2013 ጁን 15, ቅዳሜ

ቆቅ እና “ማሽሟቀቅ” . . . ከሰማሁት ያስታወስኩትን ያህል - - ኄኖክ ስጦታው



በ1993 መጨረሻ ይመስለኛል፡፡ በሩሲያ ሳይንስና ባህል ማዕከል ገጣሚና ጋዜጠኛ ነቢይ መኮንን የትምህርት ቤት ትዝታውን አንስቶ ተሞክሮውን ያካፈለበት ላይ ሲናገረው የሰማሁት ነው፡፡ አማርኛ አስተማሪያቸው “ቆቅ” በሚል ርዕስ ሁለት መስመር ግጥም እንዲጽፉ አዘው ነው ነገርየው፡፡ ከተማሪዎቹ መካከል አንዱ አማርኛ ቋንቋ ሁለተኛ ቋንቋ ኖሮ የጻፈው ግጥም ለመምህሩ ሊገባቸው አልቻለም፡፡

 እዚያ ማዶ አነዲት ቆቅ
አየኋትኝ ስታሽሟቅቅ፡፡

ተማሪውን አስነስተው “ማሽሟቀቅ” ምን ማለት እንደሆነ ይጠይቁታል፡፡ መልሱን ሰምተው ማርክ ሊሰጡ መሰለኝ፡፡ ተማሪውም እንዲህ ብሎ መለሰ፡-

“እኔ ለራሴ አማርኛ ለማወቅ እያሽሟቀቅኩ ነው”

ታዲያ የቃሉን ፍቺ በቅርቡ (ቅርቡ ጊዜ ያኔ ነው) እንደተረዳው ነቢይ መኮንን ለዛ ባለው አንደበቱ ተናግሮ ነበር፡-
“ገዢው ፓርቲ እያሽሟቀቀብን እንደነበረ የገባኝ አሁን ነው” ብሎ ታዳሚውን አስፈግጓል፡፡(በነገራችን ላይ ይህች የቆቅ “ግጥም” ከግዜያት በኋላ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ “የነገር ጥግ” አምድ ስር  ማንበቤን አስታውሳለሁ)


ነቢይ መኮንን ለታዳሚዎቹ አንድ የግጥም ርዕስ ሰጠ፡፡ “ትዝታ” በሚል ሁለት ስንኝ ግጥም ጻፉ ፤ አለ፡፡ በብርሃን ፍጥነት አንድ ሰው ጽፎ ሰጠው፡፡ አነበበልን፡-

ትዝታሽ ዘወትር ወደኔ እየመጣ
ስለሚያስቸግረኝ ፖሊስ እጠራለሁ፡፡

(አንታራም ግጥም ይሉሀል እንዲህ ነው፡፡)

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ