2013 ኦክቶበር 24, ሐሙስ

አሸባሪው ማነው? --በኄኖክ ስጦታው

አሸባሪው ማነው?

በቀይዋ ብዕሬ፣ የከተብኩት ሁሉ፤
አንዴ ከኔ ወጥቷል፣ እስቲ ተቀበሉ።

እውነትን ሊናገር፣ አፉን የከፈተ፤
ንቅዘቶችን ነቅሶ፣ ድክመትን ያተተ፤
በዚህች ጉስቁል አገር፣ ምሣር በበዛባት፤
በሚቀጥለው ቀን፣ ለርሱ ወየውለት!!

ለምን!?
ፈራጅ ነው ዘራፊ፤ ተዘራፊው ሌባ
ትችት ያሳስራል፤ በማሸበር ደባ

የታል!?
"ነፃ አውጪው" የታል!?
ሆኗል ጨቋኝ መሪ
"ለምን" ባዩን ፈራጅ፤ "በሽብር ፈጣሪ"
ደፍሮ የሚናገር፣ ዘብጥያ ታሣሪ።

ማነው!?
ፀረ—ሠላም ማነው!? ማነውስ ነፃ አውጪ!?
አሸባሪ ማነው!? ማንኛው ነው ቀጪ!?
ወንጀለኛው ማነው!? ማነውስ ታሳሪ!?
ፀረ—ሠላም ከሣሽ፣ እራሱ መስካሪ፤
"ለምን" ባይ ተከሣሽ፣ ላገር ተቆርቋሪ!!

2004 ዓ. ም.


(ከ "ሀ-ሞት" የግጥም መጽሐፍ/ በኄኖክ ስጦታው)

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ