2013 ጃንዋሪ 19, ቅዳሜ

ቅዥት - ሄኖክ ስጦታው




ቅዥት

የህልም ዓለምን ሳካልል፣
በቁም ሳለሁ ተኝቼ
ከወደቅሁበት ፀሊም ዓለም፣
ሳልፈልገው ተገፍቼ፤
እንደ ሌሊቱ ቅዥቴ፣ መሮጥ ተስኖት እግሬ
ሳልፈልገው ተተብትቤ፣ እግር-ተወርች ታስሬ፤
ልክ እንደዚያው ቅዥቴ፣
በቁም ታፍኖ አንደበቴ
እንዳላመልጥ ከእስራቴ፣
በኖ ጠፋና ብርታቴ . . .

ዘመኔን በግድ ታቅፌ
በቃ እንዳልል ጋት አልፌ
ተወግቼ አንዳች መርፌ፤

ተውሰብስቤ በእልፍ ቅዥት
ስንቱን ዓለም አካለልኩት?!
መሬት ለመሬት ስንፏቀቅ፣
ሰማየ-ሰማያት ስንሳፈፍ
ድንገት መጋለብ ጀምሬ፣
ድንገት ባሕር ስቀዝፍ . . .
ስንቱን ዓለም አካለልኩት?!

የማላውቀው ፤ ግን ያየሁት
የምኖረው፤ ግን ያከልሆንኩት
የማፈቅረው፤ ግን ያጣሁት፤
የምመኘው፤ ግን ያልሆንኩት. . . !

ትላንት ቅዥት፣ ዛሬ ቅዥት
መዋል ቅዥት፤ ማደር ቅዥት፤ መኖር ቅዥት፣
ያሻሁትን ብቃዠውም፤
ቅዥቴን ግን አልኖረውም
የኖርኩትን አልቃዠውም!

መጋቢት፣ 28፣ 1999ዓ.ም
ሄኖክ ስጦታው ከ(ሀ-ሞት የግጥም ስብስብ መጽሐፍ፣ በቅርብ ቀን የሚወጣ)

2013 ጃንዋሪ 17, ሐሙስ

ሐዘንሽ አመመኝ/ ደበበ ሰይፉ















ውል አልነበረንም የፍቅር ቀጠሮ
ቃልም አላኖርንም በወግ ተቀምሮ፤
እኔ አንቺን እንዳላይ
አንቺ እኔን እንዳታይ አምባችን ተቃጽሮ
ዕጣችን ተካሮ፤
ቀለምሽ ከዐይኔ አሻራሽ ከጣቴ ባይጠፋ ተማትሮ
(እትብት እምብርት ሁኖ እንዲኖር ደድሮ)
ይኸው አካሄደን በድንገት ዘንድሮ።
የገጽሽ ብርሃን ቢጠይም ፀዳሉ
ድምፅሽ ቢቀጥንብኝ ቢሠልብኝ ቃሉ
ወዘናሽ ቢማስን ዛሬ ያለውሉ
በእጆችሽ ጨበጠኝ ሐዘንሽ ሥዕሉ
ሐዘንሽ አመመኝ
ብሶትሽ ጠቀሰኝ።

እኔ እወድሻለሁ /ገብረክርስቶስ ደስታ /



















ብዙ ሺህ ዘመናት
እልፍ አእላፍ ሌሊት
ሚሊዮን መሰለኝ
ፍቅሬ አንችን ስወድሽ ቀኑ ረዘመብኝ።
እኔ እወድሻለሁ
የሰማይ መሬቱን
የባህር ስፋቱን
የዓለም ዳርቻ የርቀቱን ያህል
እንደ ፅጌ-ረዳ
እንደ አደይ አበባ
እንደ ሎሚ ሽታ፡፡
እንደ እጣን ጢስ እንጨት፣ እንደ ከርቤ ብርጉድ፣
እኔ እወድሻለሁ፣
አበባ እንዳየ ንብ፡፡

2013 ጃንዋሪ 13, እሑድ

ይድረስ ለወንድሜ ለማላውቅህ (ባለቅኔ ሎሬት ፀጋዬ ገብረ መድኅን)




ይድረስ ላንተ ለማላውቅህ
ለወንድሜ ሩቅ ለማልፍህ
ለምታውቀኝ-ለማላውቅህ፥ ለምታየኝ-ለማላይህ. . .
ማነህ ባክህ?
ሳትወደኝም ሳታምነኝም፥ አጢነህ ለምትፈራኝ
ስናገርህ አጠንቅረህ፥ አተኩረህ ለምትሰማኝ....
ይድረስ ለክቡር ወንድሜ፥ ለአረህ ዟሪው ለገታሩ
ለሩቅ ገጠሬ ነባሩ
ለማላውቅህ ለዳር ዳሩ፥....
ማነህ