ዓርብ 23 ዲሴምበር 2016

“ማሳ – ደግ”

(ኄኖክ ስጦታው)

በእንክርዳድ ማሳ ጥቂት ስንዴ በቅሎ
ይስፋፋ ጀመረ “እሕል ነው” ተብሎ።
*
ስንዴ ለሆድ ሲባል፣ በሰው መኮትኮቱ
ተነቅሎ ቢጣልም፣ እንክርዳድ ነው ብርቱ 
ሳይዘሩት ይበቅላል፣ የት ይሂድ ከርስቱ?!
*

ኮትኩቶ ማሳደግ፣ ቀልቦ ማደለብ፣ የሰው ታላቅ ዘዴ
“ ደረሰ… በሰለ…” የሚሉኝ በዙሳ ፣ ሊበሉኝ ነው እንዴ?!

ረቡዕ 21 ሴፕቴምበር 2016

መንገድ የግጥም መድበል ገበያ ላይ ዋለ


ውድ የእልፍኜ ታዳሚታን፣ ከዚህ በፊት "ነቁጥ" (1994ዓ/ም) እና "ሀ–ሞት"(2005ዓ/ም) ለሕትመት በቅተዋል። እነሆ "መንገድ" የተሰኘው ሶስተኛው የግጥም መድበል ታትሟል። መፅሀፉ ሁለት ፊት ያለው ሲሆን የገጣሚ አበባ ብርሃኑ "ጠፈጠፍ" የተሰኘው የግጥም መድብል ጋር ተዳብሎ ለገበያ ቀርቧል።

(አከፋፋዩ ጃፋር የመጻሕፍት መደብር ነው )

የመጻሕፍት መደብሮቻችን አድራሻ

1,  ለገሃር ኖክ ነዳጅ ማደያው አጠገብ ተወልደ ህንፃ

2, ጊዮርጊስ የአውቶብስ ጣብያውን ወረድ እንዳሉ

3, ሳሪስ አዲሱ ሰፈር መግቢያ

4, ቃሊቲ ገብርኤል ቤ/ክ አጠገብ

ያስታውሱ:-

ከጃፋር መጻህፍት መደብር መጻሕፍት ሲገዙ ሁሌም…… ከዓመት እስከ ከዓመት ከዋጋው ቅናሽ ተደርጎ ነው።

ከኢትዮጵያ ውጪ ላሉ አንባቢያን henoksitotaw65@gmail.com ቢፅፉልኝ በአድራሻችሁ የሚደርስበት መንገድ ተመቻችቷል 

ማክሰኞ 6 ሴፕቴምበር 2016

ከራስ ባህሪይ ጋር ጦርነት

አንድ የቼሮኬ አዛውንት ለልጃቸው ልጅ ይህን ታሪክ አጫወቱት፣
"የእኔ ልጅ፣ በሁለት ተኵላዎች መካከል ታላቅ ጦርነት ተፈጠረ። አንደኛው ተኩላ #ክፉ ነው። ይህም ማለት፣  ቁጣ፣ ቅናት፣ ስግብግብነት፣ ቂመኝነት፣ በየበታችነት ስሜት እና በውሸት የተሞላ ነው።
“ሌላኛው ተኩላ ደግሞ #ጥሩ ነው። ይህም ማለት… ደስታ፣ ሰላም፣ ፍቅር፣ ተስፋ፣ ትህትና፣ ደግነት፣ አዘኔታ፣ እና ሀቀኝነት ያሉት ነው።”
ህፃኑ ልጅ እንዲህ ሲል አያቱን ጠየቀ፦ "የትኛው ተኵላ አሸነፈ?"
አዛውንቱ ለጥቂት ጊዜ ያክል ዝም ብለው ቆይተው ይህን መለሱ፦
"አሸናፊው ያለው ከውስጥህ ነው።"

ማክሰኞ 5 ጁላይ 2016

"አምስቱ ሞኞችና ሌሎችም ታሪኮች…"

(ኄኖክ ስጦታው)

‘ሙሽራው በዘገየ ጊዜ ሁሉም እንቅልፍ ተጫጫናቸውና ተኙ።’
(የነቁት ግን ይህን  ለማንበብ ችለው ነበር)

ከአሥሩ ደናግላን መካከል አምስቱ ሞኞች ናቸው። አምስቱ ግን አንድ። አምስት ደናግል ብልሆች አንድ ብርሃንም ለመፍጠር መዘጋጀታቸውን የተመለከተ የዚህ ዘመን "አዛዥ" እንዲህ ሲል ሰማሁት፦

‘ለአንድ ኩራዝ አምስት ሰው ምን ያደርጋል?! አራታችሁ ተመለሱና ከአምስቱ ጎን ቁሙ!! ብርሃን ለመለኮስ አንድ ሰው ይበቃል!!! ዳይ!!!’

የተባረሩት አራቱ ብልሆችም፣ አምስቱን ጅሎች አስተባብረው ስሞታ ለማቅረብም ወደመምህራቸው አቀኑ። እንዲህ ሲሉ ጠየቁ፦

‘ጌታ ሆይ፣ ተርበህ ወይስ ተጠምተህ ወይስ እንግዳ ሆነህ ወይስ ታርዘህ ወይስ ታመህ ወይስ ታስረህ መቼ አይተን ሳናገለግልህ ቀረን?’

እርሱም ተናገረ። በርግጥ መልሱ ግልፅ ቢሆንም፣ ማንም አልሰማውም ነበር።  

‘ታዲያ ለምን ትጠይቁኛላችሁ? እኔስ ብሆን ያደረኩት ይህንኑ አይደል?!…’ 
☆   

ነገሩ እንዲህ ነው። አንድ የግብረ ገብ መምህር የዳርት ውድድር አዘጋጀ። ለተማሪዎቹ። ዳርቱ ነጭ ወረቀት ተለብጧል። ኢላማውን በነጩ ወረቀት ላይ የሚስለው እራሱ ተወዳዳሪው ነው። ለምሳሌ፣ በነጭ ወረቀት የተለበጠው ዳርት ላይ  የሚጠላውን ሰው ስም ይፅፋል። የፃፈውን ስም በፍላፀው አነጣጥሮ ከመታው ‘ጥላቱን ’ እንደተበቀለ ያህል ይረካል ።

ውድድሩ ከመጀመሩ በፊት ሁሉም ተማሪ  የራሱን ጥላቻ ለመውጋት ኢላማ ይሆነኛል ያለውን ታናናሽ ምልክቶችን በዳርቱ ላይ አኖረ ። ኢላማውን ለመውጋት አነጣጥረው የወረወሩት ሁላ የራሳቸውን ኢላማ ባይመቱም እንኳን፥ በስህተት የሌሎችን ኢላማ ክፉኛ ወጋግተውት ነበር።

እናም በመጨረሻ፣ የዳርቱን መጫወቻ የሸፈነው ነጭ ወረቀት ሲገለጥ የኢየሱስ ምስል ክፉኛ ተወጋግቶ ለሁሉም ታየ። ይህን ያደረጉት የግብረ ገብ  መምህሩ ነበሩ።

የራሱን ኢላማ  ለመምታት አነጣጥሮ የወረወረው ተሜ ሁላ እንዲህ የሚል ንግግር ከመምህሩ አንደበት ተላለፈለት፦

‘እውነት እላችኋለሁ፣ ከሁሉ ከሚያንሱት ከእነዚህ ወንድሞቼ ለአንዱ ያደረጋችሁት ሁሉ ለእኔ እንዳደረጋችሁት ይቆጠራል’
በሌላ ጊዜ፤ 

ሁለት አማኞች ስለ ሃይማኖት እያወሩ ነበር።

አንደኛው ለሌላው፣ "አንዳንዴ ፈጣሪን… ለምን ድህነት፣ ረሃብ፣ ኢፍትሐዊነት… በአለም ላይ ሊያስወግድ እንዳልቻለና የሆነ ነገር እንዲያደርግ በፀሎት ብጠይቀው እወድ ነበር።" ሲለው ሁለተኛው አማኝ ተገርሞ ፦

"ታዲያ እንዳትጠይቀው ምን አገደህ?!" ሲል ይጠይቀዋል ።

እናም፣ የመጀመሪያው አማኝ እንዲህ ሲል መለሰ፦ "አምላክ ፤ እነዚህኑ ጥያቄዎች እኔኑ መልሶ እንዳይጠይቀኝ ሰግቼ ነዋ!" 
።።።።።።።።።።።።።።

እኔም ይህን አልኩኝ፦

‘ከዚህ በኋላ የምትጠይቀኝን መልሼ እጠይቅሃለሁና ስትጠይቀኝ ተጠንቅቀህ  ጠይቅ!’

*መነሻ ሃሳብ (ማቴዎስ 25…)

ሐሙስ 23 ጁን 2016

ውጣ—ውረድ

(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)

“ነበር” ላይ ሊያበቃ፣ የ“ነው” ባይ  አቅጣጫ፤
ከ"ነው" እና "ነበር"፣ የታል የኔ ምርጫ?


መድረሻው መነሻ
          መነሻው መድረሻ
ጠይቅ “የታል” ብለህ… “የታል ውጣ—ውረድ”?
(ሕይወት መሰላል ነው፤ የእርብራብ መንገድ!)

የጥያቄ ምላሽ፣ በምጥ ላይወለድ
“እውነት” ካስጨነቀህ፣
  በስንዝር ቦታ ላይ፣ ጋት ጨምር… ተራመድ
መልሱን ተወውና፣ መጠየቅን ውደድ
                    ውጣ
           ወይም
ውረድ!

ሐሙስ 9 ጁን 2016

ፀሐይ

(ኄኖክ ስጦታው ናኁሰናይ)
የልቤን መሻት ለማድረስ፣ ውጣ ውረዱ ሲበዛ 
የመንፈስ ብርታት ልትሆነኝ፣ ሙቀቷ ሕይወት ሊነዛ
ፀሐይ ምድር ደርሳለች፣ ፍኖተ ሃሊብ ተጉዛ፡፡
ዝለቂ ከዋሻው ብርታቴ፣ ስንፍና ሰበቡን ይጣ
“ፀሐይ ልሞቅ ነው” በማለት፣ እኔም ከዋሻው አልውጣ፡፡

ረቡዕ 8 ጁን 2016

ወጣ ያሉ የግዕዝ ቅኔያት

ወጣ ያሉ የግዕዝ ቅኔያት

በአጋጣሚ አግኝቼ ያነበብኩት መጽሐፍ ነው። “ቅኔያዊ የእውቀት ፈጠራ“ ይሰኛል ርዕሱ። በማርዬ ይግዛው ተሰናድቶ በ የጀርመን የባህል ማዕከል፣ 2006 ዓ.ም የታተመ ነው።

“…አብዛኛዎቻችን ቅኔ ኃይማኖታዊነት ብቻ የሚንጸባረቅበት ይመስለን ይሆናል። ቅኔ የማይዳስሰው ነገር የለም። የጾታ ተራክቦን (የግብረ—ሥጋ ግንኙነትን) እና መዳራትን ጨምሮ።…” እያለ ይቀጥላል የመጽሐፉ ትንታኔ።
ቀነጫጭቤ ጋበዝኳችሁ፦

ቅኔ ፩

ኢይጠፍእ ሕልጽ እሳት ላዕሉ ወታህቱ፣
እስኪት ጉልጥምት እስመ ተዳፈነ ቦቱ።
ትርጉም፦
          እምስ የላይና የታቹ እሳት አይጠፋም፤
          ቁላ/ጉልጭማ (እንጨት) ተዳፍኖበታልና።
ምስጢር ፦

ጉልጭማ የተዳፈነበት እሳት እንደማይጠፋ ቁላ የሚገባበት እምስም ሙቀት አይለየውም። በተለምዶ እሳት የሚጠፋው በውሃ፣ ሙቀት የሚበርደውም በቀዝቃዛ ነገር ነው። እምስ ግን ራሱ የቁላን ትኩሳት የሚያስታግሰው በማይጠፋ ሙቀት ነው እንጂ ከቀዘቀዘ አስተናጋጅነቱ ይቀራል።

እሳቱ/ሙቀቱ የማይጠፋ የሚለው የመራባት የሰው እንስሳዊ ህይወት ምንጭ መሆኑንም ያመላክታልና በዚህ ግልፅ ወሲባዊ ቅኔ ውስጥም ስለ ሕይወት ቁም ነገር አልጣበትም።

ቅኔ ፪

እታገኝ ደመርኪ እምላእለ ክብርኪ ክብር፣
ለነዳይ እስኪት እስመ ወሀብኪ ቂንጥር።

ትርጉም ፦
         እታገኝ በክብር ላይ ክብር ጨመርሽ
         ለድሃው ሰው ቁላ ብልት በመጽውተሽ። (መጽውተሽዋልና)

ምስጢር ፦
ይህ ቅኔ እማሆይ ገላነሽ እታገኝ የተባለች ልጃቸው ስታገባ የተቀኙት ነው ይባላል። ሰሙ በዚህ ዓለም ለተራቡ ሰዎች የሥጋ ብልት ሳይቀር የሚመጸውቱ ሰዎችን ይገልፃል። ባለቅኔዋ እታገኝ የተባለችው ልጅ ስታገባ ለተራበ ቁላ የሚገባውን ምግብ በመስጠት የጽድቅ ሥራ ማድረጓን አስመስጥረዋል።