2013 ጁላይ 22, ሰኞ

ውዝግብግብ …."ያላዘነው ውሻ እኔ ነበርኩ" በ-ኄኖክ ስጦታው





ዛሬ ደግሞ አንድ ወጣት ተሰቅሎ ሞተ፡፡ ወጪ ወራጁ ደረቱን በጆቹ ጠፍሮ መንሾካሾክና መረጃ መለዋወጥ ጀመረ፡፡ ሁሌም በሚሞት ሰው ላይ እንዲህ አይነት ነገር ይንፀባረቃል፡፡

“ቅድም ሰላም ብሎኝ ነበር ያለፈው፤ የሚሞት አይመስልም ነበርኮ” ትላለች አንዷ ለሌላዋ፡፡

 “ትላንት ከኛ ጋር ነበር ያመሸው፤ ምንም የተለየ ነገር አይታይበትም ነበር” ይላል ሌላው፡፡

“ሌሊት ውሻ ሲያላዝን ሰምቼ ደግሞ ማንን ሊገፋ ነው ይህ ሟርተኛ እያልኩ ሳስብ እንቅልፍ ባይኔ ሳይዞር ነጋ፡፡” አንዲት እናት ከጎናቸው ላሉ እኩያቸው ሲናገሩ ሰማሁ፡፡

ቀባሪዬ፣ እኔ ነኝ ውሻው፡፡ ሌሊት እንቅልፍ እንቢ ሲለኝ አላዘንኩ፡፡ እንደውሾቼ ጮህኩ፡፡ የሞት ጠረን ሸቶኝ ግን አልነበረም፡፡ ታንቆ መሞት ለዚህች መንደር አዲስ አይደለም፡፡ የሚሞት ባይኖር እንኳን የሚረዳ አይጠፋም፡፡ የጥሩንባ ድምፅና የውሻ ማላዘንን በሚፈራ ማህበረሰብ “የሞት መልእክተኛ” ተብዬ ለመፈረጅ ጊዜ አልፈጀብኝም፡፡ በጥቂት ሰዓታት ውስጥ ብቻ ውሻው እኔ እንደነበርኩ ሁሉም ነዋሪ አወቀ፡፡ ምሽት ላይ ከታጣቂዎች ጋር  ተፋጠጥኩ፡፡

“ሌሊት ስትጮህ ታይተሃል!” አለኝ አንዱ መሳሪያ ታጣቂ፡፡

“እና?”

“ምን “እና” ትላለህ? ለምን ሰላማዊ ሰውን ትረብሻለህ?” አፈጠጡብኝ፡፡

“እናንተ ለምን እኔን ትረብሻላችሁ?”

“ተነስ እንሂድ”

“አልነሳም!”

“መታሰር ትፈልጋለህ?” በሚያባብል ድምፀት ሌላው ተናገረ፡፡

“መታሰር ምንድነው?” መለስኩለት ጤነኛ እንዳልሆንኩ አንዴ ደምድመዋል፡፡ የትም ይዘውኝ ሊሄዱ እንደማይችሉ አውቃለሁ፡፡ ሊደበድቡኝ ይችላሉ፡፡ ሊያጠቁኝ አቅሙ አላቸው፡፡ ሰላማዊ ሰው ረብሼ ይሆናል፡፡ ለእኔ ግን ሰላማዊ ሰው በውሻ ድምፅ የሚረበሽ አይደለም፡፡ ቀድሞ እራሱን ባጉል እሳቤ የበጠበጠ ሰላማዊነቱ አይታየኝም፡፡

“አማኑኤል መግባት ትፈልጋለህ?” ብረት አንጋቹ ጠየቀኝ፡፡ የሱ ግንዛቤ አማኑኤልን ጥላቻ እዚህ የተቀመጥኩ መስሎት ይሆናል፡፡ ከዚህ የተሻለ ስፍራ ሊሆን ይችላል፡፡ ማገገሚያ አያስፈልገኝም፡፡ ግን ማየት ፈለኩ፡፡

“አዎ! አማኑኤል ውሰዱኝ!” ለመንኳቸው፡፡ ደጋግሜ ወተወትኳቸው፡፡ ማሰሪያ ገመዳቸው ተበጣጠሰ፡፡ አማኑኤልም ሊወስዱኝ አይችሉም፡፡ ታዲያ ለምን መጡ? ሊያስፈራሩኝ? ሊደበድቡኝ? እስኪሰለቹኝ ድረስ ኃይለ - ቃል ወረወሩብኝ፡፡ የማያደርጉትን ዛቱብኝ፡፡ ሰላማዊ ሰው ብረብሽ ከባድ እርምጃ እንደሚወሰድብኝ አስጠንቅቀው ነገሩኝ፡፡ በእነርሱ ዘንድ እብድ መሆኔ አስንቆኛል፡፡ በእኔ ዘንድ ሰላማዊ ሰው መሆናቸው አስንቋቸዋል፡፡ በመሰሎቻቸው ላይ የሚያደርሱት ቅጥቀጣ ለካስ እብድ መሆናቸውን ስላላመኑላቸው ነው! እብድ መሆኔን ማመናቸው ነፍስ ባጠፋም እንዳይፈርዱብኝ ያደርጋቸዋል፡፡ ምክንያቱም እብድ ነኛ! ህጉም ቢሆን ከጎኔ የሚቆመው ሰዎች ሰብአዊነቴን ስለሚዳፈሩ ሳይሆን ወንጀለኛ መሆን ስችል ብቻ ነው፡፡

 የሰላማዊነት ሎጅክ በነፍጥ አንጋች እና በኔ መካከል ልዩነት አለው፡፡ ዛሬ ባልጮህ ሰው አልበጠብጥም፡፡ ፍርሃታቸውን አልቆሰቁስም፡፡ አስተሳሰባቸው የወለደው ፍራቻ ይበቃቸዋል፡፡ ውሻ በጮኸ ቁጥር ግን ያስቡኛል፡፡ በኔ ላይ በሚጥሉት ሽርደዳ ሰላሜን ቢዳፈሩም እንቅልፍ አጥተው የሚፈሩትን ሞት አላስታውሳቸውም፡፡ ይህን ሳደርግላቸው ግን በመጮሄ የማገኘውን ሰላምን እየሰዋሁላቸው መሆኑን ይረዱት፡፡ እነሱም ይህ ውለታዬን አንድ ቀን ለመሬት ይከፍሉልኛል፡፡ ይሞታሉና!

አሽ-ሙጥ በ Henok Sitotaw

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ