2013 ጁላይ 2, ማክሰኞ

“ፍትሃዊ የሥጋ ክፍፍል” - ኄኖክ ስጦታው

እኩል መስተንግዶ ለሁሉም ሰው- በሁሉም ቦታ!!”





ይህ ጽሑፍ የልኳንዳ ማስታወቂያ ሊመስል ይችላል፡፡ ((ልኳንዳ ቤት ሥጋ መብላት ለከፋ ለችግር ይዳርጋል፡፡ ምክናያቱ ግልፅ ነው፡፡ አቅም ያናጋልና፡፡)) እውነታው ይህ ነው፡፡ ለእኔ፡፡

አንዳንዴ ግን ሥጋ እሳፈጣለሁ፡፡የመጣው ይምጣ፤ ከልኩ አያልፍም፤ ሺህ ዓመት አይኖር፤ የበላና የተማረ ወድቆ አይወድቅም፤ ሆድን በጎመን ቢደልሉት ጉልበት ዳገት ላይ ይለግማል….” ቅብርጥሶ ቀብርጥስጥሶ ሃሳቦች ከአቅም በላይ ሆነው ሲሰለጥኑብኝና አምሮቴ ሲገንን ልኳንዳ ቤት አገባለሁ ….. ዛሬ አንዱ ቤት እንደገባሁት ማለት ነው፡፡

የቅንጦት ምግባችንሥጋነው፡፡ አትክልትማ ዘመናችንን ሙሉ ስናላግጥበት ኖረናል፡፡

በልጅነት ዘመኔ ዓውድ ዓመት እንዲመጣ የሚያስመኙኝ ሁለት ነገሮች ነበሩ፡፡ አንደኛው ትምህርት ቤት ይዘጋል፡፡ /በዓል... ቅዳሜና እሁድ እንዳይውል እጸልይ ነበር/ ሁለተኛው ደግሞ ቀይ ወጥ እንደጉድ ይበላለታል፡፡ /አቤት እንዴት ያለ ትዝታ ነው!? /

ከሁሉም የማልረሳው ትዝታ፣ ለመሥራት ረጅምና አሰልቺ ጊዜ የሚወስደው ዶሮ ወጥ እስኪደርስ አላስችል ብሎኝ ከቁሌት ካልሰጣችሁኝ ብዬ ኩሽና ውስጥ የምረብሸው ነገር ነው፡፡

ያኔ ታዲያ ቤታችን የሚሠራው ቀይ ወጥ የራሱ የሆነ ቅደም ተከተል ነበረው፡-

የመጀመሪያዎቹ ሁለት እና ሶስት ቀናት ----- ቅባት እና አንኳር ሥጋ የበዛነት

ቀጥሎ፣ ------ በድንች ወጥ ውስጥ ጥቂት ሥጋ ጣል ጣል ያለበት

በመጨረሻ ------- ሽሮ ወጥ ውስጥ በስህተት የገቡ ሥጋዎች /ቦዘና/

የመጨረሻው መጨረሻ ----- ልሙጥ ሽሮ ነው፡፡

አንዳንዴ ጊዜ፣ ቤታችን ከገጠር ዘመድ ይመጣል፡፡ ያኔ ታዲያ መደዳውን ከምንበላው ሽሮ ጣልቃ ሥጋ ወጥ ይገባና የሽሮን ታሪካዊ ሚና ይሽረዋል፡፡

/ገጠር ያሉ ዘመዶች ሲመጡ በእነሱ አጠራርዳቦ ቆሎከእጃቸው አይለይም፡፡የተቆላ ዳቦቢባል የሚሻል መጠሪያው እንደሚሆን አስባለሁ፡፡ እውነት ለመናገር ለብዙ ዓመታትዳቦ ቆሎማለት ከዳቦ ትንሽ አነስ ያለ፣ ከሽንብራ ቆሎ በመቶ እጥፍ የተለቀ ይመስለኝ ነበር፡፡/

የልጅነት ትዝታዬን እዚህ ጋር ልግታውና ዛሬ ያጋጠመኝን ልኳንዳ ቤት ትንሽ ላሞጋግስ፡፡

በቲፕ ሰበብ ሙስናው ይበልጥ ደርቷል፡፡ በተለይ በስጋ ቤቶች፡፡ እኔና ጓደኞቼ አንድ ኪሎ ስጋ ለመመገብ አንድ ኩንታል ስጋት ተሸክመን የገባንበት ቤት እስከዛሬ ካየኋቸው ቤቶች በብዙ መንገድ ይለያል፡፡

የሥጋ ቆራጮቹ ጋወን ንጣት፣ ቁጥር እየጠሩ የሚጯጯሁ አስተናጋጆች አለመኖር፣ ደህናውን ሥጋ እንዲቆርጥላቸው የሚሹ ደንበኞች ሥጋ ቆራጩን ለመደለል /ጉርሻ ቢጤ ብር እንዳይሸጉጡ/ መከልከላቸው ……. ዋናዎቹ ናቸው፡፡ በስንት ድርድር ገንዘብ አጋጭተን የገባንባቸው ሥጋ ቤቶች ውስጥ የሚሠሩ አሻጥሮች እዚህ የሉም፡፡ ወይም አላጋጠመንም፡፡

እውነቴን ነው፣

ብዙ ቦታ ላይ የሚያጋጥመን ““-ፍትሃዊ የሥጋ ክፍፍል”” እዚህ ቤት ተሽሮ ማየቴ የነጋዴዎቻችንን ብስለት መጨመር ገምግሜበታለሁ፡፡

ልኳንዳ ቤቱ እንዲህ የሚል ማሳሰቢያ ጽፎ ሳይ ደስ አለኝ፡፡

ለምንሰጠው መልካም መስተንግዶ ሲባል
ለቆራጮች ጉርሻ መስጠት አይፈቀድም!!”

ጽሑፌን ለመደምደም ይህን አልኩ፡፡

እኩል መስተንግዶ ለሁሉም ሰው- በሁሉም ቦታ!!”

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ