2013 ጁላይ 24, ረቡዕ

የኔዋ ምርጥ ቮልስ /ዩሴን ቦልት/ በ-ኄኖክ ስጦታው


ከዚህ ቀደም በዚህቹ ጉደኛ ቮልስ መኪናዬ ዙሪያ በጥቂቱ አውርቼላችሁ ነበር፡፡፡ እስቲ ዛሬ ደግሞ ጥቂት ትውስታዎቼን ላካፍላችሁ፡፡

ያው መቼስ የቮልስ ባሉካ የሆንኩ ሰሞን የወረት ነገር በጥቂቱም ቢሆን ደባብሶኝ ነበር፡፡ መኪናዋን ማሽከርከር እንደጀመርኩ ወዳጅ ዘመዶቼን ሁሉ በመኪናዋ መስኮት ነበር ሰላም የምለው፡፡ መሬት የምረግጠው ከቤት ስወጣና እቤት ስገባ ነው፡፡ ቁርስ፣ ምሳ ፣እራት የምመገበው እዚህቹ መኪና ውስጥ ነበር፡፡ ጥቂት ጓደኞቼ በጣም ስናፍቃቸው ይደውሉና “ኧረ በጣም ናፍቀኸናል፤ መቼ ነው በአካል የምናገኝህ?” ይሉ እንደነበር አስታውሳለሁ፡፡ በአካል እንደማያገኙኝ ቁርጡን ሲያውቁ ይህን ውሳኔ አስተላለፉ፡፡“በተገኘበት ቦታ ከመኪናው ላይ ተጎትቶ እንዲወርድ!!!” 

ደግነቱ እነሱ ጎትተው እኔን ከማውረዳቸው በፊት የፍሪሲዮን ካቦ ተበጠሰና ቮልሴን እያስጎተትኩ ጋራጅ ገባሁ፡፡ ያኔ በአካል ጋራጅ ድረስ መጥተው አገኙኝ፡፡ መኪናዋ ተሰርታ እስክታልቅ ድረስ ከጋራጅ አልወጣም ብዬ ነበር፡፡ ሜካኒኩ “ሲያልቅ እንጠራሀለን፡፡ በቃ፣ ሂድ” በማለቱና በእነሱ ጉትጎታ እጅግ አዝኜ ወጣሁ፡፡ መኪናዬ ተጠግና ስትወጣ በድጋሚ ጠፋሁባቸው ፡፡ 

ለቮልሴ የዘመኑን ሲዲ ማጫወቻ ያስገጠምኩላት ሰሞን ጓደኞቼ ብቻ ሳይሆኑ አገርም “ጉድ!” አለ፡፡ ጥቂቶች “ለቮልሱ ሲዲ ማጫወቻ ገጠመለት” አሉ፡፡ ብዙዎቹ ደግሞ “ለሲዲ ማጫወቻው ቮልስ ገጠመለት፡፡”

ከሁሉም የሚገርመኝ አንድ ሰሞን ወንድሜ ይነዳት ነበር፡፡ ከግቢ ውስጥ አውጥቶ መቶ ሜትር ያህል ያሽከረክርና የዋናው አስፓልት መንገድ ላይ አቁሞ በታክሲ ይንቀሳቀስ በነበረበት ሰሞን ይህቺው ቮልስ ቅፅል ስም ወጥቶላት ጠበቀኝ፡፡ እሱንም የነገረኝ ወንደሜ ነው፡፡ 

“እንዴት ናት ቮልሴ?” ብዬ ስጠይቀው፡-
“ምን እዚህ ሰፈር መች ያስነዱና!?? ቁጭ ብለው ቅፅል ስም መስጠት ነው ስራቸው፡፡ መኪናዋን ማን እንዳሏት አልሰማህም!? ” 
“ማን አሏት!?”
“ዩሴን ቦልት” 
እንደዚህ ጊዜ ስቄ አላውቅም፡፡ ወንድሜ መቶ ሜትር እየነዳ በመቶ ሜትር ጃማይካዊ ሯጭ ስም አስጠርቶልኝ አረፈው፡፡  

ይችው መኪና አንድ ከባድ ችግር አለባት፡፡ ጭንቀት አትችልም፡፡ ልብ ድካም ያለባት ይመስለኛል፡፡ በቃ፣ የተጨናነቀ አደባባይ መሀል ገባታ ቀጥ ነው! ጭንቀቷ ሌሎችን መኪና ይበልጥ እስኪያጨናንቅ ድረስ የአደባባዩን ውጥረቱን ታንረዋለች፡፡ እንደዚህ ሲሆን ከሶስት ያላነሱ ትራፊኮች ወደኔ ይመጣሉ፡፡ ያው ከቆመች መምጣታቸው እንደማይቀር ስለማውቅ የሞተር ቀሚሷን/ኮፈኗን/ ከፍቼ “ፖምፔታዋን/ ፊውል ፓምፕ” በውሃ እያቀዘቀዝኩ እጠብቃቸዋለሁ፡፡

“ከሥራ ክፉ ኩርኩር ግፉ” እንዲሉ . . . በጣም ጥቂት ሰው በቀር “መሀል አደባባይ ላይ ቮልስ ብንገፋ ስማችን ይጠፋል” ብለው ስለሚያስቡ ትራፊክ ፖሊስ እስኪመጣ ድረስ ከመጠበቅ በቀር አማራጭ እንደሌለኝ በሹፍርና አጭር ዘመኔ የቀሰምኩት ጥበብ ነው፡፡ ቮልስ ለመግፋት ዝንባሌ ያላቸው ጥቂቶቹም ቢሆኑ ከገፉ በኋላ እጃቸውን ዘርግተው በተራዬ ብር ወደነሱ እንድገፋ ስለሚጠይቁ አይመቹኝም፡፡ትራፊኮቹ ግን ገንዘብ የሚጠይቁኝ ሞተር ሲጠፋ ሳይሆን እኔ ሳጠፋ ነው፡፡ ከእነሱ ብዙዎቹ፣ “የቮልስ ሹፌር የሆነው በጣም ቢቸግረው ነው” ብለው ስለሚያስቡ መክረው የሚለቁ ናቸው፡፡ /አቦ መካሪ ትራፊክ አትጡማ/

እንደምንም ከተጨናነቀው መንገድ በተራፊክ እያስገፋሁ ልክ ነፃ መንገድ ሳገኝ ሞተሩ በራሱ ጊዜ ተረክ ብሎ ይነሳል፡፡  
  
የገዛኋት ሰሞን ባትሪዋ የኋላ መቀመጫ ስር ነበር፡፡ የመቀመጫው ታች ጥምዝምዝ ሽቦዎች አሉ፡፡ ከእነሱ በላይ እንደ እንቅብ የሚመስል የደረቀና የሳር ባህርይ ባለው ግብዓት መቀመጫው ተደልድሎ ጨርቅ ለብሷል፡፡ ይሄ ጥምዝምዝ ሽቦ ከመቀመጥ ብዛት በመላላቱ ሰው ሲቀመጥበት ወደ ባትሪው ወርዶ ከ“ኔጋቲሽ” እና ከ“ፖዘቲቭ” አካሉ ጋር እየተነካካ “ማሳ” (እሳት) ይፈጥራል፡፡ ይህን “ጥበብ” ያወቅኩት በተግባር ነው፡፡ ሁለት ጓደኞቼን . . . አንዱን ከፊት ሌላውን ከኋላ ጭኜ ስዘውር ከኋላ የተቀመጠው ጋደኛዬ በተረብ መልክ እንዲህ አለ፡-

“መቀመጫው በጣም ይሞቃል፡፡ ሃሃሃ . . . "ኤሲ" አስገጠምክለት እንዴ!?”

“ሞተሩ ከኋላ ስለሆነ ሙቀት ወደውስጥ ገብቶ ይሆናል፡፡” አልኩት በባለሙያ አገላለፅ ልበ ሙሉ ሆኜ፡፡

“አይመስለኝም” አለ እየትቁነጠነጠ፡፡ “ወደዳር አድርገውና እንየው፡፡ መቀመጥ አልቻልኩም . . .” እያለ ሳለ መኪናዋ ጨሰች፡፡ የኋላ በር እንኳን አልኖራት፡፡ ተፈጥፍጦ አንድ ነገር ይሆን ነበር ፡፡ድንጋጤ አስፈንጥሮ እላያችን ላይ ጣለው፡፡ እንዴት እንዳቆምን ትዝ አይለኝም፡፡ ጥቂት ሮጥ ሮጥ ብለንም ነበር፡፡ የሆኑ ሰዎች ለዚሁ ጉዳይ ያጠራቀሙት የሚመስል እጅግ የቆሸሸ ውሃ እያመጡ ወደውስጥ ይረጩ ጀመር፡፡ ብቻ እሳቱ "ወደሌሎች" ሳይዛመድ በቁጥጥር ስር ዋለ፡፡ 

ታዲያ ያኔ (መኪናዋ እየተቃጠለች ሳለ) እኔ ባልለውም ዛሬ ድረስ እንዲህ ብሎ ነበር ይባላል፡፡ ውሃ እየደፉ እሳቱን ሊያጠፉ የሚረባረቡትን ሰዎች፡-

“ተውዋት! ትቃጠል! እኔንም እንዲህ ነበር ያቃጠለችኝ!!!”

2013 ጁላይ 22, ሰኞ

ውዝግብግብ …."ያላዘነው ውሻ እኔ ነበርኩ" በ-ኄኖክ ስጦታው





ዛሬ ደግሞ አንድ ወጣት ተሰቅሎ ሞተ፡፡ ወጪ ወራጁ ደረቱን በጆቹ ጠፍሮ መንሾካሾክና መረጃ መለዋወጥ ጀመረ፡፡ ሁሌም በሚሞት ሰው ላይ እንዲህ አይነት ነገር ይንፀባረቃል፡፡

“ቅድም ሰላም ብሎኝ ነበር ያለፈው፤ የሚሞት አይመስልም ነበርኮ” ትላለች አንዷ ለሌላዋ፡፡

 “ትላንት ከኛ ጋር ነበር ያመሸው፤ ምንም የተለየ ነገር አይታይበትም ነበር” ይላል ሌላው፡፡

“ሌሊት ውሻ ሲያላዝን ሰምቼ ደግሞ ማንን ሊገፋ ነው ይህ ሟርተኛ እያልኩ ሳስብ እንቅልፍ ባይኔ ሳይዞር ነጋ፡፡” አንዲት እናት ከጎናቸው ላሉ እኩያቸው ሲናገሩ ሰማሁ፡፡

ቀባሪዬ፣ እኔ ነኝ ውሻው፡፡ ሌሊት እንቅልፍ እንቢ ሲለኝ አላዘንኩ፡፡ እንደውሾቼ ጮህኩ፡፡ የሞት ጠረን ሸቶኝ ግን አልነበረም፡፡ ታንቆ መሞት ለዚህች መንደር አዲስ አይደለም፡፡ የሚሞት ባይኖር እንኳን የሚረዳ አይጠፋም፡፡ የጥሩንባ ድምፅና የውሻ ማላዘንን በሚፈራ ማህበረሰብ “የሞት መልእክተኛ” ተብዬ ለመፈረጅ ጊዜ አልፈጀብኝም፡፡ በጥቂት ሰዓታት ውስጥ ብቻ ውሻው እኔ እንደነበርኩ ሁሉም ነዋሪ አወቀ፡፡ ምሽት ላይ ከታጣቂዎች ጋር  ተፋጠጥኩ፡፡

“ሌሊት ስትጮህ ታይተሃል!” አለኝ አንዱ መሳሪያ ታጣቂ፡፡

“እና?”

“ምን “እና” ትላለህ? ለምን ሰላማዊ ሰውን ትረብሻለህ?” አፈጠጡብኝ፡፡

“እናንተ ለምን እኔን ትረብሻላችሁ?”

“ተነስ እንሂድ”

“አልነሳም!”

“መታሰር ትፈልጋለህ?” በሚያባብል ድምፀት ሌላው ተናገረ፡፡

“መታሰር ምንድነው?” መለስኩለት ጤነኛ እንዳልሆንኩ አንዴ ደምድመዋል፡፡ የትም ይዘውኝ ሊሄዱ እንደማይችሉ አውቃለሁ፡፡ ሊደበድቡኝ ይችላሉ፡፡ ሊያጠቁኝ አቅሙ አላቸው፡፡ ሰላማዊ ሰው ረብሼ ይሆናል፡፡ ለእኔ ግን ሰላማዊ ሰው በውሻ ድምፅ የሚረበሽ አይደለም፡፡ ቀድሞ እራሱን ባጉል እሳቤ የበጠበጠ ሰላማዊነቱ አይታየኝም፡፡

“አማኑኤል መግባት ትፈልጋለህ?” ብረት አንጋቹ ጠየቀኝ፡፡ የሱ ግንዛቤ አማኑኤልን ጥላቻ እዚህ የተቀመጥኩ መስሎት ይሆናል፡፡ ከዚህ የተሻለ ስፍራ ሊሆን ይችላል፡፡ ማገገሚያ አያስፈልገኝም፡፡ ግን ማየት ፈለኩ፡፡

“አዎ! አማኑኤል ውሰዱኝ!” ለመንኳቸው፡፡ ደጋግሜ ወተወትኳቸው፡፡ ማሰሪያ ገመዳቸው ተበጣጠሰ፡፡ አማኑኤልም ሊወስዱኝ አይችሉም፡፡ ታዲያ ለምን መጡ? ሊያስፈራሩኝ? ሊደበድቡኝ? እስኪሰለቹኝ ድረስ ኃይለ - ቃል ወረወሩብኝ፡፡ የማያደርጉትን ዛቱብኝ፡፡ ሰላማዊ ሰው ብረብሽ ከባድ እርምጃ እንደሚወሰድብኝ አስጠንቅቀው ነገሩኝ፡፡ በእነርሱ ዘንድ እብድ መሆኔ አስንቆኛል፡፡ በእኔ ዘንድ ሰላማዊ ሰው መሆናቸው አስንቋቸዋል፡፡ በመሰሎቻቸው ላይ የሚያደርሱት ቅጥቀጣ ለካስ እብድ መሆናቸውን ስላላመኑላቸው ነው! እብድ መሆኔን ማመናቸው ነፍስ ባጠፋም እንዳይፈርዱብኝ ያደርጋቸዋል፡፡ ምክንያቱም እብድ ነኛ! ህጉም ቢሆን ከጎኔ የሚቆመው ሰዎች ሰብአዊነቴን ስለሚዳፈሩ ሳይሆን ወንጀለኛ መሆን ስችል ብቻ ነው፡፡

 የሰላማዊነት ሎጅክ በነፍጥ አንጋች እና በኔ መካከል ልዩነት አለው፡፡ ዛሬ ባልጮህ ሰው አልበጠብጥም፡፡ ፍርሃታቸውን አልቆሰቁስም፡፡ አስተሳሰባቸው የወለደው ፍራቻ ይበቃቸዋል፡፡ ውሻ በጮኸ ቁጥር ግን ያስቡኛል፡፡ በኔ ላይ በሚጥሉት ሽርደዳ ሰላሜን ቢዳፈሩም እንቅልፍ አጥተው የሚፈሩትን ሞት አላስታውሳቸውም፡፡ ይህን ሳደርግላቸው ግን በመጮሄ የማገኘውን ሰላምን እየሰዋሁላቸው መሆኑን ይረዱት፡፡ እነሱም ይህ ውለታዬን አንድ ቀን ለመሬት ይከፍሉልኛል፡፡ ይሞታሉና!

አሽ-ሙጥ በ Henok Sitotaw