2020 ፌብሩዋሪ 2, እሑድ

“አብሾ “፥ “አፍልሆ”፥ መድሃኒት (ኄኖክ ስጦታው)



አለቃ ለማ ትዝታቸውን ለልጃቸው ለመንግስቱ ለማ(ለአብዬ መንግስቱ) ያጫወቱት ነው ፤ በመምህሩ አፍልሆ ስለተደረገለትና በቅኔ ተወዳዳሪ ስለሌለው አንድ ተማሪ ነው ጨዋታው። መምህሩ አለቃ ተጠምቆ ይሰኛሉ። የተማሪው ስም ሠረገላ ብርሃን የተሰኘ በኋላም የታወቀ የቅኔ አስተማሪ የሆነ ሰው ነው። አለቃ ለማ በጣፈጭ አንደበታቸው ለልጃቸው እየተረኩለት ነው።

“ተማሪያቸው ነው አፍልሆ አርገውለታል ይመስለኛል ተጠምቆ፥ መዳኒት ጸሎት በውሃ እሚደግም - ለቅኔ ብቻ አይደለ፤ ለዜማም ለመጣፍም እንዲያው ለሚጠናው ሁሉ ነው። በውሃ ስለተደገመ ነው አፍልሆ የተባለው. . . እገሌ ሰው ያህለዋል አይባልም ቅኔ በማሳመር - ቅኔው ሌላ ነዋ ባያሌው። ሲመራ! ወዲያው መምራት ነው። አራት ተማሪ አቅርቦ ይመራል የሚባለው እሱ ነው። መምህር ሆኖ፤ . . . እሱን እንዲህ ያደረገው አለቃ ተጠምቆ ናቸውና እኔም እንደሱ እሆናለሁ ብዬ ተነስቼ ሄድኩ ኸሳቸው። . . .” (መፅሐፈ ትዝታ ዘዓለቃ ለማ፤ ገፅ 79)

ስለ አብሾ (አፍልሆ) በቃል የተናገሩት ሊቀ ጉባኤ ፈቃደ ስላሴ ተፈራ ናቸው። አያሌ ጥያቄዎችን የሚመልስና ብዙ ጥያቄዎችን የሚያጭር መረጃ ሆኖ ለዚህ ዕሑፍ የጀርባ አጥንት ሆኖኛል። “በአገራችን የቤተክርስቲያን ምሁራን ዘንድ ትምህርት ይገልፃል፥ አእምሮ ይስላል እየተባለ በልዩ ልዩ ሁኔታዎች ተቀነባብሮ በተለያየ የእድሜ ደረጃ ላሉ ተማሪዎች የሚሰጥ መድሃኒት ሲሆን በተጨማሪ “ዘኢያገድፍ” እንዲይዝ የማይጥል፣ “መክሰተ ጥበብ” እና “መፍትሄ ሀብት” እየተባለ ይጠራል. . .” ሲሉም አክለውም ስለ አብሾ ምንነት ያብረራሉ።

ይህ ገለፃቸውን ለሚመረምር ሰው የአብሾን ጥቅም ከዕውቀት ገላጭ ከመሆኑ ጋር ብቻ እንዳልሆነ ይረዳል። የመጀመሪያው ደረጃ መድሀኒት “ዘኢያገድፍ” ተብሎ የተገለፀው በቤተክህነት ትምህርት ፊደለም ሆነ ቅኔ ለሚገድፉት የሚሰጥ ሲሆን የሚማሩትን በቃላቸው ቶሎ እንዲይዙ (እንዳይጥሉ) የማድረግ አቅም ያለው መድሃኒት እንደሆነ ግልፅ ነው። ሌላኛው “መክሰተ ጥበብ” የሚሰኘውም የቃላቱ ትርጓሜ እንደሚነግረን ጥበብ ገላጭ እንደሆነ ያመላክታል። ይህም ከዕውቀት አንድ ደረጃ ከፍታውን ወደ ጥበብ የሚያሳድግ መድሃኒት ነው።  ሶስተኛው “መፍትሄ ሀብት” ነው። ለነዋይ ማካበቻ ይረዳል ተብሎ የሚሰጥ መድሃኒት እንደሆነ ተረድቻለሁ።

[በተለይም የአብሾ አፍልሆ ለቅኔ ዘረፋ እድሜ ልክ የሚያነቃቃ አብነት ነው። እየተባለ ይጠጣል። በቃልም፥
ጠላ ያለጌሾ
ቅኔ ያለአብሾ . . . እየተባለ ይተረታል። አብሾ ሶስት አይነት ዝርያ ሲኖረው ጥቁር፥ ቀይና ነጭ ናቸው። ጥቁሩ በአገራችን በየትኛውም ቦታ በቅሎ የሚገኝ ሲሆን አስተናግር ተብሎ የሚታወቀውም ጥቁሩ ነው። (አብሾ የተሰጠው ተማሪ) . . . የሚነገረው ትምህርት የማይጠፋውና የሰማውን ነገር የማይረሳ ከሆነ ሆሳዕናው (መድሃኒቱ) ሰመረለት ይባላል። ካልሰመረለት የርኃወተ ሰማይ ቀን ጠብቆ እንደገና ይደረግለታል እየተባለ ይነገራል። (ርኃወተ ሰማይ የሰማይ መከፈት ነው) ይኸውም የሚሆነው በአመት አራት ጊዜ ሲሆን ጳጉሜ 3፥ ታህሳስ 13። የካቲት 4 እና ግንቦት ስምንት ቀን ነው። ]

ጥንታዊው የቤተክህነት መፅሐፍት መካከል፣ “ፅፀ ደብዳቤ” አንዱ ነው። በጥንታዊ አባቶቻችን በመድኃኒቶች ላይ የነበራቸውን ጥበብ በአውደ ነገሥት ላይ ሰፍረው ይገኛሉ። ከእነዚህም መድኃኒቶች ተራ ቁትር 56ኛው አብሾ (አብሶ) በሚል ስም ተጠርቷል። ስለሆሳእናው (መድሓኒቱ) ምንነት እና አድራጎት፣ በባህላዊና መንፈሳዊ ህክምና ጥበብ አማካኝነት ትምህርት ለማይዘልቀው ልጅ ሁነኛ መድሃኒት እንደሆነ እንዲህ ሲል ይገልፀዋል፦

[፶፮፤ አብሶ (ዕፀ ፋርስ አስተናግር) በበርኻ የበቀለ ነጩ ፍሬውን ደቍሶ በነጭ ሽንኵርት ብቻ በተደለዘ በርበሬ ሽሮ በነጭ ጤፍ እንጀራ እየፈተፈቱ መልክአ ኢየሱስን እየደገሙ ፯ ቀን ለክተው ለሕፃናት ቢያበሏቸው ትምህርት ከመ ቅጽበት ይገባቸዋል ፍቱን ነው። እንዲሁም ከመ ዘኢያገድፍም ፫ ቀን ጠዋት ጠዋት ማዋጥ ነው።]

ሊቀ ጉባኤ ፈቃደ ስላሴ ተፈራ ስለ መድሃኒቱ አዘገጃጀት ሰፋ ያለ ትንታኔን ሰጥተዋል።[“. . .የሚዘጋጀውም ከልዩ ልዩ እፅዋት ቅጠል፥ አበባ፥ ስርና ተቀፅላ በመሆኑ በማር ወይም ንፁህ ማር ወፍ ባልቀመሰው ውሃ (በጠዋት በተቀዳ ውሀ) በሞላ ብርሌ (በጥቁር ብርሌ) ውስጥ እስከ አንገቱ ውሃ ተሞልቶ ከተበጠበጠ በኋላ ለማፍሊያ የተዘጋጀ ፀሎት እየተፀለየበት አንድ ሱባኤ ይቆያል። እስከ ሰባት ቀን ይሰነብታል። ሱባኤው ሲያልቅ በሰባተኛው ቀን ተጠቃሚው ልጅ ወይም ደቀመዝሙር በባዶ ሆዱ ይጠጣዋል። ወዲያው እንደ ጠጣ ከሰው ተለይቶ ለሶስት ቀናት ብቻውን በአንድ ክፍል ውስጥ ይታቀባል/ ይቀመጣል። ከዚያም ለአንድ ሱባኤ ወይም ለሰባት ቀናት አልያም ለሰባት ሱባኤ ወይም ለአርባዘጠኝ ቀናት የተወሰኑ ምግቦችን እየበላ ማለትም የገብስ ቆሎ ፥ የገብስና የጤፍ እንጀራ በኑግ ጭማቂ በማጥቀስ እየበላና የኑግ ጭማቂ ብቻ እየጠጣ የሚያጠናውን ንግግር በማሰላሰል እንዲቆይ ምክር ይሰጠዋል። አደራረጉ የተለያየ ከመሆኑም በላይ የሚቀመሙትም እፅዋት እንደየመምህራኑ ጥናትና እንደየገቢሩ የተለያዩ ናቸው ይባላል. . .”]

መዛግብት ይህንን ቃል በምን መልኩ አንደፈቱት ተመልክቼ ነበር። አብሾ የመድሃኒት ስያሜ ሲሆን የተለያዩ አይነት አእምሮን አነቃቂ እፆች አማካኝነት ተቀምሞ ለመፍትሄነት ሲያገለግል የኖረ ጥንታዊ መድሐኒት እንደሆነ ይናገራሉ። ከኢትዮጵያ ውጪ የጥንት ስልጣኔ ግንባር ቀደም ተጠቃሽ በሆኑት ሩቅ ምስራቅ አገራትም ውስጥ ተመሳሳይ መድሀኒቶች እንዳሉ ይታወቃል። በቻይና፣ በሕንድ እና በጃፓን እውቀት ገላጭ፣ አእምሮን አብሪ የሆኑ ባህላዊና መንፈሳዊነትን ያጣመሩ ተመሳሳይ መድሃኒቶች እንዳሉ ጥናቶች ያረጋግጣሉ።

በቤተክርስቲያን ውስጥ ተወስኖ ስላለውና እንብዛም ጥናት ባልተደረገበት “አብሾ” ዙሪያ በቃልና በፅሁፍ ያገኘኋቸውን መረጃዎች ተቀነጣጥበውም ቢሆን ሰፍረው ይገኛሉ፤ ከነዚህም ውስጥ አለቃ ኪዳነወልድ ክፍሌ በመዕሀፈ ሰዋሰው አስተናግር ወይም ዕፀ ፋርስ አናግር አስለፍልፍ ስለሚሰኘው ዕፅ ምንነት ሲያብራሩ፥ ‘የቀመሰው ሰው ወደ ፊት የሚሆነውንና የሚያገኘውን ስለሚያናግር አስተናግር’ እንደሆነ ይጠቁሙናል።

ደስታ ተክለወልድ የአማርኛ መዝገበ ቃላት በተሰኘው መፅሐፋቸው ስለ ዕፁ
[ዕጠ፡ ፋርስ] ተመሳሳይ ሐሳብ አስፍረው አንብቤያለሁ። [የፍሬው ልብስ እሾህ ያለበት ተክልነት የሌለው የዱር እንጨት፤ ቅጠሉን በጎች ቢበሉት ራሳቸውን ያዞራል፤ ሰውም ቢቀምሰው ያሳብዳል። ባላገሮችም ዐጤ ፋሪስ ይሉታል። ይህ ሁለት አይነት እንጨት ባገዳ በቅጠል በፍሬ ልዩ ሲሆን ልብን በመንሳት ስለተባበረ ባንድ ስም ተጠራ። በካህናት ዘንድ ግን ሁለተኛው ከአንደኛው ተለይቶ አስተናግር ይባላል። ]

በቤተክህነት አካባቢ ያሉ አንድ አባት ስለ አብሾ ምንነት እንዲነግሩኝ ጠይቄ ነበር።  “ፍሬውን የቀመሱ ሁሉ ባለብሩህ አእምሮ ይሆናሉ። ትምህርት ገላጭ ነው። ትንቢትም ያናግራል። በጥንቃቄ ካልተደረገ ለእብደትና ለሞት የሚያበቃ ስካር ውስጥ ይጥላል” ሲሉ ሃሳቡን አጠናክረውታል። 
በተለምዶ አብሾ (አብሶ) ተብሎ የሚጠራው አንዱና ዋንኛው አድራጎታዊ መገለጫው ሲሆን አስተናግር ከተሰኘ ዕፅ ይቀመማል። አድራጎት አፍልሆ ተብሎ ይጠራል። በአንድ ቀን የሚፈላ አፍልሆ አለ ይባላል። የዚህም ቅመማ ከላይ እንደተገለፀው ሆኖ በተጨማሪም ዛጎል ተደቁሶ ይጨመርበታል። ዛጎል ፀሎት የሚደረግበትን መድሃኒት ቶሎ የማፍላት ሃይል ስላለው እለቱን እንዲፈላና እንዲገነፍል ያደርገዋል። እንደ ፈቃደ ስላሴ ተፈራ አባባል ከሆነ የዚህ አይነቱ አፍልሆ (ዛጎል የገባበት) ጥሩ እንዳልሆነ ሲነገር ሰምተዋል። ተማሪዎች ቅጠሉን አፍልተውና ከጤፍ እንጀራ ጋራ ፈትፍተው በቀመሱት ጊዜ አእምሯቸውን ለውጦ ማደሪያቸውን ያናጋል፤ ማርከሻውም የኑግ ልጥልጥ ወይም በሶ እንደሆነም ያምናሉ።

ቀዩ በቆላማ ቦታዎች አካባቢ በሚፈስ ወንዝና ወንዝ መጋጠሚያ ላይ ይገኛል። ነጩ አብሾ ከጎንደር በበሸሉና አባይ መጋጠሚያ በጎጃም በዚገም ወንዝና በአባይ መጋጠሚያ፥ በሸዋ በሙገርና በአባይ ወንዝ መጋጠሚያ ይበቅላል ሲሉ ፈቃደ ስላሴ ተፈራ ስለፍሬዎቹ አይነትና ጥቅም፣ ብሎም ጉዳት ጠቁመዋል። ከፍሬዎቹም ዓይነቶች ውስጥ ጥቅም ላይ የሚውሉት ቀዩ እና ነጩ ብቻ እንደሆኑ ይነገራል። አጠቃቀሙም የተለያየ ነው። አንዳንድ መምህራን ስለአብሾ መድሀኒት ሲናገሩ አብሾ ጠጥቶ ወይንም በልቶ እስከ አርባው ቀን አልክሆል መጠጥ መቅመስ ሰካራም ያደርጋል ይላሉ። ነገር ግን አርባው ቀን ካለፈ በኋላ አልኮል ቢጠጣም ምንም ጉዳት እንደማያስከትል ይናገራሉ። በተለይ አደራረጉን የማያውቁ መምህራንም ሆኑ ተማሪዎች ወይም ግለሰቦች አብሾ ጠጥተው ወይም አጠጥተው ወዲያው አልኮል ስለሚጋቱ ሰካራሞችና አልፈው ተርፈውም እብዶች ይሆናሉ።

“የአብሾ ነገር ሲነሳ አንድ ትዝ የሚለኝ ነገር አለ” ባሉት የሕይወት ገጠመኝ በሳቸው አንደበት እንዲህ ይተረካል፦
[በ1953 ዓ.ም በነሀሴ ወር በጎጃም ክፍለሀገር በደጋ ዳሞት አውራጃ ዋሸራ የቅኔ ትምህርት ቤት በነበርኩበት ጊዜ 3 ሰዎች አብሾ ሲጠጡ ጠብቀን ብለው እኔንና ጓደኛዬን ዛሬ የቅኔ መምህር ማሞ ሀብተ ማርያምን ከዋሸራ በግምት 15 ኪሎሜትር ርቆ በሚገ/ነው በአካባቢው ሰው በሌለበት በዮሀንስ ገዳም ወስደውን በአንድ ሰፊ ደጀ ሰላም ውስጥ ገብተን ሳለ ቀኑ መሸት ሲል አብሾውን በስንዴ ዳቦ ጋግረው ሶስቱም ከበሉ በኋላ በሩን በጥብቅ ዘግተን ፀሎት ጀመሩ። ከዚያ ፀሎቱን እየፀለዩ ለሁለት ሰአት ያህል እንደቆዩ አንዱ እሪ፥ እንሽሽ ያለንበት ቤት ተቃጥሏል አለና ውሸቱን አስተጋባ። ወዲያው ለመሸሽ ከግድግዳ ጋራ እየተላተመ ስለአስቸገረ እኛ እና ሁለቱ ያልሰከሩ ጓደኞቹ ከአንድ ወጋግራ ላይ በገመድ አሰርነው። ወዲያው ሁለተኛው ተማሪ አንዳንድ ትንቢት ብጤ ሲናገር ቆይቶ “ሸማ ስራዬን አላሰራ አላችሁኝ፥ ቁቲቴን ስጡኝ” እያለ ስላስቸገረን እንደፊተኛው ከአንድ ወጋግራ ላይ ሸብ አደረግነው። ወዲያው የቅዳሴ ዜማ እንደጀመረ አንቀላፋ። ሶስተኛወ ግን ስካር እንደጀመረው “ተው ና ውረድ ቡሬ” እያለ የአራሽ መሰል ንግግሩን ጀመረ። ከዚያም ቀጥሎ
የበሬው ውለታ ይገለፃል ማታ
እብቁ በግርግብ ውሃው በገበታ።
እያለ ሲያዜም ቆይቶ እንቅልፍ ወሰደው። ከዚያ በኋላ መጀመሪያ የሰከረው ሰው የቅኔ ዘረፋውን ቀጥሎ ዶሮ እስኪጮህ የጀመረ እስኪነጋ ድረስ እጅግ በጣም ብዙ ቅኔ ድርሰቶችን ሲደርስ አድሯል።

ከዚያ በኋላ ሶስቱ እንቅልፍ ወስዷቸው ቀኑን ከዋሉ በኋላ ሌሊቱን አድረው በሶስተኛው ቀን ሙሉ አእምሯቸው ተመልሶላቸዋል፥ አንዳንድ ጊዜ ሲገላበጡ እየጠራን እህል ውሃ እነዲቀምሱ ስንጠይቃቸው በጣም ይበሳጩ ነበር። የታሰሩትን ፈትተን ልብሳቸውን ሲጥሉ እያለበስን አስተኝተን ተራ በተራ ያለምንም ድንጋጤ ስንጠብቅ ሰንብተናል። ከዚህ ውስጥ አስገራሚው ሁኔታ ሰካራሞቹ እኛን ለመደብደብ አልሞከሩም። ስንቆጣቸው ቶሎ ደንግጠው ትእዛዛችንን ይቀበሉ ነበር።]

2018 ማርች 2, ዓርብ

ዋ! አድዋ! (ኄኖክ ስጦታው)

ዋ! አድዋ! 

 “Many died…[and] no one knows their names…but their names are written in Heaven, in the book of life…for they became martyrs…” The Mannawe Manuscript 
“ብዙዎች ሞቱ ... [እና] አንዳችም ስማቸውን የሚያውቅ ሰው የለም ... ነገር ግን ስማቸው በመንግሥተ ሰማያት፣ በህይወት መዝገብ ላይ ተጽፏል ... ሰማዕታት ስለሆኑ ...” 
*

አንድ ወቅት ላይ የኢጣሊያ መንግስት ስልጡን ለሆነው ህዝቡ አንድ እቅድ አቀረበ። የእቅዱ ስያሜ “የኢጣሊያ ክቡር ተልዕኮ” ይሰኛል። “ክቡር ተልእኮ” ምንድነው?!
ኢጣሊያ፣ የውስጥና የውጭ ችግሮቿን ለመፍታት ከነደፈቻቸው እቅዶች አንዱ በአፍሪካ ውስጥ ያላትን የቅኝ ግዛት ማስፋፋት ነበር። በ1860ዎቹ(እኤአ) ውስጥ በኢኮኖሚ መዋዠቅ ውስጥ ለተዘፈቀችው ኢጣልያ “ክቡር ተልእኮ” ታቀደ። የገጠር ነዋሪዎች እና በድህነት ውስጥ ያሉ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢጣልያውያን የተሻለ ሕይወት ለመፈለግ ሀገራቸው መሰደዳቸውን ለማስቀረት የኢጣሊያ ንጉሥ የሆኑት ንጉሥ ኡንቤርቶ በአፍሪካ የሚካሄደው ቅኝ አገዛዝን ይበልጥ ማስፋፋት ሁነኛ መፍትሄ ይሆን ዘንድ ተለሙ፤ እቅዳቸውም ከአገር ከመሰደድ ይልቅ ለአገር መሰደድ ላይ ያተኮረ ነበር። ስያሜውንም “የኢጣሊያ ክቡር ተልዕኮ” በሚል ገለፁት። ድህነት፣ ሥራ አጥነትና የውጪ አገራት ጣልቃ ገብነት ጫናን ለማስወገድ መፍትሄ ለመስጠት የቅኝ ተገዥ አገራትን በአፍሪካ ማስፋፋት እንደ ታላቅ መሳሪያ ተደርጎም የወረራው አቅጣጫ ኢትዮጵያ ላይ አተኮረ።” (A Plebano, Storia dela Fianza Italiana III, Turin, 1902)
የጦርነቱ መንስኤ

ሚያዚያ 1881 ዓ.ም. ንጉሥ ምኒልክና እቴጌ ጣይቱ ውጫሌ በሚባለው ቦታ ሳሉ የኢጣልያ ልኡክ የሆነው አንቶኔሊ፣ ንጉሥ ምኒልክን ለማግኘት ውጫሌ ድረስ በማምራት በኢጣሊያኖች የተረቀቀውን ውል አቀረበ። የውጫሌ ውል ሃያ አንቀጽ ያለውን ሲሆን በኢጣሊያ በኩል በንጉሥ ኡምቤርቶ ተወካይነት አንቶኔሊ ሲፈርም፣ በኢትዮጵያ በኩል ደግሞ በዳግማዊ ምኒልክ ተፈረመ። ስያሜውም “የውጫሌ ውል” ተባለ። 
ከዚህ ውል ውስጥ 17ኛው አንቀጽ በአማርኛው፣  “የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ከአውሮጳ ነገሥታት ለሚፈልጉት ጉዳይ ሁሉ በኢጣሊያ መንግሥት አጋዥነት መላላክ ይቻላቸዋል” ሲል፣ በኢጣሊያኛው ደግሞ “የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ከአውሮጳ መንግሥታት ለሚፈልጉት ግንኙነት በኢጣሊያ  መንግሥት አማካኝነት ማድረግ ይገባቸዋል” ይላል። ይህ አንቀጽ ውሎ አድሮ በሁለቱ ሀገሮች መካካል የአድዋ ጦርነት ተብሎ ለሚታወቀው ጦርነት መነሻ ምክንያት ሆኗል።
ውሉም እንደ ጸደቀ፣ “ኢትዮጵያ በኢጣሊያ ሥር ናት” የሚል ጽሑፍ በየጋዜጦቹ ላይ ታትሞ ወጣ። ይህንኑ መልዕክት የኢጣሊ ጠቅላይ ሚንስትር ክሪስፒ ጥቅምት አንድ ቀን 1882 ዓ.ም. ለአሜሪካና ለ12 አውሮጳ መንግሥታት አስታወቀ። በዚህ ሂደት ውስጥ ነበር ዳግማዊ ምኒልክ ሥርዓተ ንግሣቸውን ለማሳወቅ ደብዳቤ የጻፉላቸው መንግስታት፣ እንግሊዝና ጀርመን፣ ለአፄ ምኒልክ በጻፉት መልስ ላይ፣ በውጫሌ ውል መሠረት ግንኙነታችን በቀጥታ ሳይሆን በኢጣሊያን በኩል ብቻ ነው በሚል ያሳወቁት። ይህ ደግሞ አፄ ምኒልክን ይበልጥ አስቆጣ። የጣልያን አካሄድ የተለሳለሰ ቢመስልም ችግር ማስከተሉን የተመለከቱት አፄ ምኒልክ ጥር 19 ቀን 1882 ዓ.ም. ለኢጣልያው ንጉስ ኡምቤርቶ “ለአገሬ ውርደት እንደሆነ ደርሼበታለሁ…” የሚል መልእክት መላካቸውን “አፄ ምኒልክ እና የአድዋ ድል” የተሰኘው መፅሃፍ ይናገራል። 
*
አፄ ምኒልክ የውጫሌውን ውል በተዋዋሉ በአራተኛው ዓመት፣ ለአውሮጳ ኃያላን መንግሥታት የውጫሌን ውል ማፍረሳቸውን የካቲት 4 ቀን 1885 ዓ.ም. በደብዳቤ አስታወቁ። 
በህዳር 1886 ዓ.ም. የኢጣልያ ጠቅላይ ሚኒስትር የሆነው ክሪስፒ፣ አንቶኔሊን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጸሐፊ፣ ጄኔራል ባራቲየሪን ደግሞ አዲሱ የኤርትራ ገዢ አድርጎ ሾማቸው። ጄኔራል ባራቲየሪ በ1886 ዓ.ም. አጋማሽ ላይ ጦሩን እየመራ የኢትዮጵያን ግዛት ዘልቆ በመግባት የሰሜኑን ክፍል በኃይል መያዝ ጀመረ። 
ጄኔራል ባራቲየሪ በ1887 ዓ.ም. ለዕረፍት ወደ ሮም ሲመለስ በጣሊያን ፓርላማ ተገኝቶ ንግግር ከማድረጉ በፊት፣ አባላቱ ከመቀመጫቸው ተነሥተው የደመቀ ጭብጨባ በመስጠት ተቀብለውታል። ንጉሡ ኡምቤርቶም ድል አድራጊው ጄኔራል ባራቲየሪን በማድነቅ የጣልያን ኃይልን “የሠለጠኑ የበላይነት ኋላ–ቀር በሆኑ ላይ” በማለት አወድሰውታል። ጄኔራል ባራቲየሪም “በጥቅምት ወር ጦርነት ይኖራል። የእኛ የሠለጠነው አሥር ሺህ ጦር ከሃያ ሺህ እስከ ሰላሳ ሺህ የሚደርሰውን ያልሠለጠነ የኢትዮጵያ ጦር በቀላሉ ያሸንፈዋል፤ የኢትዮጵያውን ንጉሥ በቀፎ አድርጎ ሮም ያመጣዋል” ሲል በኩራት  ተናገረ። በቅኝ ግዛት መስፋፋት ምኞት ሕልም የሰከረው ፓርላማም ንግግሩን ከሰማ በኋላ የጄኔራሉ ዓላማ እንዲሳካለት ለአንድ ሺህ ተጨማሪ ወታደሮች መቅጠሪያ በጀት አፀደቀለት። ጄኔራል ባራቲየሪ በመስከረም 15 ቀን 1888 ዓ.ም. ተመልሶ ምፅዋ ገባ። በዘመኑ ከጣልያን የወገኑ ቅጥር ወታደሮችን ከአፍሪካ የመለመላቸው ሲሆን በቀን አንድ ሊሬ ከሽልንግ ይከፈላቸው እንደነበር  “The Battle of Adwa: African Victory in the Age of Empire” የተሰኘው መጽሐፍ ይነግረናል። 
ንጉሠ ነገሥት አፄ ምኒልክም የውጫሌውን ውል ሲያፈርሱ፣ ከኢጣሊያኖች ጋር ጦርነት የማይቀር መሆኑን አውቀውት ስለነበር፣ ወታደሮቻቸውን ማዘጋጀትና ዘመናዊ የጦር መሣሪያዎችን ከራሺያና ከፈረንሳይ በጅቡቲ በኩል ማስመጣት ቀጠሉ። በ1895 ዓ.ም. በአጠቃላይ ለዚህ ጦርነትዝግጅት አፄ ምኒልክ ከ70 -100 ሺህ የሚደርስ ዘመናዊ ጠብመንጃ እና 5 ሚሊዮን ጥይት መግዛት ችለው ነበር።
የክተት ዐዋጅ
የጦርነት አይቀሬነት ርግጥ ሲሆን ኢትዮጵያም ለፍልሚያ ተዘጋጀች። ዝነኛው የአፄ ምኒልክ የክተት አዋጅም ነጋሪት እየተጎሰመ ተለፈፈ።
“እግዚአብሄር በቸርነቱ እስካሁን ጠላት አጥፍቶ አገር አስፍቶ አኖረኝ፤ እኔም እስካሁን በእግዚአብሔር ቸርነት ገዛሁ፡፡ ከእንግዲህ ብሞትም ሞት የሁሉም ነውና ስለእኔ ሞት አላዝንም፡፡ ደግሞ እግዚአብሔር አሳፍሮኝ አያውቅም፤ ወደፊትም ያሳፍረኛል ብዬ አልጠራጠርም፡፡ አሁንም አገር የሚያጠፋ፤ ሃይማኖትን የሚለውጥ፣ በፊት እግዚአብሔር የወሰነልንን ባህር አልፎ መጥቷል፡፡ እኔም የአገሬን ከብት ማለቅ፤ የሰውን መድከም አይቼ እስካሁን ዝም ብለው ደግሞ እያለፈ እንደፍልፈል መሬት ይቆፍር ጀመር፡፡ አሁን ግን በእግዚአብሔር ረዳትነት አገሬን አሳልፌ አልሰጠውም፡፡ የአገሬ ሰው ከአሁን ቀደም የበደልሁህ አይመስለኝም፡፡ አንተም እስካሁን አላስቀየምኸኝም፡፡ ጉልበት ያለህ በጉልበትህ እርዳኝ። ጉልበት የሌለህ ለልጅህ፣ ለምሽትህ፣ ለሃይማኖትህ ስትል በሃዘንህ እርዳኝ፡፡ ወስልተህ የቀረህ ግን ኋላ ትጣላኛለህ፡፡ አልምርህም፡፡ ማርያምን ለዚህ አማላጅ የለኝም…”
(“አፄ ምኒልክና የኢትዮጵያ አንድነት” በተክለ ጻዲቅ መኩሪያ ገጽ 226)


የጦርነት ውሎ
ዘመቻው ጣይቱ ብጡል ከምኒልክ በላይ ግልተው የታዩበት ነበር። ጣይቱ ያስከተሉትን ጦር ይመሩ የነበሩት ባልቻ ከጦር መሪነታቸውም በተጨማሪ የምኒልክ ግምጃ ቤት ኃላፊ እና የዘውድ ጠባቂም ጭምር ነበሩ። ጣይቱ በሺህ የሚቆጠሩ ወታደሮች ብቻ ሳይሆን የሙዚቀኞች ቡድን ያቀፈ ስብስብ አካተው በሽለላና በፉከራ የታጀበ ቡድን ጭምር እንደነበር ታሪክ ይናገራል። 
ጦርነቱ የካቲት 23ቀን 1888 ዓ.ም. ማለዳ ተጀመረ። በወቅቱ ስለነበረው ሁኔታ “የተተከለው ድንኳን ሲታይ ከብዛቱ የተነሣ አፍሪቃ አውሮጳን ለመጠራረግ የተነሣች ይመስላል፡፡ የጦርነቱ ዕለት ኢትዮጵያውያኑ ደማቅ ቀለም ያለው ካባ ለብሰው፣ የነብርና ያንበሳ ቆዳ ለብሰው አዝማሪዎቹ እየዘፈኑ፣ ቄሶች፣ ልጆች፣ ሴቶች ሳይቀሩ ፀሐይዋ ፈንጠቅ ስትል በተራራው ላይ በታዩ ጊዜ የኢጣሊያን ጦር አሸበሩት፡፡”  ሲል ታሪክ ጸሃፊው በርክለይ ይገልፀዋል።
በጦርነቱ ላይ ከተሳተፉት የታሪክ ምስክሮች መካከል ፊታውራሪ ተክለ ሐዋርያት ተክለማሪያም አንዱ ሲሆኑ “ኦቶባዮግራፊ” በተሰኘው ማስታወሻቸው ላይ የጦርነቱን ውሎ እንዲህ ሲሉ ይተርኩልናል፦
“ጠመንጃ ሲንጣጣ ሰማን፤ መድፍ ወዲያው ያጓራ ጀመር። ተኩሱ እያደር እየባሰበት ተቃረብን። ዐረሮቹ ማፏጨት ጀመሩ። የቆሰሉ ሰዎች ተቀምጠው አገኘን።… ጦራችን ተደበላልቋል። ሰውና ሰው አይተዋወቅም።… ሴቶች በገንቦ ውሃ እያዘሉ፣ በበቅሎቻቸው እንደተቀመጡ፣ ለቁስለኞች ውሃ ያቀርባሉ። ሲነጋገሩ ሰማኋቸው። “ኧረ በጣይቱ ሞት” ይላሉ።… ነጋሪቱ ከግንባርም፣ ከጀርባም፣ ከቀኝም፣ ከግራኝ ይጎሸማል። የተማረኩ ጣልያኖች አየሁ። ወዲያው ምርኮኞቹ በዙ። አንዳንዶቹ ወታደሮች ሦስት ይበልጥም ጣልያኖች እየነዱ መጡ። በኋላ የምርኮኞች ብዛት ለዓይን የሚያሰለች ሆነ። ድል ማድረጋችንን አወቅሁት። ጣልያኖች መዋጋታቸውን ትተው ማርኩን እያሉ ይለምናሉ።” 
አክለውም፣ ጦርነቱ አልቆ እንኳን ወደግንባር የሚሄደው የሰው ብዛት እንደ ውሃ ሙላት እንደነበር ፊታውራሪ ተክለ ሐዋርያት ይገልፁታል። 

“The Battle of Adwa: African Victory in the Age of Empire” መጽሐፍ ስለጦርነቱ ሲገልፅ፦
“የጣልያን ሠራዊት በመገስገስ ላይ የነበሩትን የኦሮሞ ፈረሰኞች በተመለከተበት ወቅት የሚገባበት ጠፋው፡፡ ቀድሞ በሠራዊቱ ውስጥ ስለኦሮሞ ፈረሰኞች የተነገራቸው ኋላ ቀር እና ተራ ተዋጊዎች እንደሆኑ ነበር፡፡ በጦር ሜዳ ላይ የተመለከቱት ግን ፈረሰኞች እጅግ ፈጣን እና የተካኑ መሆናቸውን ነበር፡፡
“የጀ/ል አርሞንዲ የበታች ከኾኑት መካከል ጂዩቫኒ ቴዶኔ ለሠራዊታቸው መሸነፍ ቁልፉን ሚና የተጫወቱት የኦሮሞ ፈረሰኞች መሆናቸውን መስክሯል፡፡ የወቅቱን አስፈሪ ሁኔታ ሲገልፅም “ፈረሰኞቹ ወደ ሽለቆሁ ሲወርዱ በድንገት የገነፈለ ጥቁር ባህር ይመስሉ ነበር” ብሏል፡፡ በወቅቱ ሌ/ኮ አጎስቲኖ ቺጉ ፣ ሌ/ኮ ሎኔንዞ ከምፕያኖ ፣ ሌ/ኮ ጊሊዮ እንዲሁም በመጨረሻ ራሱ ጀነራል አሪሞንዲ አንድ በአንድ መግደላቸውን ጠቅሷል፡፡
“በርካታ የጦር መሪዎች ራሳቸውን አጥፍተዋል፡፡ ል/ኮ ጋሪባልዲ ቬናዞ እና ሌ/ኮ ማዞሌኒ የኦሮሞ ፈረሰኞችን ጦርና ጎራዴ በመፍራት በራሳቸው ሽጉጥ ራሳቸውን አጥፍተዋል፡፡ ቴዶኔ ሁኔታውን ሲገልፅ በተለይ ኮ/ል ፔናዚ መጀመሪያ የተኮሰው ጥይት ስላልገደለው ለኹለተኛ ጊዜ ደረቱን በራሱ ጥይት መምታቱን ገልጿል፡፡ ራሱ ታዶኔ ቆስሎ የተማረከ ሲሆን ጦርነቱም በዚያው ተጠናቋል፡፡” 
*
የአድዋ ጦርነት ድል አሸናፊ ይሆናል ተብሎ በተደመደመለት ኃያል መንግስት ተቃራኒ ሆነ። ድሉም በአሸናፊዎቹ ዘንድ ወራሪን መክቶ መመለስ ቢመስልም ውጤቱ ግን በሃያላን ሃገራት አስገድዶ ቅኝ የመግዛት ስርዓት እና ደካማ ሃገራትን ለመቀራመት በጉልበት የመግዛት ሂደት ውስጥ ለቅኝ ገዢዎችም ሆነ በቅኝ ተገዢነት ላሉት ሁሉ የማይታመንና አስደንጋጭ የዓለማችን ክስተት ለመሆን በቃ። “ጥቁር ሕዝቦች የባርነት ቀንበር ለመሸከምና ተገዢ ለመሆን የተፈጠሩ እንደሆኑ” ያምኑ የነበሩትንም ጭምር ቆም ብለው እንዲያስቡ ከማድረግም አልፎ ሽንፈታቸውን በግድ እየመረራቸው ለመመስከር አስገደደ። ይብስ ብሎም መጽሔቶች የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ዳግማዊ ሚኒሊክ የኢጣሊያን ንጉስ በጦር ሲወጉ የሚያሳይ የካርቱን ምስል አስደግፎ በመዘገብ አንድ ሃያል አገር “ኋላ ቀር “ እንደሆነ በሚታመን “ጥቁር ሕዝብ” መሸነፉን አወጀ። ይህኔ ነበር በግልጽ ለኢጣልያ ወግኖ የሚፅፈው የጆርጅ በርክሌይ ምስክርነት እንዲህ የቀል፦
“ከሰፊው የፖለቲካና የታሪክ ትንታኔ አኳያ የዐድዋ ጦርነት በአፍሪቃ ምድር አዲስ ኃይል መነሣቱን የሚያበስር ይመስላል። የዚህች አህጉር ተወላጆች፣ የማይናቅ ወታደራዊ ኃይል ሊሆኑ እንደሚችሉ ልናሰላስል ተገደናል።… ነገሩ አስቂኝ ቢመስልም፣ ይህ ሁኔታ (ማለትም ዐድዋ) ጨለማይቱ አህጉር በላይዋ ላይ ሥልጣኗን ባንሰራፋችው በአውሮጳ ላይ የምታደርገው አመፅ የመጀመሪያው ምእራፍ ነው…”
*
የታሪክ ተመራማሪው ባሕሩ ዘውዴ “የኢትዮጵያ ታሪክ” በተሰኘው ምርምራቸው ሥራቸው ላይ በገፅ 89 እንደገለፁት “ዐድዋ ልዩ ትኩረት ያሰጠው ጥቁሮች በነጮች ላይ የተጎናጸፉት የመጀመሪያው ዐቢይ ወታደራዊ ድል በመሆኑ ነው…።”
*

2018 ጃንዋሪ 18, ሐሙስ

ምስር ብሉ!

(ኄኖክ ስጦታው) 


ምስር ባህል ነው። ምስር እውቀት ነው። አኗኗራችን ከምስር ጋር ተቆራኝቷል። ባህላችን፣ ልምዶቻችን፣ የሥነምግባር ተግዳሮታቸረን፣ የመረጃና የእውቀት መለዋወጫ መንገዳችንም ጭምር ነው-ምስር። በሀዘንና ደስታችን ውስጥም አለ በሃዘን ቤት ምስር አለ። በለቅሶ ቤት ውስጥ ምስር አለ። ምስር የወጥ ግብኣት ብቻ አይደለም። የሃዘናችን ተካፋይና የደስታችንም ተጋሪ ጭምር እንጂ። 

አስደሳች ነገር ሲያጋጥመን “የምስራች!” እንላለን። “ምስር ብላ/ ብዪ)” አፀፋችን ነው።  በሃዘናችን ጊዜ ገበታ ነው። በሞት ለተለየን ሰው ሃዘን በተቀምጥን ጊዜም ለሃዘንተኞች የሚቀርብ የገበታ ስርዓታችን አካልም ሆኖ ዘመናት ተሻግሮ ዛሬ ላይ ደርሷል። 

ምስርን የነውራችን መሸፈኛና የጓዳ ውስጥ ገመናችን ቋንቋም ጭምር ነው። በአደባባይ ስንገልጠው ለማይገባቸው የተደበቀ፣ ለሚግባቡበት ግን የአደባባይ እውነታ ጭምር። ለሚያውቁት ብቻ የመግለጫ መግባቢያ መሳሪያችን ነው። በአዋቂዎች ዘንድ ሚስጥራዊ መግባቢያ በመሆንም ያገለግላል።

በአንዳንድ አካባቢዎች ባል “እራት ምንድነው?” ብሎ በየቀኑ ይጠይቃል። ምክንያቱ እራቱን ምን እንደሚበላ ማወቁ ላይ እንዳይመስላችሁ። “እራት ምስር ነው” ከተባለ፣ ምላሹ ሁለት ተቃራኒ ትርጓሜ ያላቸውን ንግግሮች አጣምሮ ይይዛል። አባወራው ቀኑን ሲማስን ደክሞት ከዋለና ቤቱ ገብቶ እራቱን በልቶ መተኛት ብቻ ከሆነ ፍላጎቱ መርዶ ነው። ከሚስቱ ጋር “እንትን” አምሮት ከሆነ ደግሞ የምስራች!
ምስር ብሉ

እኛ እኮ ቃለ-ጽዩፎች ነን። እንኳን ተገላልጠን ይቅርና ተከናንበን እንኳን ምግባራችን በተከናነቡ ቃላቶች ውስጥ የመገለጥ ክዋኔው ክብርን የሚያዋርድ ሳይሆን የሚያገዝፍ የሚሆንብን። በሃዘን ቤት ውስጥ ባል ያላቸው ሴቶች ይግባቡባቸዋል ተብለው ውስጥ ውስጡን በእድሜ ደርሰን ከታዘብነው ንቁሪያ መካከል አንዱ ይሄን ይመስላል፦

ሚስት ለአዘንተኛው ምስር ወጥ ጨላፊ ናት። ምራት ደግሞ እንጀራ አቅራቢ። እና ምራት በቅናት ርር ብላ ለሚስት “ከምስሩ በደንብ ጨልፊለት” ስትል በነገር ትወጋታለች። ሚስትም ቀላል ሰው አልነበረችምና፦
 ያንቺን እንጀራ በልቶ ሲጨርስ እጨልፍለታለሁ” አለች አሉ። 
እስቲ ምን እንደተባባሉ የገባው ሰው ስንት ይሆኝ?

ከተረታችን ውስጥ “እንትን” ምን እንደሆነ በማይታወቅበት ዘመን አንድ ምሳሌያዊ አባባል ተፈጥሮ ነበረ። የሚገርመው ነገር የዚህ “እንትን” ምንነት ዛሬም ድረስ ግልጥልጥ ብሎ አልታወቀም። ዘመን ገስግሶ፣ መግባባት በዕድሜና በአቻ መሆኑ በቀረበት የሳይበር ዘመን ላይ ደረስንና በተግባር ሊመለሱልን ለሚገቡ ጥያቄዎች ጉግል በማሰስ ብቻ ተቆነፃፅለን ስናበቃ “እሱን ትደርስበታለህ” ስንባል፣ “እሱን ስትገረፍ ታወራዋለህ” በማለት እድገትና መድረስ በማይፈታው መደነቋቆር ዘመን ውስጥ ከታላላቆቻችንና ከታናናሾቻችን እኩል ቁመት ይዘን ሳንግባባ መኖር ከጀመርን ሁለት አስርታት እየተቆጠሩም አይደል? ታዲያ ለዚህ መፍትሄው መንድነው?

ምስር ነዋ! ምስር ሃይል ነው! ምስር ብርታት ነው! ምስር አስተምህሮት የሚጠናበት አንዳች መላ መቀየሻ መንገድ ነው! ምስር አብሮነት ነው! ምስር ከላይ እንደተገለፀው “እንትን” ቀስር ነው! “እንትን” ማለት ግን ምንድን ነው? ብለን ብንጠይቅ ሁሉም ሰው በአንድ ድምፅ “እንትን ነዋ!” የሚል አይጠፋም። እንትን ግን ምስጢር ነው። በዘመናችን “እንትን” የሚለው ቃል ሳይወድ በግድ ትርጉም አልባ ቃል መሆኑ ቀርቶ ውስን ትርጓሜን ብቻ እንዲይዝ የተገደደ የግፍ እስረኛ ቃል ሆኗል! #እንትን_ይፈታ! 
  

አንድ ጥንታዊ ተረት አለ። የገበሬዎች የእርሻ ማሳ ላይ የዘሩትን አተር በድብቅ እየገባች የምትበላ አንዲት ጦጣ ነበረች። በዚህ ድርጊቷ የተማረሩ ገበሬዎች ተመካክረው አንድ ውሳኔ ላይ ደረሱ። “ማሳችን በጦጣ እየተደፈረ፣ ያሸተው ፍሬም እየተበላሸ ምርታችን ቀነሰ። ድካማችን መና ቀረ። ምን እናድርግ?” ሲሉም ተመካከሩ። “ምስር ዘርተን ለምን አንገላገልም?” ሲሉ አንድ አዋቂ አባት መፍትሄ አመላካቱ። እናም ሁሉም ተስማምተው በአተር ፋንታ ምስር ዘሩ። ታዲያ ሰብሉ ሲደርስ ለማዳዋ ጦጣ ወደሰብሉ በመግባት ምስሩን ትቀምሰዋለች። ፍሬው ከማነሱ የተነሳ እንኳን ለመብላት ለመያዝና ለመፈልፈል አልመች ቢላት በሰው ልጅ ተበሳጭታ ስተሰበቃ፤ 
“አተር መዝራት ወይ ብልሃት
ምስር መዝራት፣ ሥራ ማጣት!” በማለት ተረተች። 

የማይወዱትን ማጣጣል የሚወዱትን ነገር ከፍ ከፍ ማድረግ የሰው ልጅ ስር ሰደድ ጠባይ እንደሆነ ለማስተማርና ለማመላከት የቀረበ ቀላል የመወያያ ተረት እንደነበር ልብ ይሏል።


*****
ምስር፦
ለወጥ የሚኾን ፍሬው ዐነስተኛ አበባ እህል (ብርስን ምስር ([ግዕዝ])። በአፍሪቃ ሰሜን በሚዲቴራኔአን ባሕር ወሰን ያለ ከፍልስጥኤም ጋር የሚዋሰን ምስር በሚስራይም ምስር የተባለ የጥንት አንቲካ የሚገኝበት።

ምስር፦
ቃና የቀንድ ጡሩንባ የቀንድ መለከት በዐመት በዐል ቀን በንጉሥ ፊት የሚነፋ ነው ምስር ቡዋቡዋ ሠረገላ ማለት ነው የነፊው ትንፋሽ በቡዋቡዋው በሠረገላው ውስጥ እየተላለፈ ልዩ ልዩ ድምፀ ቃናን ስለሚአሰማ ምስር ቃና ተባለ ምስር ቡዋቡዋ ቃና ዜማ ([ዐረቢኛ])።ያይጥ ምስር ቅጠሉ ምስር የሚመስል ሐረጉ እንደ አደንጓሬ ሐረግ የሚሳብ ፍሬው ጠንካራ። ግብጥ ምስር አንድ ዐይነት ወጥ።

ብርስን (ግዕዝ ሲሆን ቃሉ ትርጓሜው ‘ምስር’ ነው)፦ በቁሙ ብርስን (መ፡ ፈ)፡፡ ስመ ሀገር ግብጥ የሚጽራይም ክፍል ሚጽር፡፡ ሊጣፍ የሚገባው በጻዴ ነው እንጂ በሳት ሰ፡ አይዶለም፡፡ ደለወ ምስር፡፡ ማዕልቃ ዘምስር፡፡

ቮልቴር ስለ ቃላት የሃሳብ መሸሸጊያ መሳሪያነት ሲናገር እንዲህ ብሎ ነበር፦ “ዋናው የቃል ጠቃሚነቱ ሃሳባችንን ለመሸሸግ ማገልገሉ ላይ ነው”

ለምሳሌ  በ“የምስራች” ውስጥ “ምስር ብላ” ተሸሽጓል። በምስር ውስጥ “ወሬ የለውም ፍሬ” የሚለው አስተምህሮ ተቀብሯል። የምስራች ወሬ ቢሆን ኖሮ “ወሬ- የለውም ፍሬ!” የሚለው ቃል ምስር ወጥ ሆኖ በተበላ ነበር። ወሬ የደቃቋን የምስር ፍሬ ያህል ዋጋ ከሌለው ታዲያ ስለምንስ “የምስራች!” ይበሰራል? በርግጥ ብስራት በሚለው ቃላት ውስጥ (ብስል-ዕራት እና ምስር) ተሸሽገው ይሆን? ወይስ ራሱ “ምስራች” የሚለው ቃል (ምስ-እራት) ከሚለው ተወልዶ? 

አያሌ “የምስራቾች ወሬ ሆነው ለፍሬ ሳይበቁ እንደሚያልፉ ምሳሌ የሚሆን ሰሚ ያጣ ተናጋሪ ምርር ብሎ እንዲህ ተናግሯል ሲሉ ሰማሁ፦

“ወሬኛ ሳይጠፋ ሞልቶ ተትረፍርፏል
ራብ የሚያስታግስ፣ የሚሰማኝ የታል?”

ምስር የወሬን ያክል አቅም ባይኖረውም ወሬን በተግባር (በቅንጣት ፍሬው አልመሽምሾታል። ወሬ አቅም አልባ እንደሆነ ከቅንጣት ያነሰው ፍሬ ምስክር ተጠርቷል። ምክንያቱም ዛሬ ስለ ምስር የማበስረው ገድሉን እንጂ ወሬ ብቻ ባለሞኑም ጭምር ነውና ተከተሉኝ፥ 

በአበው እና እመው አንደበት “ጦር ከፈታው፣ ወሬ የፈታው” እንደሚበልጥ ስነገረን እያደመጥን አድገናል። ያም ሆኖ ግን ወሬ የምስርን ያህል ቅንጣት ፍሬ የለውም። “ወሬ- የለውም ፍሬ!” ለአበባ የለውም ገለባ! ሲባል ያለምክንያት አልነበረም። ፍሬ ያለው ወሬ እንዳለ ጭምር ለማመላከት ነው። ያ ፍሬ ያለው ወሬ ደግሞ “የምስራች” ነው!
“የምስራች!”
ምስር ብሉ!
“የደገኛ ነወይ ወይስ የቆለኛ፣
የምሥራች ሞተች የሚል አማርኛ፣
እኛም ብንመረምር ሰውም ብንጠይቅ፣
የምሥራች ሞተች ተብሎም አያውቅ”

ጥንታዊ ከሆኑ ሰብሎች መካከል የሚመደበው ምስር የጥንታዊውን የግብርና አብዮት ካቀጣጠሉት ሰብሎች ውስጥ በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳል። በቅርቡ በግሪክ፣ በግብፅ እና በቱርክ የተገኙ የአርኪዮሎጂ ግኝቶች የሚመሰክሩትም ይሄንኑ እውነታ ነው። 

ከስምንት ሺህ አምስት መቶ አመት በፊት የሰው ልጆች ምስርን አምርተው ለምግብነት አውለውት የነበረ ከመሆኑም ባሻገር፣ በቅዱስ መፃሕፍትና በጥንታዊ መዛግብት ላይ ሳይቀር ብዙ ተብሎለታል። 

በመፅሐፍ ቅዱስ ውስጥ ኤሳው ብኩርናውን በምስር ማጣቱ አንዱ ምሳሌ ነው። ኤሳውና ያዕቆብ መንታ ወንድማማቾች ናቸው። ኤሳው ቀድሞ በመውለድ ይበልጠዋል። ኤሳው አዳኝ በመሆኑ አንድ ቀን ደክሞት ወደቤቱ ሲመለስ ያዕቆብ ምስር ወጥ እየሰራ ይደርሳል። የይስሐቅ የመጀመሪያ ልጅ የነበረው ኤሳው የብኩርና መብቱን በማራከሱ የተነሳ አንድ ቀን ኤሳው ተርቦ ሳለ ምግቡን ባየ ጊዜ ብኩርናውን (ውርሻው) መብቱን ለስጋ ድክመቱ አሳልፎ የሚሰጥበት አጋጣሚ ይፈጠራል። ይህም በዘፍጥረት 25:30 እንዲህ ተገልጿል።  

“ቶሎ በል እባክህ፣ በጣም ስለደከመኝ ከዚያ ከቀዩ ወጥ የተወሰነ ስጠኝ!” አለው። በዚህ ጊዜ ያዕቆብ “በመጀመሪያ የብኩርና መብትህን ሽጥልኝ!” አለው። ኤሳውም “እኔ ለራሴ ልሞት ደርሻለሁ! ታዲያ የብኩርና መብት ምን ይጠቅመኛል?” አለው። ያዕቆብም “በመጀመሪያ ማልልኝ!” አለው። እሱም ማለለት፤ የብኩርና መብቱንም ለያዕቆብ ሸጠለት። ከዚያም ያዕቆብ ለኤሳው ዳቦና ምስር ወጥ ሰጠው፤ እሱም በላ፣ ጠጣም፤ ተነሥቶም ሄደ። በዚህ መንገድ ኤሳው የብኩርና መብቱን አቃለለ።” ከዚያ በኋላ ስሙ ኤዶም (ቀይ) ተባለ። ቄእ ወጥ? ቀይ ምስር? (ብቻ ከሁለት አንዱን ነው)

ምስር በዋነኝነት ለሰው ልጅ ምግብነት ብቻ ሳይሆን በአንፃሩ ሲታይ አነስተኛ መጠን ቢሆንም ለእንስሳት መኖ ጥቅም ላይ ይውላል። በፕሮቲን የበለፀገ ሲሆን፣ ካርቦሃይድሬት 47-65% ፕሮቲን 20-33%፣ 2-4% መአድናት እና 2% ቅባት ይዟል። በተለምዶ “ደም ማነስ” የሚለው አገላለጽ በደም ውስጥ በቂ ሂሞግሎቢን አለመኖሩን የሚያመለክት ነው። በሂሞግሎቢን ሞለኪውል ውስጥ የሚገኙት አራት ወሳኝ የብረት አተሞች ከሌሉ በዚህ ሞለኪውል ውስጥ የሚገኙት የተቀሩት 10,000 አተሞች ምንም ፋይዳ አይኖራቸውም። ስለዚህ ጤናማ ምግብ በመመገብ በቂ የብረት ማዕድን ማግኘት በጣም አስፈላጊ ነው። በብረት ማዕድን የበለጸጉ የምግብ ዓይነቶች ውስጥ ዋንኛው ደግሞ ምስር ነው። 
*ምስር ለብርታት!
የአይረን (ብረት) እጥረት ለጤና መዛባትና ለአካላዊ መዳከም እንደሚያጋልጥ ተደርሶበታል። ምስር ብርታትን ለመጨመር ይጠቅማል። ልብ በሉ፤ በተለምዶ “ደም ማነስ” የሚለው አገላለጽ በደም ውስጥ በቂ ሂሞግሎቢን አለመኖሩን የሚያመለክት ነው። በሂሞግሎቢን ሞለኪውል ውስጥ የሚገኙት አራት ወሳኝ የብረት አተሞች ከሌሉ በዚህ ሞለኪውል ውስጥ የሚገኙት የተቀሩት 10,000 አተሞች ምንም ፋይዳ አይኖራቸውም። ስለዚህ ጤናማ ምግብ በመመገብ በቂ የብረት ማዕድን ማግኘት በጣም አስፈላጊ ነው። በብረት ማዕድን የበለጸጉ የምግብ ዓይነቶች ውስጥ ዋንኛው ምስር ነው። 
ምስር ብሉ!
ቀላሉ ነገር ምስር “እንትን” የከላከላል። እውነቴን ነው፤ ማለት ካንሰርን ይከላከላል! 
ምስር ብሉ!


2017 ማርች 14, ማክሰኞ

የካህኑ የመጨረሻ ቃል

አንድ ካህን በጠና ታሞ ከተኛበት ሆስፒታል ውስጥ እንዳለ በነፍስ ተይዞ እያጣጣረ፣ አንድ ፖሊስ እና  አንድ ፖለቲከኛ እንዲጠራለት ዶክተሩን አጥብቆ ለመነ።

ከደቂቃዎች በኋላ እንዲጠሩለት የጠየቃቸው ሰዎች ከሆስፒታሉ ተገኝተው ከአልጋው ግራ እና ቀኝ ቆመው ነበር። 

ካህኑ የሁለቱንም እጅ የቀረውን እንጥፍጣፊ አቅም አሟጥጦ ያዘ። ፖለቲከኛው ሰው ግን እጅግ ተጨንቆ ጠየቀው፦

“እኛን ለምን ብለህ እንዳስጠራኸን አልገባኝም። ግን ለምንድን ይሆን?”

ካህኑ ትንፋሹን ሰብስቦ እንዲህ አለ፦

“እኔም ልክ እንደ ኢየሱስ በተመሳሳይ መንገድ በሁለት ወንበዶች መካከል መሞት እፈልጋለሁ ...”

እናም ሞተ !!!!

አባይ ጠባብ መንገድ

(ኄኖክ ስጦታው)

የወንዝ አገሩ መነሻው፤ የወንዝ አገሩ መድረሻው
ወንዝ የሌለበት አገር ነው፣ መውጫ መግቢያው የጠፋው¡
*
የወንዞች ህብር ውጤት፤ የውኆች ስብስብ ጥምር
አባይ ፀሎቴን ስማ፣ ልንገርህ አንዳች ምስጢር።

ወደሄድክበት ውሰደኝ፤ እኔም አፈር ነኝና፣
ከአገሬ አንዴ ከወጣሁ፣ ሌላ ወንዝ አላጣምና።
*
አባይ ፀሎቴን ስማ፣ ከነአፈሬ አብሬህ ልውጣ
ሺህ ቢጎድል ተገድቦ፣ ሺህ ቢሞላ የሚቆጣ
ወንዝ ብቻ እንደሆነ፣ አውቃለሁኝ፤ ታውቀዋለህ!
አብረን ታስረን፣ ነፃ እንውጣ።

2017 ጃንዋሪ 9, ሰኞ

በእንክርዳድ ማሳ ላይ (ስኬች)

(ኄኖክ ስጦታው)

*1*
ስንዴ እና ገብስ እንክርዳድ ተነቅሎ ከተዘጋጀው የማሳ ላይ ተዘሩ።

“ሞተን እየተቀበርን መሆን አለበት ” አለ ገብስ።

“አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ” የተባለው ቃል እየተፈፀመ ነው። ሲል ስንዴ መለሰ።

*2*

ጥቂት ዘሮች በወፎች ተበሉ። ብዙዎችም መበስበስ ጀመሩ። መበስበሳቸው የህይወታቸው ፍፃሜ አልነበረም። የሌላኛው ሕይወት ጅማሬ እንጂ።

*3*
የማቆጥቆጥ ዘመን

“እነሆ የመጨረሻው ዘመን ፍሬዎች እንሆን ዘንድ ለፍርድ ተነስተናል።” ሲል አንዱ ስንዴ አጠገቡ ላለው ሌላ ስንዴ ተናገረ።

“አይደለም። ፀድቀን ነው። ዙሪያህን ተመልከት! እኛ ብቻ አይደለንም የፀደቅነው። ከመካከላችን ጥቂት ወንድሞቻችን ፀድቀዋል።”

ገብስ ተናገረ “እኔ ከመሰሎቼ ነጥሎ ከናንተ መካከል እንድበቅል ያደረገው ፈጣሪ ተቆጥቶ ቢሆን ነው።” አለ ዙሪያውን ለከበቡትን ስንዴዎች።

እንክርዳድ ግን ከመካከላቸው ሆኖ“ወዶኛልና አዳነኝ” እያለ ጮክ ብሎ ይዘምር ነበረ።

2017 ጃንዋሪ 5, ሐሙስ

“ጠጣህብኝ”!

አንድ እጅግ ያዘነ ሰው ባር ውስጥ ተቀመጦ ፊት ለፊቱ ያለውን መጠጥ ላይ እንዳተኮረ ሰላሳ ደቂቃ በላይ ቆየ። በዚህ መሐል አንድ ጠጪ ወደርሱ ቀርቦ ጠረጴዛው ላይ ያለውን መጠጥ አንስቶ ሻት አደረገው።

ምስኪኑ ሰው ስቅስቅ ብሎ ማልቀስ ጀመረ። “ተረጋጋ ወንድሜ፣ ለጨዋታ ነው  የጣሁብህ። ሌላ መጠጥ አዝልሃለሁ” ሲል ሊያረጋጋው ሞከረ።

“ነገሩ አልገባህም፣ ዛሬ ለእኔ ሲበዛ በመከራ የተሞላ ቀን ነው። ጠዋት መስሪያ ቤት ስብሰባ ላይ ጥቂት ደቂቃ አርፍጄ ብገኝ አለቃዬ ከስራዬ አሰናበተኝ። ወደ ቤት ለመመለስ መኪናዬን ወዳቆምኩባት ቦታ አመራሁ። በቦታው ግን አልነበረችም። መኪናዬ ተሰርቃ ነበር።  ለፖሊስ አመለከትኩ። እነሱ ግን ምንም ሊረዱኝ እንደማይችሉ ገልፀው አሰናበቱኝ። በጣም እያዘብኩ በኮንትራት ታክሲ ወደቤት ስመለስ ሞባይሌና የእጅ ቦርሳዬን ረስቼው ወረድኩ። ከዚህ ሁሉ መከራ ልታፅናናኝ የምትችለው ባለቤቴ ብቻ ነበረች። እሷም ቤት ስገባ ከአትክልተኛችን ጋር አልጋ ላይ ተኝተው ደረስኩ። ነገሮች ሁሉ ከአቅሜ በላይ ሆኑ። በመጨረሻ ወደዚህ ባር የመጣሁት ራሴን ላጠፋ ነበር። አንተ ግን መርዜን ጠጣህብኝ።”