2013 ጁላይ 20, ቅዳሜ

ውዝግብግብ …. ዘዶሮ ማነቂያ /ከሌላኛው ምዕራፍ የተቀነጨበ/ --- በ-ኄኖክ ስጦታው




ውሾቼን ገደሏቸው! መርዝ የተቀባ ስጋ ሰጥተው ውሾቼን ገደሏቸው፡፡

ቀባሪዬ፣ መግደል እንጀራ በሆነበት አገር እንደመኖር ውስብስብ ነገር እንደሌለ ተረዳሁ፡፡ “ውሾች ለጤና ጠንቅ ናቸው” በሚል መርዝ አበሏቸው፡፡ ውሾች የመኖር መብት አላቸው፤ ፍጥረት ናቸውና፡፡ ባለቤት የሌላቸው መሆናቸው ግን አስገደላቸው፡፡ ልከላከል ሞክሬ ነበር፤ እንዳይበሉት ለማድረግ ጥሬ ነበር፤ ገዳዮቹን ለማባረር ጥሬ ነበር፤ ግን ብቻዬን ነኝ! ውሾቼኮ የበጋ ወዳጆቼ ናቸው፡፡ ይህ ክፉ ክረምት ውሾቼን ዳግም እንዳላያቸው የመሰናበቻ ጊዜ ሆነ፡፡ አለቀስኩ፣ ጮህኩ፣ ጉልበቴ ደክሟል፡፡ በጎረምሶች እጅ እግሬ ተይዟል፡፡

 የመንደሪቷ ነዋሪዎች የውሾቹን አሟሟት በማየት ለራሳቸው ደስታን ሲፈጥሩ እውነቴን ነው የምልህ ይበልጥ ጠላኋቸው፡፡ ለዚህች መንደር ነዋሪዎች የሞት ስቃይ ማየት የሚፈጥረውን ደስታ ማጣጣም አዲስ አይደለም፡፡ ሰዎች የሞት ቅጣት ይበየንባቸው የነበረበት ቦታ እዚህ መሆኑን እወቅ! ከብዙ ዓመታት በፊት የሞት ፍርደኞች በአደባባይ ይሰቀሉ እንደነበር ቦታ ላይ ነኝ፡፡ ይህ ታሪክ የማይረሳው ሰው በአደባባይ በሞትና በህይወት መሀል በነፍስ ከስጋ ለመለየት የሚደረግ መንፈራገጥን ምንነት የተገለጠበት ቦታ ነው፡፡ ይግባህ! የማወራው ድሮ ማነቂያ ስለነበር ስፍራ ነው፡፡ በክር አንገትህ ታንቆ መሞት ምን እንደሆነ የምታይበት ስፍራ፡፡ መንደሬን ያወካት መሰለኝ፡፡ ሞትን ወደህ ሳይሆን ተገደህ መጎንጨት ሰውን ሳይሆን የሞትን ክብር መንካት ነው፡፡

 መርዝ የተለወሰ ስጋ የበሉ ውሾች ሲዳከሙና ለሀጫቸውን ማዝረክረክ ሲጀምሩ ቦት ጫማና የጎማ ጓንት ያጠለቁ ገዳዮች በእጃቸው የያዙትን የብረት ማነቂያ አንገታቸው ውስጥ እየከተቱ አነቋቸው፡፡

ተፈጥሮ በህይወት ጉዞ ውስጥ ከለገሰቻቸው ሞቶች የበለጠ የሰዎች ፈጠራ ውጤት የሆነ የመግደያ ብልሃቶች ዘግናኝ ናቸው፡፡ ምስኪን….፣ ውሾቼ ሰዎችን ማመናቸው አሳዘነኝ፡፡ ትላንት በአደባባይ፣ ሊያውም በጠራራ ፀሐይ ጎዳና ላይ ሲተኙ ኮቴም ሆነ የመኪና ጥሩንባ አይቀሰቅሳቸውም ነበር፡፡ ሰው በመኖሩ ብቻ መኖር የቻሉ አድርገው የወሰዱ ይመስለኛል፡፡ ሰው ሳይኖር መኖር የሚሳነው ሰው ብቻ መሆኑን አውቀዋለሁ፡፡ ውሾቼ አለቁ! እንቁራሪቶቼም ለህፃናት መጫወቻ እየሆኑ ነው፡፡ ከሞት የተረፉትን በጋ ላይ አልሰማቸውም፡፡ የውሾቼ በድን መኪና ላይ ሲጫን የሞት ትርኢቱ ተደመደመ፡፡ የመንደሬ ለቅሞ አዳሪዎች ወደሬሳነት ተለውጠዋል፡፡ ገና ለገና አብደው ሰው የጎዳሉ በሚል ፍራቻ የመኖር መብታቸውን አጡ፡፡ አንድ ቀን እኔም `ጭራቅ” ሆኜ ደማቸውን እንዳልመጥ ይገድሉኝ ይሆናል፡፡ እጅ እግሬን ጠፍረው ይዘውኝ የነበሩ ወጣቶች ለቀውኝ ሄደዋል፡፡ ምሽት ብርታት እስቲሰጠኝ ባለሁበት መቆየትን መረጥኩ፡፡

ቀባሪዬ፣ ይህች የሰዎች ታንቆ መሞቻ መንደር ከስሟ ጀምሮ የብቻዬ እንጉርጉሮ እንዲያገረሽ አደረገብኝ፡፡

አንቺ ዶሮ ማነቂያ የሆንሽው ዶሮ ማነቂያ ሆይ! ዛሬ ምኒሊክ አደባባይ የሆነው ስፍራሽ ላይ የነበረው ትልቅ ዋርካ ይታየኛል፡፡ ያን ጊዜ አለመፈጠሬ ዋርካሽ በፈረሰኛው ምንሊክ ሃወልት ቢተካም፣ የግሪኮች ጣሪያ አልባ (አንፊ) ቴአትር የመሰለው ዘመንሽን ውስጤ በከሰተልኝ ዋርካሽ የጥቁር ብካይ ሂደትሽ ይታየኛል፡፡ አንቆ መግደልን “ፍትህ” ነው ብለው የሚያምኑ ነገሥታቶችሽ አጣብተውሽ ከሄዱት ክፉ ባህርይ ጋር ዛሬም ያው መሆንሽ፣ ዛሬም ማነቂያ መሆንሽን አወጋሻለሁ፡፡

2013 ጁላይ 19, ዓርብ

ብሌንን ያስታወሰኝ “ንቅሳት” ወ “ንክሳት” - ኄኖክ ስጦታው



ካፌ ውስጥ ነኝ፡፡ አንድ ሰው ከፊቴ እጀ ጉርድ ካናቴራ አድርጎ ካፑቺኖውን ይጠጣል፡፡ ቡና ከረባቴን አዝዤ ሰውየው ላይ አፈጠጥኩ፡፡ በእጆቹ ክንዶች ላይ ተነቅሷል፤ ተነቃቅሷል፡፡

በደህና ጊዜ የረሳሁትን “ታቱ”ዬን አስታወሰኝ፡፡

የንቅሳት ጠበብት ፡- “ንቅሳት ዘመን የማይሽረው ውጨ-ተውብሆ ነው” ይላሉ፤ ሊሆን ይችላል፡፡ እናቴ አንገቷ ላይ ተነቅሳለች፤ የአጎቴ ልጅ ደግሞ ድዱ ላይ ጉራማይሌ ተነቅሷል፡፡ እኔ . . . ሃሃሃ . . . ክንዴ ላይ ተነቅሼ ነበር፡፡ ጓደኞቼ ንቅሳቴን ዓይተው “ተነክሰህ ነው ተነቅሰህ?!” እያሉ ሲያላግጡብኝ አስፈግፍጌ አስጠፋሁት፡፡ /አስጠበስኩት ብል ይቀለኛል፡፡/ ጥሎት ያለፈውን ጠባሳ ስመለከት እውነታቸውን እንደሆነ አረጋግጣለሁ፡፡ አሁን ነዋ ከንቅሳትነቱ በላይ ንክሳት እንደሆነ የሚያስታውቀው፡፡
  
ሰውየው….
በእጆቹ ክንዶች ላይ ተነቅሷል፤ ተነቃቅሷል፡፡ በቅጥልጥል የእንግሊዘኛ ፊደል የተጻፈ ነው፡፡ ትርጉሙን ለመረዳት ለማንበብ ሞክሬ አልተሳካልኝም፡፡ እንኳን ተቀጣጥሎ እንዲሁ በ“ARIAL font” ተጽፎም አይነበብልኝም፡፡

 የድሮው ንቅሳት አንገት እና ጥርስ ብሎም ግንባር እና አገጭ ተኮር ነበር፡፡ ዘመንኛው ንቅሳት ጥቂት የማሸጋሸግ ሂደት ይስተዋልበታል፡፡ አንገት ላይ የነበረው፣ ወደ ደረት . . . ድድ ላይ የነበረው ወደጆሮ ግንድ  . . . የተጨመሩት ደግሞ፣   ጀርባ ላይ እና እምብርት ላይ ያሉት ናቸው፡፡ /ዘለቅ ብዬ አላየሁም እንጂ ሌላም፣ ሌላም ቦታ ላይ ተነቅሰው ይሆናል፡፡/

ንቅሳታሙን ሰው ምን እንደተነቀሰና ለምን እንደተነቀሰ ልጠይቀው አሰብኩ፡፡ ግን፣ ምንስ ቢነቀስ እኔ ምን አገባኝ?? አልኩና ተውኩት፡፡  ለምን ጥያቄውን ከእራሴው አልጀምርም፡፡እኔ ለምን ነበር የተነቀስኩት?!

“ብሌን” የተባለች ቆንጆ ወደድኩና ተነቀስኩ፡፡ የተነቀስኩ ሰሞን ከቅጥነቴ የተነሳ “ቆዳ ቅብ” አይት ነበርኩ፡፡ ታቱ የሠራልኝ ሰው ብዙ  አሪፍ አሪፍ ዓይነት አማራጭ ምስሎች ነበሩት፡፡ ግን ምኔ ላይ ይንቀሰኝ?? አልወደድኩትም እንጂ የሚመጥነኝ “ታቱ” አግኝቶልኝ ነበር፡፡ ልክ እንደ እጅ አምባር ሆኖ ክንድ ላይ የሚነቀስ፡፡ ትርጉም አልባ ነገር ከመነቀስ እስከነአካቴው አለመነቀስ ይሻላል፡፡ “ብሌን” ብለህ ነቅሰኘኝ አልኩት፡፡ ነቃሹ “አይሆንም” ብሎ ሞገተኝ፡፡ “ብሌን” ሶስት ፊደላት ነው፡፡ ክንድህ ደግሞ ወደታች እንጂ ወደጎን ቦታ የለውም፡፡ ስለዚህ “የዓይን ምስል” ይሻልሃል፡፡ አለና አሳመነኝ፡፡ ተነቀስኩ፡፡ የንቅሳቴ ቀለም ባግባቡ ሳያጠግግ ከብሌን ጋር ተለያየን፡፡ እንዴት እንደተለያየን አላውቅም፡፡ ስጠረጥር ግን “ለምን የአባቴን ስም አብረህ አልተነቀስክም??” በሚል አኩርፋኝ ሊሆን እንደሚችል እጠረጥራለሁ፡፡

እና አሁን በካፌ ውስጥ ካፑቺኖ የሚጠጣውን ሰው ሰውነት እና ቅጥልጥል የበዛበት ንቅሳት ሳስብ አንድ ነገር ተገለፀልኝ፡፡ ይህን ጊዜ እኮ “ብሌን ኃይለ ማርያም” ብሎ ይሆናል የተነቀሰው!

አንተ ሰውዬ፤ ልብ በል!!   “ንቅሳት ዘመን የማይሽረው መዋቢያ ቢሆንም ለተነቃሹ ግን ልዩ ምልክት ነው፡፡”


2013 ጁላይ 15, ሰኞ

“የፒያሳ አመልህን ይዘህ ቦሌ አትሂድ” - ኄኖክ ስጦታው



ወደ ቦሌ አካባቢ ሄደህ ፣ መዝናናት ካማረህ እባክህን ከማጨብጨብ ተቆጠብ፡፡

ከእለታት በአንድ የተረገመች ቀን እንዲህ ሆንኩላችሁ፡፡ ደምበል አካባቢ ካለው “ላ ፓራዚያን ካፌ” እግር ጥሎኝ ገባሁ፡፡ ከውስጥ መግባት ፈርቼ ወይም ሸሽቼ ከበረንዳው በስተቀኝ ወዳለችው የመናፈሻ ሳምፕል ወደመሰለችኝ “መናፈሻ” ገብቼ ተቀመጥኩ፡፡ ለደቂቃዎች ዞር ብሎ የሚያየኝ አስተናጋጅ አጣሁና በጭብጨባ ለመጥራት እጄን ማፋተግ ጀመርኩ፡፡ ያው …. ፒያሳ የለመደብኝ አመሌ አገረሸ፡፡

/ፒያሳ እኮ ካላጨበጨብክ የሚታዘዝህ አስተናጋጅ ጥቂት ነው፡፡ ኧረ አንዳንዴማ፣ አስተናጋጅ ለመጥራት ልታፏጭ ሁሉ ትችላለህ፡፡ የምመክርህ ነገር ቢኖር የፒያሳ አመልህን ይዘህ ቦሌ አትሂድ ፡፡/

ይህ አመሌ አገሸና ማጨብጨብ ጀመርኩ፡፡ አጨበጨብኩ፡፡ ዝም!
ደጋግሜ አጨበጨብኩ፡፡ ጭጭ!

የጭብጨባዬ ድምጽ “ላውድ” ላይ አድርጌ ቀወጥኩት፡፡ አሁን ዘዴዬ ሠራ መሰል አንዲት አስተናጋጅ መጣችና ቁልቁል በመመልከት “ምን ይጠበስ?!?” በሚል አስተያየት ታየኝ ጀመር፡፡

“ምንድን ነው?! ሳጨበጭብ አትሰሙም እንዴ!??!” አልኩ ቁጣ ባጠቃው ድምፀት፡፡

“ይኸው ልጨፍር መጣሁ እኮ!!” አለች እጆቿን ወገቧ ላይ አድርጋ፣ ትከሻዋንም “እስከስ” እያደረገች፡፡

ኧረ፣ መውረግረግ!!!


ምነው እጄን በቆረጠው! ምነው አቅሜን አውቄ እዛው ፒያሳ ባጨበጭብ!! ሃሃሃ /ባላጨበጭብስ/