ እኛ ቤተሰቦቿአንቺየሚለውን ድምፀት ከአንደበታችን ለማጥፋትአዛሉብለን በመጥራት አንቺን ከአንቱ አስታርቀነዋል፡፡

አዛሉ ሞባይል የያዘች ሰሞን ጥቂት ተቸግራ ታስቸግረን እንደነበር አይረሳኝም፡፡ በተለይየቴሌዋ ሴትዮብላ ከምትጠራት ጋር ያነበራት ጠብ እጅግ የከረረ እንደነበር አስታውሳለሁ፡፡

አዛሉ፣ በሞባይል ስልኳ ስትደውል (የቴሌዋ ሴትዮ) ... “የደወሉላቸውን ደንበኛ አሁን ማግኘት አይችሉም...” ስትላት ነው መሰል እንዲህ ስትል ሰምቻታለሁ፡-

ምነው እቴ! አሁን ብታገናኚኝ ክብርሽ አይቀንስ...”

አዛሉ ሚሴጅ ሲደርሳትምየቴሌዋ ሴትዮትብጠለጠላለች፡፡እንግሊዝ ያስተማረችኝ አይመስልም አሁን?! ጉድ እኮ ነው! አበስክ ገበርኩ..... እስቲ ይህች ሴትዮ ምን እንደምትል አንብብልኝ...” ብላ ስልኳን ትሰጠኛለች፡፡ በቁጥር ስህተት ካልሆነ፣ አልያም የቴሌዋ ሴትዮ ካልተላከላት በቀር፣ ከማንም መልዕክት ደርሷት አያውቅም፡፡

እናም መልዕክቱን አነብላታለሁ፡-

“Dial *808*3# and call up to 6o minutes for only Br 4.99 or *808*4# for unlimited calls with only Br 9.99 from 11:00PM -6 :00AM (NIGHT TIME).”

ደግሞ አሁን፣ ምን አድርጉ ነው የምትለው?” ትላለች አፏን በሽርደዳ መልክ እያሞጠሞጠች፡፡ እንምንም ላስረዳት እጥራለሁ፡፡ እስኪገባት ድረስ ግን ታግሳ አትሰማኝም፡፡ ተቋርጠኝና፤

መልሰህ ላክላት! ʿእንኳን ዘንቦብሽ እንዲሁም ጤዛ ነሽʾ ብለህ ላክላት!” ትላለች እየተንጨረጨረች፡፡ ከንዴት ጋር ያላት ቅርበት፣ ለማወቅ ካላት ትዕግስት አልባነቷም ያይላል፡፡

አክስት አዛሉ፣የቴሌዋ ሴትዮከምትላት ባላንጣዋ ጋር ሳትነታረክ ውላ አታውቅም፡፡ አንዳንዴ፣ያለዎት ቀሪ ሂሳብ አነስተኛ ነው... እባክዎን ተጨማሪ ሂሳብ...”  የሚለውን ንግግር ትሰማና መልስ ትሰጣለች፡፡

እሺ፣ እሞላለሁ፡፡ እኮ ምን አለብሽ?! እኔ በሞላሁት ካርድ የምታወሪው አንቺው....”

አንድ ጊዜየቴሌዋን ሴትዮድምፅ መስማት -- ብሏት እንዲህ በማለት የጠየቀችኝ አይረሳኝም፡-

እንደው ይህቺን ሴትዮ የሚተካ አንድ ደህና ወንድ በአገሩ ጠፍቶ ነው እንዲህ ቀን ተሌት ቦርቂባቸው ብለው የለቀቁብን?! ”

አክስቴ፣ምን ወንድ አለ ብለሽ ነው....” እላታለሁ ነገሯ እንዲራዘም ስለምፈልግ፡፡


እውነት ብለሃል! ይህ መንግስት ሴቱን የሚያደራጀው ለምን ሆነና?! ወንዱንማ ደርግ ጨርሶታል....”